>

ይህችን ጀግና የከዳ ሕዝብ ... !!! (ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው)

ይህችን ጀግና የከዳ ሕዝብ … !!!

ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው

 

* በሥራዋና ታታሪ በትምህርቷ የማስተርስ ዲግሪዋን በተከታታይ 4 ነጥብ በማምጣት በማዕረግ የተመረቀችና ስኬታማ ሴት መሆኗና የአገዛዙ አረመኔነት ለሀገሯ የዜግነት ግዴታዋን ከመወጣት፣ ለወገን ከመታገል ወደኋላ ያላስቀራት የዘመናችን ጀግና ሴት ናት!!! 
 
አስቴር ሥዩም አበራን የማያውቅ ሰው ያለ አይመስለኝም!!! 
ከዚህም በላይ ከተከበረ ትዳሯ የምታጠባው ሕፃን ልጅ እያላት ለሀገሯ ከምታደርገው ትግል ሳያቅባት ስትታገል ነበር በወያኔ/ብአዴን ደኅንነቶች በርካቶቻችን አማራ በርካታ መራራ ዋጋ ከፍለንበት በነበረው በአግ7 ታጋይነት ተወንጅላ ተይዛ ከሀገሯ ጎንደር ወደ አዲስ አበባ ማዕከላዊ ተወስዳ ማዕከላዊ ሰቆቃ ወይም ቶርቸር ሲፈጸምባትና መራራ ዋጋ ስትከፍል የቆየችው፡፡ በዚህ ዓይነት የሰቆቃ እስር እያለችም የቤተሰቧን አባል እንድታጣ ተደርጓል!!!
አገዛዙ ለውጥ የሚል ድራማ አምጥቶ ቀድሞውንም ቢሆን መታሰር ያልነበረባቸውን እስረኞችን በመፍታት ለውጥ የመጣ አስመስሎ ሕዝብን ለማጃጃል እስረኞችን ሲፈታ ነበር አስቴር ሥዩምም (ቀለብ ሥዩምም) ተፈትታ የነበረው!!!
ልጅቷ ሕልም ያላት፣ የዜግነት ግዴታ ዕዳ እንዲኖርባት ፈጽሞ የማትፈቅድ፣ የታሪክ አደራ እንቅልፍ የሚነሣት እውነተኛና ብርቅ ድንቅ ኢትዮጵያዊት በመሆኗ ከእስር ከተፈታች በኋላም ዋጋ የከፈለችለት አግ7 ወድቆና መስመር ስቶ ስታየው እሱን ትታ ባልደራስን በመቀላቀል ትግሏን በምትቀጥልበት በዚህ ሰዓት ነበር አገዛዙ ፈጽሞ ባልዋሉበት አውሎ ፈጽሞ ማንንም ሊያሳምን በማይችል በፈጠራ ክስ ከእነ እስክንድር ጋር አስሮ ወኅኒ ያወረዳት!!!
ሕዝባችን በተለይም ልኂቃኑ ክፍል ዓይነ ሕሊናው የታወረ ስለሆነ ነው እንጅ በርካታ አሳሪና ወደኋላ የሚጎትት ገመድ እያለባት እነኝህን ገመዶች በጣጥሳ በመውጣት እየታገለች ያለችው ይህች ጀግና እኅት አርአያ በሆነችው፣ የተጋድሎ ታሪኳ ለትግል ባነሣሣው በቀሰቀሰው ነበር!!!
ምን ዋጋ አለው ታዲያ ሕዝባችን እንደሆነ እንደምታዩት ሌላ ሰው ዋጋ ከፍሎለት ነጻ እንዲወጣ ይፈልጋል እንጅ ለራሱ ነጻነት ያለ እሱ ማንም ዋጋ ከፍሎ ነጻ ሊያወጣው የማይችል መሆኑን ተረድቶ እንደ አስቴር ሁሉ በቆራጥነት ለመታገል ባለመቻሉ ነጻነት ልናገኝ አልቻልንም፣ የዚህች ጀግና መሥዋዕትነትም ለውጥ ሊያመጣ አልቻለም፣ ሕዝቡም ከመማቀቅ ሊወጣ አልቻለም!!!
የኢትዮጵያ ሕዝብ ከሀገር ውስጥ እስከ ውጭ ሀገራት ያለኸው አጥብቄ ማስጠንቀቅና ማሳሰብ የምፈልገው ነገር ቢኖር እነ አስቴርን የመሰሉ እውነተኛ ታጋዮችህን በፈጠራ ክስ አስሮ እያሰቃየ ያለውን የወያኔ ኩሊ ዐቢይ አሕመድን ደግፈህ “ዐቢይ ዐቢይ!” ስትል ፈጣሪ ፈጽሞ የማይለመንህና ምሕረት ይቅርታውንም መቸም ቢሆን የማይሰጥህ መሆኑን አውቀህ ለራስህ ስትል ይሄንን የግፍ እስራት በማውገዝ ላንተ ለራስህ ሲሉ መራራ ዋጋ እየከፈሉ ካሉት ከግፍ ሰለባዎቹ ጎን ቆመህ እያጃጃለ በነፍስ በሥጋህ እየተጫወተብህ ያለውን አገዛዝ እንድትታገል ነው!!!
የወያኔው  ዐቢይ አሕመድ በቅቤ ምላሱ ሊደብቀው ቢጥርም የደበቀው ማንነቱ በተግባሩና በተለያየ መንገድ ግልጥ በወጣበትና በሚገባ በታወቀበት በአሁኑ ሰዓት በተለይ በዳያስፖራ ያለኸው ዜጋ ተገዝተህም ይሁን በጥቅም ተደልለህ ወይም በሌላ ምክንያት ይሄንን ሁሉ ግፍ እያየህና እየሰማህ የወገኖችህን ጨፍጫፊ የወያኔን ኩሊ ዐቢይ አሕመድን ደግፈህ እየወጣህ “ዐቢይ ዐቢይ!” ብትል የንጹሐን አምላክ ፈጣሪ አይለመንህ! ፣ ልጅ አይውጣልህ! ፣ ፈጣሪ በሕይዎት ዘመንህ ለቅጽበትም ቢሆን የደስታ ቀን አያሳይህ!!!
Filed in: Amharic