>

ለፖለቲካቸው ትርፍ ሲባል ጭዳ እየሆነ ያለው ወገኔ...!!!    (ዘመድኩን በቀለ )

ለፖለቲካቸው ትርፍ ሲባል ጭዳ እየሆነ ያለው ወገኔ…!!!

   ዘመድኩን በቀለ 

. እኔ እዚህ ከተማ ውስጥ ከሞት ጋር ነው የምራመደው፤ በየቀኑ ! ” 
ሀጫሉ ለOMN
• “ጦርነቱን የምንጀምረው አዲስአበባ ላይ ነው። ይሄን ደግሞ በቅርቡ ያዩታል”
አቶ ጌታቸው ረዳ OMN ላይ የተናገረው።
( ህወሓት)
“የግድቡን ርዕስ ሊያስቀይር የሚችል አንድ አዲስ አጀንዳ ጠብቁ። ከፈለጋችሁ እንወራራድ።”  ( ዳዊት ከበደ ህወሓት)
አዲስ ላፕቶፕ ገዝቻለሁ። (ጃዋር መሐመድ ኦነግ፣ አፌኮ)
ሃጫሉ ይቅርታ ካልጠየቅክ እርምጃ እንወስድብሃለን። ( ጃልመሮ፣ ኦነግ ሸኔ)
↵* በደቡብ ጎንደር ዞን የላይ ጋይንት ወረዳ አስተዳዳሪ የሆኑት አቶ ታረቀኝ ዮሴፍ በላይ ጋይንት ወረዳ የደሮ ቀበሌ በስራ ላይ እንዳሉ ለጊዜዉ ማንነታቸዉ ባልታወቁ ግለሰቦች በተተኮሰ ጥይት ህይወታቸው ማለፉ ታውቋል ።
አ.መ.ብ
 “የሰውን ደም የሚያፈስስ ሁሉ ደሙ ይፈስሳል፤ ሰውን በእግዚአብሔር መልክ ፈጥሮታልና!” ዘፍ 9፥6
•••
ይሄ ሁሉ ሆኖም እንኳ ሀገረ እግዚአብሔር የተባለች ኢትዮጵያ ምንም አትሆንም። ህዝበ እግዚአብሔር የተባሉ ኢትዮጵያውያንም ምንም አይሆኑም። ገዳይ ግን ይገደላል። ሴረኛም በሴራው ተጠልፎ ይወድቃል። እደግመዋለሁ። “የሰውን ደም የሚያፈስስ ሁሉ ደሙ ይፈስሳል፤ ሰውን በእግዚአብሔር መልክ ፈጥሮታልና።” ዘፍ 9፥6
•••
በሀገረ አሜሪካ የጥቁሩን ጆርጅ ፍሎይድን በአሜሪካውያኑ ፖሊሶች እጅ በግፍ መገደል ተከትሎ ዓውሮጳን በስሱ የነካ ተቃውሞ በዚያው በሀገረ አሜሪካ ተነሣ። በዚህ በዘመነ ኮሮና ህዝቡ በሽታውን ሳይፈራ በድፍረት አደባባይ ውሎ በማደር ተቃውሞውን ገለጸ።
•••
ውሎ ሲያድር ህዝባዊ ተቃውሞው ወደ ህዝባዊ ዐመጽ ከፍ ብሎ ሌላ መልክ ያዘ። እግረመንገዱንም ዐማጺው ህዝብ በጥንት ጊዜ ጥቁሮችን ይሸጡ ይለውጡ የነበሩ የባሪያ አሳዳሪ ሃውልቶችን ያፈርሱ ጀምር። ይሄ የባሪያ አሳዳሪ ሃውልት ማፍረስ ከአሜሪካ አልፎ በአውሮጳዋ እንግሊዝም መፈጸሙ ይታወሳል።
•••
ወዲያው ነው በኢትዮጵያም የዐቢይን መንግሥት ያንበረክክልናል ብለው ያሰቡ የኦሮሞና በትግራይ እንደ ህወሓት ያሉ የተቃዋሚ ኃይላት በኢትዮጵያዊው ንጉሥ በአጼ ምኒልክ ላይ ጠንካራ ዘመቻ የከፈቱት። ለዚህ ዘመቻቸውም ተመጣጣኝ ምላሽ በአንድነት ኃይሎች ተሰጥቷቸው ፀረ ሚኒልካውያን ተሸነፉ። የአንድነት ኃይሉ በሃሳብ ልዕልና አሸነፈ።
