>
5:13 pm - Wednesday April 19, 2890

ቤተክርስቲያን እያቃጠሉ ሃገር እንገንባ የሚባል ተረት መስማት አልፈልግም ዝምታው ይሰበር!... (ዘመድኩን በቀለ)

“ ቸርች ማቃጠል ነበር! ወደፊትም ይቀጥላል!!!
– ይሄማ ጅማሮ ነው ” ከዚህ የሚከፋውን ነው እየጠበቅን ያለነው።   “ ዐቢይ አህመድ አሊ”
                         *★★★*
 •••
ሰሞኑን እንደ አዲስ ብንን፣ ብትት ብለውም ከጥልቅ እንቅልፋቸው የተነሱ ሰዎች እንደ ጉድ ሰፈሩን ሲረብሹ እያየሁ ነው። በሶማሌ ክልልና በጅጅጋ ከ10 በላይ አብያተ ክርስቲያናት ሲወድሙ፣ አበው ካህናትና ምእመናን በካራ ታርደው ወደ እሳቱ ሲጣሉ እያየ ባላየ ባልሰማ ጮጋ ሲል የከረመው ሁላ ሰሞኑን እንደ አዲስ እየዬ እያለ ሲል እያየሁት ነው።
•••
በከሚሴ፣ በሲዳማ ቤተ ክርስቲያን በቦንብ እና በእሳት ምእመናንና ካህናት በጥይትና በቢለዋ በድንጋይም ተደብድበውና ተቃጥለው እያየ የመደመር መንፈሱ እንዳይበላሽበት ጮጋ ሲል የነበረ ሁሉ ሰሞኑን እንደ ጉድ እንደ እብድም ያወራጨው ይዟል።
•••
አስቀድመን ስንናገር እንደ አፍራሽ፣ እንደ ጨለምተኛ፣ ሲያዩን የነበሩ ሁሉ ዛሬ ወብርተው እያየን ነው። ተዉ ረጋ በሉ። አትጣደፉ። ያለልክ አትዝለሉ ስንል እንደ ለውጥ አፍራሽ የቆጠሩን። ከሃይማኖታቸውና ከሃገራቸው በላይ ዘራቸው የበለጠባቸው ግለሰቦች ነገሩን እያወቁት ፣ አካሄድን እየተረዱትም ቢሆን በምንአገባኝ መንፈስ ተውጠው ጮጋ ነበር ያሉት።
•••
ኦሮሞና ትግሬ ነን የሚሉ የተዋሕዶ ልጆች በሙሉ የዳር ተመልካች ነበሩ። የዐማራ ዕዳም አድርገው ነበር የቆጠሩት። የሚገርመው ግን ችግሩ ማንንም አለመማሩ ነው። በምሥራቅ ኢትዮጵያ የጀመረው ኦርቶዶክስን የማውደም ጉዞ በደቡብ ኢትዮጵያ አልፎ በሰሜን ሸዋ ጎንደር ደርሷል። እንዲህ ሆኖም የአክሱም ጽዮን ልጆች ዝምታን መርጠዋል። “ ቸርች ማቃጠሉ ግን ወደፊትም ይቀጥላል ነበር ያሉን ጠቅላያችን። እስከመቼና ስንት ገዳማትና አድባራት እንደሚቃጠሉ ግን በዝርዝር አልነገሩንም። ብቻ ማቃጠሉ ጎንደር ደርሷል። ትግራይ ደግሞ ለጎንደር ጎረቤቱ ነው።
•••
ይሄም ብቻ አይደለም። ጠቅላያችን በተለያዩ ጊዜያት አፋቸው እንዳመጣላቸው እንዲህ ሲሉም ተደምጠዋል።
 “ … ከሳምንት በኋላ የሚኖሩንን አዳዲስ ሹመቶች አስመልክቶ ተቃውሞ ከገጠመን መተራረድ ይመጣል”።
ዐቢይ አህመድ አሊ “መተራረድ!” የምትለዋን ያዙልኝ!
