>
5:13 pm - Wednesday April 19, 8079

የገዳ ሥርዓትና ዲሞክራሲ ምንና ምን ናቸው? (አቻምየለህ ታምሩ)

የገዳ ሥርዓትና ዲሞክራሲ ምንና ምን ናቸው?
አቻምየለህ ታምሩ
ኦነጋውያን የገዳን ሥርዓት የዲሞክራሲ ስርዓት አድርገው ያቀርቡታል። እውነት ነው ወይ? እስቲ እንመርምረው! የዴሞክራሲ መርኅ ናቸው ከሚባሉት መካከል ዋናው «የብዙሐን አገዛዝ እና የጥቂቶች መብት» ወይም በእንግሊዝኛ «Majority Rule and minority Right» የሚለው ጽንሰ ሀሳብ ነው። በዚህ የዲሞክራሲ መርኅ የገዳ ሥርዓትን ስንመዝነው ገዳ የዲሞክራሲ ፍጹም ተቃራኒ ሆኖ እናገኘዋለን። ላስረዳ!
በኦሮሞ ስነ ቃል ውስጥ Salgan Borana, sagaltamman Garba [Nine are the Borana [pure Oromo] and ninety the Garba [the assimilated] የሚል ታዋቂ  ትውፊት አለ። ምንጭ፡ 1ኛ. G.W.B Huntingford (1955). The Galla of Ethiopia. London: International African Institute፥ ገጽ 46; 2ኛ. Cerulli, E. (1933). Etiopia Occidentale (Dallo Scioa alla frontiera del Sudan): note del viaggio 1927-1928. Sindacato Italiano Arti Grafiche. Vol. I ገጽ 33]።
ይህ ትውፊት ኦሮምኛ ከሚናገረው ውስጥ «ገርባዎች ዘጠና፤ ቦረናዎች ግን ዘጠኝ ናቸው» ማለት ነው። ይህ ትውፊት ኦሮምኛ የሚናገረው ማኅበረሰብ ቦረናዎች [እውነተኛ ኦሮሞ] እና ገርባዎች [ተገዶ ማንነቱን የቀየረ] ተብሎ በሁለት እንደሚከፈል የሚገልጽ ነው።
ከአስር ኦሮምኛ ተናጋሪዎች መካከል «ዘጠኙ ገርባ [ኦሮሞ ያልሆነ] አንዱ ኦሮሞ» ነው ከሚለው የኦሮሞ ትውፊት ውስጥ ኦሮሞ የሆነው በቁጥር እጅግ ጥቂት እንደሆነና ገርባው ደግሞ በቁጥር እጅግ አብዝሐ መሆኑን መገንዘብ ይቻላል።
የገዳ ሥርዓት መርኅ ናቸው ከሚባሉት መካከል ዋናው ማንነቱን እንዲቀይር የተደረገው ወይም ገርባው እንኳን መሪ ሆኖ ሊመረጥ የገዳ ስርዓት በሚካሄድበት አካባቢ ድርሽ እንዳይል ማድረግ ነው። በገዳ ሥርዓት መሰረት መሪ ወይም አባዱላ የሚሆነው ሰው የሚሰየመው እውነተኛ ኦሮሞ ወይም ቦረና ከሆኑት ብቻ የበለጠ የገደለውና ብዙ የወረረው ነው። በቁጥር አናሳ ከሆኑት እውነተኛ ኦሮሞዎች ወይም ቦረናዎች መካከል የበለጠ የገደለና ብዙ ገርባ ያስገበረ ጦረኛ አባ ዱላ ሆኖ ይሰየማል። ይህ የገዳ ስርዓት መርኅ ነው።