•••
ጃዋር መሐመድ በኦሮሞ ህዝቦች ዘንድ ተቀባይነቱ እየቀነሰ መምጣቱን አሳምሮ ያውቃል። በዚህ በኩል የእነ ዐቢይ አሕመዱ ብልፅግና ፓርቲ በእነ ጃዋር የመንፈስ ሠራዊት ላይ መቀዳጀቱ በግልጽ ይታይ ነበር። የእነጃዋር የገንዘብ ማሺን የሚባለው ድንቁ ደያስ በብልፅግናዎች መመታቱ እነጃዋርን አሳብደ። ቀመር ዩሱፍ ከእጃቸው ወጣ። የኢትዮጵያ ህዝብ ይፍረደኝ ማለቱ አሳበዳቸው። ጃዋርም ይሄን ተቀባይነቱን ለማስመለስ እንቅልፍ አጥቶ ሌት ተቀን ይሠራም ጀመር። “አዲስ ላፕቶፕ ገዝቻለሁ” ያለውም በዚሁ ሰሞን ነበር። ቄሮ መንገድ ዝጋ ለማለት እኮ አዲስ ላፕቶፕ አያስፈልግም ነበር።
•••
ሃጫሉ ሁንዴሳ ስለ ዐቢይ አሕመድ ንፁሕ የኦሮሞ ልጅ መሆን ተናግሯል፣ ብልጽግና ፓርቲንም ይደግፋል፣ ኦነግ ሸኔንም ይቃወማል ተብሎ በሰፊው ማስወራት የተጀመረውም ባሳለፈናቸው ጥቂት ሳምንታት ውስጥ ነበር። ይሄ እንግዲህ ሃጫሉ ራሱን እንደ ነፃነት ተጋይ ይቆጥር ስለነበር የዐቢይን መንግሥት መደገፉ በኦሮሞ ቄሮዎች ዘንድ የኦሮሞ ታጋይነቱን አሳልፎ እንደሸጠ አድርጎ በማስወራት ልጁን ስሜታዊ ለማድረግ የተዘየደ ፖለቲካዊ ሴራ መሆኑ ነው።
•••
በሌላ በኩል ሃጫሉ ሁንዴሳ በእነ ጃዋር ቡድን ብላክ ሜይል ተደርጓል። በመሃል አዲስ አበባ ውስጥ መሬትና የብረታ ብረት ቢዝነስ እንዲጀምር ከኦሮሚያ ባንክ 10 ሚልዮን ብር ብድር እንደተሰጠውም እነ ጃዋር ያውቃሉ። የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባ ኢንጅነር ታከለ ኡማ የሃጫሉ የሩቅ የሥጋ ዘመድ እንደሆኑም ያውቃሉ። እናም በሃጫሉ በኩል የሞት ድግስ መደገስ ጀመሩ። ናና ኢንተርቪ ስጥ አሉት ሃጫሉን።
•••
ግብጽ በዓባይ ጉዳይ እየተሸነፈች መጣች። ውጥረቱ ከፍ አለ። ወዲያውኑ ባልተለመደ መልኩ ጃዋር መሐመድ አሐዱ ቴሌቭዥንን ጠርቶ “ በዓባይ ወንዝ ላይ ያለውን አቋም ገለጸ። ታይቶ ነማይታወቅ ሁኔታም ፍጹም ኢትዮጵያዊ ሆኖም ቀረበ። ምስክርነቱንም የመቀሌው ዳዊት ከበደ አውራ አንባ ጋዜጣ ላይ ጃዋር የሰጠው ኢንተርቪው ነው የተባለ አርቲክል እንዲወጣ ተደረገ። ጃዋር በኢንተርቪው ህወሓትን ደግፎ፣ ስሜ መሀመድና የዐማራ ስላልሆነ እኮ ነው የምጠቃው በማለት መርዘኛ ቅስቀሳ አደረገ። እናም በዚህ ጉዳይ፣ በዓባይ ጉዳይ የዐቢይ መንግሥት ሙሉ ለሙሉ ስህተት እንደሠራም በይፋ በማወጅ የሌለ ኢትዮጵያዊ መስሎ በመታየት ነጥብ ለማስቆጠር ሞከረ።
