>

ሞቼ ባረፍኩት...!!! ተስፋዬ ሀይለማርያም

ሞቼ ባረፍኩት…!!!

ተስፋዬ ሀይለማርያም
.
—-
ሜጀር ጄነራል ዶክተር ተክለብርሃን ወልደአረጋይ። ይሄ ሰውዬ ይህንን ከባድ ስም እንዴት ተሸከመው? አጅሬ ከሁለት ዓመት በኋላ እንደገና ለቃለ ምልልስ ብቅ ብሏል። በዕድሜው ላይ ሁለት ዓመት ጨምሮ አሁንም አልበሰለም። አማርኛ ቋንቋ ማወቁ እንደቆጨው በአማርኛ ነግሮናል።
ስለዚህ ሰውዬ ከሁለት ዓመት በፊት ጽፌ ነበር። ሰውዬው በ40 ዓመቱ አንደኛ ክፍል ገባ፣ ከሁለት ዓመት በኋላ 12ኛ ክፍል ጨረሰና ዩኒቨርስቲ ገባ፣ አሁንም ከሁለት ዓመት በኋላ ዶክተር የሚል ማዕረግ ተሰጠው፣ እንደገና ከሁለት ዓመት በኋላ ጄነራል ሆነ፣ እንደገና ምንም ሳይቆይ የኢንሳ ዳይሬክተር ሆነ።
የዚህ ሰውዬ ታሪክ ድሮ ልጆች ሆነን ያነበብነውን “ታሪኬ ባጭሩ” የሚለውን ንባብ ያስታውሰኛል። ሰኞ ተረገዝኩ፣ ማክሰኞ ተወለድኩ፣ ሮብ ክርስትና ተነሳሁ፣ ሐሙስ እንጨት ለቀማ ሄድኩ የሚለውን።
ስሙን በእንግሊዝኛ ለመጻፍ ዳገት የሚሆንበት ይሄ ሰውዬ በረሃ እያለ ስለ ህወሃት ጠላቶች ትንታኔ ሲሰጥ እንዲህ አለ ። “ህወሃት ሶስት ጠላቶች አሏት፣ አንደኛው የአሜሪካን ኢምፔሪያሊዝም፣ ሁለተኛው የአማራው ነፍጠኛ፣ ሶስተኛው ደግሞ ወ/ሮ ብሪቱ ናቸው” አለና አረፈው።
ወ/ሮ ብሪቱ የሰውዬው እንጀራ እናት ነበሩ። ለእሱ በጣም ክፉ ሴት ስለነበሩ ለህውሃትም ጠላት ሆኑ። ሰውዬው በቂም በቀል ያደገ ሰው ነው።
በ1997 ምርጫ በኋላ ኢትዮጵያውያን በአግአዚ ሠራዊት የተጨፈጨፉ ጊዜ “ወታደሮቹ ለምን ወደ ሰማይ አልተኮሱም?” ተብሎ ሲጠየቅ “ዋይ! በሰማይ ምን ሰው አለና?” ብሎ የመለሰ ታሪከኛ ሰው ነው።
እሱና ጓደኞቹ በስተርጅና ጥይት እየቆጠሩ የሂሳብ መደመርና መቀነስ ከመማር ውጭ ከዕውቀት የተጣሉ አገርን በጨበጣ በመምራት ገደል የከተቱ ናቸው። አንድ የማውቀው ሰው ይህንንና ሌሎቹን የወያኔ ጡረተኞችን ባያቸው ቁጥር “ሞቼ ባረፍኩት” ይላቸዋል።  እውነትም ሞቼ ባረፍኩት።
Filed in: Amharic