>

ለእሳቸው ቻይናን መንካት እናት ድርጅታቸው  ላይ መፍረድ ነው (ውብሸት ታዬ)

ለእሳቸው ቻይናን መንካት እናት ድርጅታቸው  ላይ መፍረድ ነው “ 

ውብሸት ታዬ
ዓለምአቀፍ የሰብዓዊ መብት ተቋማት ለአፍሪካውያኑ እየጮኹ ነው። አንድ ጮሌ ሰው ግን ድምጻቸውን አጥፍተዋል።
አፍሪካውያን በቻይና መከራቸውን እያዩ ነው። ኮቪድ 19ኝን ታሰራጫላችሁ በሚል በአፍሪካዊነታቸው ተለይተው በጸጥታ ሐይሎች ከቤታቸው እየተገፈተሩ ወደጎዳና እየተጣሉ ነው። የደቡባዊ ቻይና (Guangzhou)ሆቴሎች አፍሪካውያኑን ከክፍሎቻቸው እያስወጡ ይገኛሉ፤ ድብደባዎችና አስነዋሪ የዘረኝነት ዘለፋዎች እያደረሱባቸው እንደሆነ ዓለምዓቀፍ ሚዲያዎች እየገለጹ ነው።
የአፍሪካ ሕብረት ሊቀ መንበር የሆኑት ሙሳ ፋኪ እና በቻይና የአፍሪካ አገራት አምባሳደር በተለያየ ጊዜ የቻይናን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋንግ ዪን ስለሁኔታው ማብራርያ ጠይቀዋል። ዓለምአቀፍ የሰብዓዊ መብት ተቋማት ለአፍሪካውያኑ እየጮኹ ነው። አንድ ጮሌ ሰው ግን ድምጻቸውን አጥፍተዋል።
ለእሳቸው ቻይናን መንካት የእናት ድርጅታቸው ሰዎች ስልጣንን ሽፋን አድርገው ለዓመታት ያሸሹት የኢትዮጵያ ሕዝብ ሐብት ላይ መፍረድ ነው። የማሌሊትን ኮሙኒስታዊ አጋርነት መውጋት ነው። እሳቸው አንድ ጣታቸውን ቻይና ላይ ቢቀስሩ ወደሳቸውና ወደሕወሓት ብዙ ጣቶች እንደሚቀሰሩ ያውቁታል። ሳይባሉ ኔግሮ ተባልኩ አፍሪካውያን ሲነኩ አልታገስም ያሉት የቻይናው ጠበቃ ሳይውል ሳያድር ጭምብላቸው ተገለጠ።
በቀናነት ከጎናቸው እንቆማለን ያሉትን ሁሉ አሳፍረዋል። የሌሎቹ ጉዳይ እንኳ ወዲህ ነው። ብዙዎቹ ከሕወሓት ጋር የዘረፉ፣ የገደሉ፣ ያሠሩ፣ ኢትዮጵያውያንን በመከራ ጅራፍ ሲገርፉና ሲያስገርፉ የኖሩ ናቸው። እነሱ አገር ይያዝ ቢሉ የሚጠበቅ ነው። የኛዎቹ ማፈርያዎች(ፖለቲከኛ አይሏቸው አክቲቪስት፣ ጋዜጠኛ አይሏቸው /ሌላ/) ነገር ግን ያንገበግባል።
እንዲህ በእግረ መንገድ ሳይሆን ራሱን ችሎ የሚባልበት ስለሆነ ለጊዜው ይቆየን። በሰውየው የአመራር ልምሾነት የደረሰው ጉዳት ግን “ከጎኑ ነን” በሚሉ አጫፋሪዎች ሊካካስ አይችልም። ዶ/ር ቴዎድሮስ ስንት ብቃት ያላቸው ልጆችን ለዓለም ካበረከተች አገር በፖለቲካዊ ሰልፋቸው ታጭተው በዓለምአቀፍ መድረክ ያሳፈሩን ሰው ናቸው። ሕወሓት የነካው ሁሉ በታሪክ ውስጥ አንገት እንዳስደፋ ያኖራል።
ያለመታደል ሆኖ ከዚህ በኋላ የእሳቸው ስም ሲጠራ ኢትዮጵያም መጠራቷ አይቀርም። ኢትዮጵያውያን ለዓለም አቀፍ ቦታዎች በተወዳደሩ ቁጥር የሰውየው ስም ያጠላባቸዋል። ያሳዝናል !
“እኔ ወያኔ ነኝ!” ብለው የማይጠግቡትና አጫፋሪዎቻቸው በግድ የኢትዮጵያዊነት ካባ ሊደርቡላቸው ፈልገው የከሸፈባቸው ቴዎድሮስ(ዶ/ር)በዓለም ላይ ያደረሱት፤ በእኛ ላይ ከእነ ድርጅታቸው ለ27 ዓመታት ሲያደርሱ ከኖሩት በጣም ጥቂቱ ነው..
Filed in: Amharic