•••
በሌላ አንቀጽ ብላክ ሜይል ተደራጊው ሃጫሉ ሁንዴሳ የኢትዮጵያው ኢንተርሃምዌይ OMN የቴሌቭዢን ጣቢያ ላይ እንዲቀርብ ተደረጎ ከትግራይ ህወሓትን፣ ዐማራውን በንጉሥ ሚኒልክ በኩል፣ ብልጽግናንና የዐብይን መንግሥት፣ እንዲሁም የጃዋር ቀንደኛ ጠላት የሆነውንና ጃዋር ካላረፍክ እገድልሃለሁ ብሎ ሞት ያወጀበትን የወለጋው ጃልመሮ የሚመራውን የኦነግ ሸኔን እንዲሰድብ፣ እንዲተች፣ እንዲያወግዝ አስደረጉት። ቀጥሎ እንዲህ ሆነ።
•••
እዚያው ኦሜኤን ስቱዲዮ የሚሠሩ ልጆች ለሃጫሉ የዛሬው ኢንተርቪህ ልክ አይደለም። ፍጹም ትክክል አይደለም። እናም እንዳይተላለፍ አስደርግ እንዳሉት ይነገራል። ሃጫሉም ነገሩን መላልሶ ሲያስብበት ከቆየ በኋላ “ ለኦኤም ኤን የሥራ ኃላፊዎች ለእነ ግርማ ጉተማ ጭምር በተደጋጋሚ ደውሎ ኢንተርቪው እንዳይተላለፍ መናገሩም፣ መማፀኑም ተስምቷል። እነ ግርማ ጉተማ ግን የዐቢይን መንግሥት የሚያንቀጠቅጥ ጮማ አጀንዳ ስላገኙ ሃጫሉን “ ዝጋ፣ አርፈህ ተቀመጥ” በማለት በድፍረት የልጁን መብት ሳያከብሩ ኢንተርቪውን ለህዝብ ይፋ አደረጉት።
•••
በሃጫሉ ኢንተርቪው የተካፋው ዐማራው ሃጫሉ ላነሣው ሃሳብ እንደተለመደው ሃሳብ አንሥቶ ሃሳብን ሰነድና ታሪክ አጣቅሶ በሰፊው ሞገተው። አቶ ሌንጮ ለታ ሳይቀሩ የሃጫሉን ሃሳብ ሞገቱ። የብልጽግና ሰዎችም ለምን በዚህ ጊዜ ሃጫሉ እንዲህ ማለት ፈለገ ብለው ትንሽ ተቆጡና ጮጋ አሉ። ህወሓት በጋዜጠኛ ዳዊት ከበደ በኩል “ የሆነ አጀንዳ ሰሞኑን ጠብቁ ” የሚል የሚያውቀውን ትንቢት መሳይ ግልጽ ነገር አስነገረች። ጌታቸው ረዳ የጃዋር ኦኤምኤን ላይ ቀርቦ ጦርነቱን እዚያው አዲስ አበባ ላይ እንጀምረዋለን ብሎ ዐወጀ። ከአሜሪካ አሉላ ሰሎሞን ለዐመጽ ህዝቡ እንዲነሣ ቋመጠ። የወለጋው ጃልመሮም “ ሃጫሉ ሁንዴሳ እኛን በመናገርህ በአስቸኳይ ይቅርታ ካልጠየክ እርምጃ እንወስድብሃለን ” በማለት ግልጽ መልእክት በፌስቡክ ገፁ ላይ ጻፈለት። ከዚህ በኋላ ሃጫሉ ያለው ዕድል የሞት ቀኑን መቁጠር ብቻ ነበር። ያለሙያው ፖለቲከኛ አድርገው ቁማር ሠሩበት።