“… በአሁኑ መንግሥት ላይ መፈንቅለ መንግሥት ማድረግ የሚሳካ አይደለም። በአንድ ቀን በመቶ ሺዎችን ሊያሳርድ የሚችል ዕቅድ ነው”።
ዐቢይ አህመድ አሊ። “ሊያሳርድ!” ይች የእርድ ጉዳይ ተምልሳ መጥታለች ትመዝገብልኝ
 “… እኔ ማረጋጋት ካልቻልኩ መንግሥታችን ተነካ ብለው፣ ከቡራዩ፣ ከለገጣፎ፣ ከሰበታ ሰው ታጥቆ እየመጣ ነበር” ። ”
ዐቢይ አህመድ አሊ። “…መንግስታችን ተነካ ብለው…!!! ? ይችም ከእርዱ ያልተናነሰች ማስፈራሪያ መሆኗ ነው
•••
ወዳጄ ደማሪህ እኮ “ ነቢይ” ነው። ነቢይ የሚነግርህንማ ጫ ብለህ ስማ። ሰምተህም እመን እንጂ። እመን እንጂ ወዳጄ፣ አትጠራጠረው፣ አትፍራውም። እሱ “ ነቢዩ ” ወደፊት ሊሆን ያለውን ነገር ሁሉ አስቀድሞ የነገረኽ እኮ ነው። ይኽን መሰል ትንቢት ደግሞ “ከነቢያት” በቀር ማን እንዲነግርህ ትፈልጋለህ? ይልቅ ፦
ዐቢዬ የኔ፣
ዐቢዬ የኔ፣
አንተን ባየሁ አይኔ፣
ሌላው ሌላው ለምኔ። የሚለውን ዝማሬህን ሞቅ አድርገህ ቀጥል። ጨፍር፣ ዝለል። ተቃጥለህ፣ ነድደህ፣ ታርደህ እስክታልቅ ድረስ። ጨፍር አልኩህ።
•••
ለእኔ በእኔ ዕይታ ዐቢይ አህመድ አሊ ሆደ ገራገር ነው። ነገር መደበቅ፣ መሰወር የማይሆንለት ገራገር። ዐቢይ አህመድ አሊ የሐረር ሰዎች ጠባይ ነው ያለው። ያሰበውን፣ ያቀደውን ሁሉ በፈለገው ሰዓት በፈለገው መድረክ ላይ ሳይደብቅ፣ ሳይሰስት ይነግርሃል። የሚሰማው አጣ እንጂ እሱስ መንፈስ ቅዱስ ፊቱን ፀፍቶ አፉንም ከፍቶ እያናገረው ነው። በዚህ በኩልስ እግዚአብሔር ይመስገን። ሆድ ያባውን ብቅል ያወጣዋል እንዲሉም ዐቢይ አህመድ አሊ ሳይጠይቁት ነው ሁሉን የሚዘረግፈው።
•••
ይልቅ እኔን የጨነቀኝ ከፊታችን ሊመጣ ስላለው ክፉ ዘመን
እነግራችሁ ዘንድ ከአባቶች የተላከን መልእክት እንዴት እንደምነግራችሁ ነው ግራ የገባኝ። እጄን ከሞባይል ጣቴ አገናኝቼ መጻፍ ሁላ ነው ያቃተኝ። አምና ሐምሌ 8 ንገር ያሉኝ አንድ በአንድ ተፈጽሞ ካየሁ በኋላ ይሄኛው አስፈራኝ። የአሁኑ አስፈራኝ። “ መጥነህ፣ በሚረዱት ቃል ንገራቸው። ለህዝቡ ንገረው ” ያሉኝን ቃል እንዴት እንደምናገረው ነው ግራ የገባኝ። ለማንኛውም የሰሞኑ መጥፋቴ ከዚህ ጭንቀት የተነሳም ነው። እስቲ ኃይል አሰባስቤ እንደምንም ልነግራችሁ፣ ልጽፍላችሁ እሞክራለሁ።
•••
#ማስታወሻ | ~ ከቪድዮው ላይ ለጦማሬ አጋዥ የሚሆነኝን ክፍል ብቻ ነው ቆርጬ የወሰድኩት። ሙሉውን ብትሰሙት ደግሞ የጠቅላዬን የታሪክ አረዳድ ስህተት ትሰሙበታላችሁ። የፀጋና የቅባትን የቦሩ ሜዳ ክርክር እስላሞች ታረዱበት የሚል አዲስ የፈጠራ ታሪክ ነው የምትሰሙበት። እኔ የመረጥኩት “ ቸርች መቃጠል ይቀጥላል ” የሚለውን ብቻ ነው።
•••
ሻሎም !   ሰላም ! 
ነሐሴ 23/2011 ዓም
ከራየን ወንዝ ማዶ።
Filed in: Amharic