በርካምበር እንዳጠናው አርሲ ውስጥ ሁለት ሶስተኛው ሕዝብ የሐድያ ነገድ አባል የሆነና ኦሮምኛ የተጫነበት ነው። ሆኖም ግን አስተዳደሩን ሙሉ በሙሉ ተቆጣጥረውት የነበሩት ጥቂቶቹ የቦረና ኦሮሞዎች ናቸው። በርካምበር እንደሚለው « አርሲ ውስጥ የኦሮሞ ጎሳ ከሆነው ከቦረና በስተቀር ከሁለት ሶስተኛ በላይ የሚቆጠሩት የሐድያ ጎሳዎች እንዲያስተዳድሩ አይፈቀድላቸውም፤ መሶሻል ስታተስም የሀድያ ጎሳ የሆኑ አርሲዎች ከኦሮሞ ጎሳ ያነሰ ቦታ ይሰጣቸው ነበር» ምንጭ፡Braukämper, U. (1980). Geschichte der Hadiya Sud-Athiopiens. A. Schröder፡ ገጽ 431።
የበርካምበት ጥናት የሚያሳየው የገዳ ሥርዓት አብዝሐነት የሆኑትን ገርባዎችን ለመግዛት በቁጥር አናሳ ከሆኑት ቦረናዎች መካከል በብዛት የገደለውና የወረረው አባ ዱላ ሆኖ በመሪነት የሚሰየምበት ሥርዓት እንደሆነ ነው። ዲሞክራሲ ግን የዚህ ተቃራኒ ነው። ዲሞክራሲ ብዝሐ ቁጥር ያላቸው ተገዥዎች ሙሉ በሙሉ ተገልለው ጥቂት ቁጥር ያላቸው ገዢዎች ብቻ እየተፈረራረቁ ተገዢዎችን ገርባና ባሪያ የሚያደርጉበት ስርዓት አይደለም። ገዳ የአንድ ኅብረተሰብ ግማሽ አካል የሆኑትን ሴቶችን ሙሉ በሙሉ እንደሚያገልል ስናስብ ደግሞ ስርዓቱ «የብዙሐን አገዛዝ እና የጥቂቶች መብት» የሚለውን ዋናውን የዲሞክራሲ መርኅ ጥርሱን እንዳረገፈው ማሰብ አይከብድም።
ባጭሩ ዲሞክራሲ «የብዙሐን አገዛዝ እና የጥቂቶች መብት»የሚከበርበት ስርዓት ነው። ገዳ ግን አብዝሐ ቁጥር ያላቸውን ገርባዎችን በገዳ ስርዓት ሙሉ በሙሉ እንዳይሳተፉ አግዶ በቁጥር አናዛ ከሆኑት እውነተኛ ኦሮሞዎች መካከል አብዝሐውን ለመግዛት በአባ ዱላነት የሚሰየሙበት ሥርዓት ነው።
ለዚህም ነው ጥቂቶቹ እውነተኛ ኦሮሞዎች አብዝሐ ቁጥር ያላቸውን ገርባዎች እንዲገዙ ተደርጎ የተዋቀረው የገዳ ስርዓት በኦነጋውያንና ደቂቆቻቸው እንደሚደሰኮረው እንኳን ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት፣ እንኳን መንግሥታዊ ሥርዓት ፖለቲካዊ ሥርዓትም አልነበረም የወረራ ሥርዓት እንጂ። ባጭሩ የገዳ ሥርዓት ምንም አይነት ዲሞክራሲያዊነት የሌለበት ፍጹም የሆነ ወታደራዊ ሥርዓት ነው።
የገዳ ሥርዓት የዲሞክራሲ ስርዓት ነው የሚል ቢኖር Salgan Borana, sagaltamman Garba የሚለውን የኦሮሞ ትውፊት መሰረት አድርጎ የገዳ ስርዓት የዴሞክራሲ መርኅ ናቸው ከሚባሉት መካከል ዋና የሆነውን «የብዙሐን አገዛዝ እና የጥቂቶች መብት» [Democracy is based on both majority rule and minority rights] እንደሚያሟላ ያስረዳ!
Filed in: Amharic