•••
እነ ጃዋር የሃጫሉን ኢንተርቪው በኦኤም በኩል ደጋግመው ማሰማት ጀመሩ። በአንድ በኩል የአንድነት ኃይሉን ለማበሳጨት በሌላ በኩል ደግሞ የኦሮሞ፣ ቄሮ ስማው፣ ውጤቱን ጠብቅ ለማለት መሆኑ ነው። አምባሳደር ሱሌይማን ደደፎም የእነ ሃጫሉን መስመር ተከትሎ ምኒልክን መስደብ ጀመረ። ነገሩ ጦዘ።
•••
በአፍሪካ ኅብረት አደራዳሪነት የግብፅ፣ የሱዳንና የኢትዮጵያ መንግሥታት በሕዳሴው ግድብ የውኃ ሙሌት ዙሪያ ስምምነት ማድረጋቸው መነገሩ በዐቢይ መንግሥት መውደቅ ናፋቂዎች ዘንድ ሌላ ጡዘት ፈጠረ። ግብጽ ሌሊቱኑ የድል ፕሮፓጋንዳ ዘመቻዋን ከካይሮ ሆና ማሰማት ጀመረች። ከመቀሌ ህወሓት፣ ከአዲስ አበባ ከኦኤምኤን ቢሮ እነጃዋር፣ ፀረ ብአዴን የዐማራው ኃይልና የአንድነት ኃይሉ በሙሉ በዐቢይ መንግሥት ላይ በአንድ ላይ ጮኹ። ይሄ ሁሉ ሲሆን የዐቢይ መንግሥት ለሽ ብሎ እንደ እከ እንቅልፉን ተኝቶ ይለጥጥ ያንኮራፋም ነበር። ከረፈደም ቢሆን ግን አላውቅም።  የደፈረሰውም ደፍርሶ ይጠራል። ኢትዮጵያ መንፈሳዊት ረቂቅ ሃገር ናት። ይሄን ደግሞ አብረን ያየነው ነው። እናየዋለንም። ለፖለቲካቸው ትርፍ ሲባል ጭዳ ያደረጉትን የሞተውን ልጅ ነፍስ ፈጣሪ ይማር። ለቤተሰቦቹ መጽናናትንም ይስጥልን። አሜን።
•••
ሌሎቻችሁም ከመውጊያው ብረት ጋር አትጋጩ። ይብስባችኋል። የኢትዮጵያ አምላክን አታሳዝኑት። እሱ እጇን ዘወትር የምተዘረጋበትን የአሥራት፣ የተስፋ ምድሩን አይተዋትም። እንደኔ እንደ እኔ ግን ልጅ ቢሆንም፣ ከሃዲ ቢሆንም፣ ብልጣብልጥነት ቢያጠቃውም፣ የማይጨበጥ፣ የማይዳሰስ ቢሆንም በአሁን ሰዓት ከዐቢይ አሕመድ ጎን ከመሰለፍ ውጪ ሌላ አማራጭ የለም። እኔ በበኩሌ በአፉም ቢሆን የሀገሬን ስም ለሚጠራው ለአቢቹ ድጋፌን እሰጣለሁ። ለጊዜው ምርጫዬ ከበጣም መጥፎው መጥፎውን አቢቹን እመርጣለሁ። ይኸው ነው።
•••
ይህ የእኔ የዘመዴ እይታ ነው። የደፈረሰ ነገር ስክነት፣ መረጋጋት፣ ድካም፣ ረሃብ ሲመጣ መጥራቱ አይቀርም። መንግሥት OMN ን ሰከን ካደረገ፣ ትግራይ ቴሌቭዥንን ኔትወርክ ሲግናል ካጠፋበት ቀላል ይሆናል። እናም እኔም ካነሰ እያየሁ እጨምራለሁ።
•••
የሀዘን መግለጫ!!
ሻሎም!   ሰላም !
ሰኔ 23/2012 ዓም።
ከራየን ወንዝ ማዶ።
Filed in: Amharic