>

ፕ/ር አስራት እና መዐሕድ (ጋዜጠኛ ሔቨን ዮሐንስ )

ፕ/ር አስራት እና መዐሕድ

ጋዜጠኛ ሔቨን ዮሐንስ 

“ፓለቲካ ቢኖር ኖሮ…!?! ፕ/ር አስራት

እውቁ የቀዶ ህክምና ሊቁ #ፕሮፌሰር_አስራት_ወልደየስ የድርጅቱ መሪ ያደረገው መዐሕድ በምን ምክንያት ነው? የሚል ነገር መነሳቱ አይቀርም። ፕሮፌሰር አስራት ከነበራቸው ታላቅ የህክምና ግርማ ሞገስ ወደ ፓለቲካ ፓርቲ መሪነት እንደት መጡ? የሚሉ ጥያቄዎች ይኖራሉ
እርግጥ ነው #ፕሮፌሰር_አስራት_ወልዴየስ ኢሕአዴግ የሽግግር መንግስት ሲያቋቁም እሳቸው #አዲስ_አበባ_ዩኒቨርስቲን ወክለው ወንበር ተሰጥቷቸው ነበር። በጉባኤው አዳርሽ ነበሩ። አስራት ወልዴየስ የፓለቲካ ስብዕና ብሎም ገፅታ በጉልህ የታየው በዛን ጊዜ ባቀረቡት አስተያየት ነው።
አስተያየታቸው በዚያ እንደ አንድ ሰው ተመሳስለው ከተቀመጡ የፓርላማው ተወካዮች መካከል ብቻቸውን ተለይው ሀሳብ በመሰንዘራቸው ነው። ፕሮፌሰር አስራት በዚያን አዳራሽ ውስጥ #የሻቢያውን_ኢሳያስ_አፈወርቄን በማየታቸው ደስ እንዳላቸው ገለጹ። ምክንያት አንድ ላይ ሆነን ስንታይ ልዩነት እንደሌለን አስረዱ። ግን የመገንጠል ጥያቄውን በተመለከተ እዛ አዳራሽ ውስጥ የተሰበሰቡት ጉባኤተኞች #በኢትዮጵያ_ህዝብ_ስም ኤርትራንም ሆነ ሌላውን የኢትዮጵያ ክፍል ማስገንጠል እንደማይችሉ አፅንኦት ሰጥተው ተናገሩ።
#ፕሮፌሰር_አስራት ባነሱት የመቃወሚያ ሀሳብ በልዩነት ነጥረው ወጡ። ይህ የፓለቲካ ስብዕና ገናና ስም አሰጣቸው። ቀጥሎም ፕሮፌሰር አስራት #የመላው_አማራ_ህዝብ_ድርጅት/ መዐሕድ መሪ ሆነው ብቅ ሲሉ የተደበላለቀ ስሜት በሰዎች መካከል ተፈጥሯል። አንዳንድ ሰዎች ፕሮፌሰር አስራትን “ያስተማራቸው የኢትዮጵያ ህዝብ ሆኖ ሳለ እንዴት ለአማራው ሕዝብ ብቻ ብለው ትግል ጀመሩ?” እያሉ ጠየቁ። ሁለተኛው ጥያቄ ፕሮፌሰር አስራት የህክምና ሊቅ ሆነው ሳለ፤ በማያውቁበት ፓለቲካ ውስጥ ለምን ገቡ? እያሉ የሚገምቱም ነበሩ። ሶስተኛው ጥያቄ “አስራት ዘረኛ ጎሰኛ ናቸው እንዴ?” የሚሉ ሰዎች ተከስተው ነበር።
እነዚህን አንስቶ የአሜሪካ ሬዲዮ አማርኛው ክፍል ጋዜጠኛ ፕሮፈር አስራትን ቃለ መጠይቅ አድርጎቸዋል። ከጥያቄዎቹ መካከል አንዱ “እንዴት የመዐሐድ መሪ ሆነው ተመረጡ?” የሚለው ነበር። ይህንን ጥያቄ ባቀረበላቸው ወቅት አስራት እስረኛ ሆነው ታመው ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ተኝተው ነበር መልሱን የሰጡት። እርሳቸው መልስ ከሆነ ከግንቦት ወር 1983ዓ/ም በሓላ አማራ በሚባል ብሔረሰብ ላይ የተለያዩ ጥቃቶች ይሰነዘሩ ነበር። አስራት በሬዲዮው ጣቢያው ሲናገሩ የሰማሁትን ከማስታውሰው ውስጥ የሚከተለው ነው
“ገደሉ፣ ተፈናቀሉ የሚባሉ አማሮችን ሁኔታ በተደጋጋሚ እሰማለሁ። ይህ ሁኔታ እንዴት ሊከሰት ቻለ እያልኩ ማሰቤ አልቀረም። ሰው እንዴት አማራ ስለሆነ የጥቃት ኢላማ ይሆናል እያልኩ አስባለሁ። ይህንን ግድያና መፈናቀልስ ለማስቆም ምን መደረግ አለበት እያልኩ እንደ አንድ በእድሜና በትምህርት ከፍ ብሎ ከሚታይ ኢትዮጵያዊ ምን ይጠበቃል እያልኩ መፍትሄውን አስብ ነበር። ታዲያ በዚህ መሀል አንድ ቀን የሚያውቁኝ ሰዎች ስብሰባ ጠሩኝ። ግብዣቸውን ተቀብየ ወደ ስብሰባው ሄድኩ። የስብሰባው ዋና አላማ ሰዎች አማራ ናቸው እየተባለ የከፍተኛ ስቃይ ሰለባ ሆነዋል፤ ስለዚህ ይህንን እሳት እንዴት እናቁመው? ሰው አማራ በመሆኑ መገደል፣ መሰቃየት የለበትም የሚል ድምጽ ቤቱ ውስጥ በሰፊው ይንፀባረቅ ነበር እኔም ይህንን ሀሳብ እደግፍ ነበር። ሰው የየትኛውም ብሔረሰብ አባል በመሆኑ መገደልም መሰቃየትም የለበትም የሚለው ጽኑ አቅም ነበር። ከዚያም ይህን መቆሚያ ያጣውን የአማሮችን ስቃይ ለማስቆም ድርጅት አቋቁመን ድምፃችንን እናሰማ ሞትን እንግልትን ለመከላከል ሰብሰብ ብለን በተደራጀ መልኩ የዜግነት ግደተችንን እንወጣ በሚል ነበር። በወቅቱ እዚያ አዳራሽ ውስጥ አማሮች ብቻ አልነበሩ። ግድያው ያሳሰባቸው የሰው መብት ተቆርቋሪ #ኢትዮጵያውያን ነበሩ። በመጨረሻም የመላው አማራ ህዝብ ድርጅት /መዕሕድ ተመሰረተ። ልብ አድርግ ምስረታው አማራ ናችሁ ተብሎ ግፍ  የሚፈፀምባቸውን ሰዎች ለመታደግ ነው፤ ሞትን ለማስቀረት ነው፤ እሳት ለማጥፋት ነው። ከዚያም ይህን መዐሕድን የሚመራ ሰው የሚያሰባስብ ሰው ከተሰብሳቢው ውስጥ ይመረጥ ተባለ፤ ጥቆማ ተጀመረ። አንድ ሰው አስራት ወልዴየስ አለ ሁሉም ጥቆማውን ደግፎ አጨበጨበ። እኔ ደግሞ የራሴን አስተያየት ሰጠሁ። እንዲህ አይነት ድርጅቶችን ለመምራት ከእኔ የተሻሉ ሰዎች አሉ ብየ ተቃወምኩ። ነገር ግን ይህ ድርጅት ዋናው አላማው ሞትን ማስቆም ነው። አንተም በህክምና ሙያህ ስትሰራ የነበረው ሞትን፣ ስቃይን ለመከላከል ነው። እንደ ህክምና ስራህ ቁጠረው በማለት ገፋፉኝ ። እውነት ለመናገር ምርጫውን የተቀበልኩት አማራ ስለሆንኩ አይደለም፤ ሞትን ስቃይን ለመከላከል ነው።”
ይህ ከላይ የቀረበው የፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ ንግግር ከሬዲዮው ጣቢያው የወሰድኩት ነው። የፃፍኩት ቃል በቃል የሰማሁትን አይደለም የማስታውሰውን ነው። ከሞላ ጎደል የተናገሩት ከላይ በሰፈረው መልኩ ነው።
ፕሮፌሰር አስራት የቀረበላቸው ሌላኛው ጥያቄ  “እርስዎ የህክምና ሊቅ ሆነው ሳለ ወደማያውቁት ፓለቲካ ውስጥ እንዴት ገቡ የሚል ነበር?” አሁንም ከሰማሁት መልሳቸው የማስታውሰው ይህ ነው “እኔ ፓለቲካ ውስጥ አልገባሁም። ምክንያቱም ፓለቲካ በዚች አገር የለም፤ ፓለቲካ ቢኖር ኖሮ እኔ አልገባም ነበር፤ ከፓለቲከኞች እርቅ ነበር። እኔ የገባሁት ሞትን፣ ስቃይን ለመከላከል፤ ለመቃወም ነው። የእሳት አደጋን ለመከላከል ነው። የመዐሕድ መሪና አባል የሆንኩት ፓለቲካ ቢኖር ኖሮ ሰው አይገደልም፤ አይሰቃይም። ፓለቲካ ቢኖር ኖሮ በሰከነ መንፈስ ሁሉም ነገር በውይይት በመግባባት በሀሳብ ክርክር በድምፅ ብልጫና በግልፅነት ይካሄድ ነበር። ፓለቲካ ስለሌለለ ግድያና እንግልት በዛ እኔም መዕሕድን የተቀላቀልኩት ፓለቲካው እስከሚመጣ ነው። የዛን ጊዜ የመዐሕድ መሪነቱን ለፓለቲከኞች እለቃለሁ” ሲሉ አስታውሳለሁ።
ሌላው ጥያቄ “አስራት ዘረኛ ናቸው እንዴ?” የሚል ነበር። እርሳቸው ሲመልሱ በዘራቸው በቀያቸው በወንዛቸው መደራጀትን እንደሚጠሉ ተናግረው መዐሕድን የተቀላቀሉት በአማራነታቸው ሳይሆን የአማራን ግድያና እንግልት ለማስቆም ነው። በወቅቱ ልክ እንደ አማራ ለአደጋ የተጋለጠ ብሔረሰብ ቢኖር ኖሮ እርሱም በተመሳሳይ መልኩ እቆምለት ነበር የሚል መልስ ሰጥተዋል።
የፕሮፌሰር የቅርብ ሰው የሆነ፣ በትግላቸውም ጊዜ ሲያግዝ የነበረ ታላቅ ሰው መጽሐፍ ጽፎ ህወሃት እንዳይከፋፈል ስላገደችበት በቤቱ ካስቀመጠው #የአማራ_ጉዳይ  የሚለውን መጽሐፍ ሰጥቶኝ እኔም ከመጽሐፉ ቀንጨብ አድርጌ አስነበብኳችሁ!!!
ፕ/ር አስራት የከፈለልልንን መስዋዕት ልብ ብለን ወደ አንድ መጥተን ትግላቸውን ከግብ እናድርስ!!!
Filed in: Amharic