>
5:13 pm - Wednesday April 19, 8682

‹‹እሺ ማለት ከሞትይታደጋል!›› -  (ብፁዕ አቡነ ናትናኤል)

‹‹እሺ ማለት ከሞትይታደጋል!›› – 

ብፁዕ አቡነ ናትናኤል
የሃይማኖተኛ ሰው ተግባሩ መልካምና አገር ወዳድ ዜጋን መፍጠር ነው። ሃይማኖተኛ ሰው ሀገሩንም ከራሱ አስበልጦ ይወዳል። ለዚህም የኢትዮጵያዊው አቡነ ጵጥሮስን ሰማዕትነትና ተምሳሌትነት ማስታወስ በቂ ነው። ከብሔር ጠባብነት ወጥተን ሃይማኖተኛነታችንን በአንድነትና ለሌሎች አርኣያ በመሆን ማሳየት አለብን ሲሉም ይመክራሉ።
ሰዎች ራዕይ ያላቸው መሆንም ይጠበቅባቸዋል። አይቻልም የሚል ነገር ማሰብ አያስፈልግም። ለጊዜው ገንዘብ በማጣት ድሃ ቢሆንም ሞራል የሌለው መሆን ግን የለበትም። ይልቁንም የአዕምሮ ባለጸጋ መሆኑን በሥራና በመልካም ምግባር ማሳየት ይኖርበታል። ለውጦችም በሰላም መምጣት እንደሚችሉ አስተማሪም መሆን ይገባል። ለዚህ ደግሞ አንድነት ወሳኝ ነገር ነውና የሀይማኖት አባቶችም ሆኑ ትምህርት ቤቶችና የሚመለከታቸው ሁሉ ይህንን ሊያስተምሩ ይገባል ይላሉ።
የምንደርስበትን ደረጃና የምንሆነውን ነገር የሚያውቀው እግዚአብሔር ነው። እኛ ግን የድርሻችንን ማድረግ ግዴታችን ነው። ሰው መስራት በሚቻለው ሁሉ መልካምን ማድረግ ይገባዋል። ይህ ከዚህ ይበልጣል፤ ይህ ከዚህ ያንሳል ማለትም አይገባም። ሁሉም የስላሴ ፍጥረት በእኩል ደረጃ ክብር ሊሰጠው ይገባል። በተለይ እንደ ኢትዮጵያውያን አማኞች ይህ ግዴታችን መሆኑን ማወቅም ያስፈልጋል በማለትም ተግሳፃቸውን ያስቀምጣሉ።
‹‹በማንኛውም ነገር መልካም መሆንን ተመኝ፤ የልብህን መሻት የሚያውቀው አምላክ ምላሹን ይሰጥሃል›› የሚሉት አቡነ ናትናኤል፤ በሀገር ሆኖ አንድ አለመሆንና የራስን ስራ መፍጠር አለመቻሉ በጣም እንደሚያስገርማቸው ይናገራሉ። በሰው ሀገር የምንደክመውን ያህል በአገራችን መከወን አለመቻላችንም ይቆጨኛል ባይ ናቸው።
የሰው ሀገር ሲኮን አገራችን ከአየሩ ጀምሮ ይናፍቃል። በአገራችን ስንሆን ግን በረባው ባልረባው እንጋጫለን። ስለዚህም ልብ ልንል የሚገባንና በቅጡ መተግበር ያለብን አማኞች፣ አንድነት ፈላጊዎችና አገር ወዳዶች መሆናችንን ማጎልበት ላይ ነው ሲሉ ይመክራሉ።
Filed in: Amharic