>

ጭፍጨፋውን ስናስበው... (አሳዬ ደርቤ)

ጭፍጨፋውን ስናስበው…

(አሳዬ ደርቤ)

የአካባቢው አየር ሁሌም ቀፋፊ ቢሆንም የዚያን ቀኑ ቅፈት ግን ከወትሮው የተለየ ነበር፡፡ ለዚህ ምክንያቱ ደግሞ በስፍራው የነበረው መከላከያ ከመውጣቱ ጋር ተያይዞ የመነጨ ሲሆን የኦነግ ጦር የሚባለው ሃይል የመንግሥት ወታደር መሆኑን ያልተረዱት የወረዳዋ ነዋሪዎችም፣ በአካባቢው የሰፈረው መከላከያ ከዛሬ ነገ ታጣቂዎቹ ላይ እርምጃ ወስዶ ከስጋት ይታደገናል ብለው ሲያስቡ ትቷቸው የወጣበትን ምክንያት ማወቅ የማይቻል ሆኖባቸዋል፡፡
.
በሌላ መልኩ ግን የአማራ ተወላጅ የሆኑት ዜጎች ‹‹ጥቃት ይደርስብናል›› ብለው ስለሰጉ እራሳቸውን ለመጠበቅ በመንደራቸው እየተሰባሰቡ መዘጋጀትና መደራጀት ጀምረው ነበር፡፡ ይሄንንም ቅድመ ዝግጅት የተረዱት የመንግሥት ካድሬዎች ‹‹በአካባቢያችን ባንዣበበው አደጋ ዙሪያ ለመመካከር ስለምንፈልጋችሁ ወደ አዳራሽ እንድትመጡ›› በማለት ስላዘዙ፣ ሕዝቡም የተባለውን አምኖ አባወራዎች ከዘራቸውን ይዘው፣ እናቶች ጥላቸውን ዘርግተው ወደ ስብሰባው ቦታ አመሩ፡፡ አንዳንድ እመጫቶችም አራስ ልጆቻቸውን አዝለው ለመሄድ ተገድደው ነበር፡፡
.
በቁጥር 250 የሚደርሱ አማራዎችም አዳራሹ ውስጥ ታምገው ከተቀመጡ በኋላ ለስብሰባ የጠሯቸው አመራሮች ውይይቱን በመጀመር ፈንታ መረጋጋት አቅቷቸው ሲብቀጠበጡ ባዩ ጊዜ የስጋት ስሜት ይሰማቸው ያዘ፡፡ በዚህ መሃከልም ወጣ ገባ ሲሉ የነበሩት አመራሮቹ ሕዝቡ ከመድረኩ ራቅ ብሎ እንዲመጥ ካደረጉ በኋላ ተመልሰው ወደ ውጭ ወጡ፡፡
.
በዚያች ቅጽበትም ክላሽ ያቀባበሉና ጸጉራቸውን የጠቀለሉ አረመኔዎች ‹‹እንዳትንቀሳቀሱ›› እያሉ ወደ ውስጥ ዘለቁ፡፡ ይሄንንም የተመለከቱ እናቶች ማሕጸናቸውን መቆጣጠር ሲሳናቸው፣ ሕጻናቱ ደግሞ ጡት ሲጠቡበት የነበረውን አፋቸውን በድንጋጤ ከፍተው ተውት፡፡ እራሳቸውን መከላከል በማይችሉበት ሁኔታ ውስጥ የወደቁት አባወራዎችም መንቀሳቀስ ቀርቶ መተንፈስ አቅቷቸው ጭራቅ የሚመስሉትን ታጣቂዎች እየተመለከቱ አማራ ሆነው መፈጠራቸውን ይራገሙ ጀመር፡፡
.
ከዚያ በኋላ የሆነው ነገር ለሰብአዊ ፍጡር ቀርቶ ለእግዜርም ዐይን የከበደ ነበር፡፡ ወደ አዳራሹ ተከታትለው የገቡት ታጣቂዎች የጠመንጃቸውን አፈ-ሙዝ ደግነው መድረክ ላይ ከተደረደሩ በኋላ ‹‹እናንተ የተረገማችሁ ነፍጠኞች›› እያሉ ክላሻቸውን ያንፈቀፍቁት ጀመር፡፡
ለስብሰባ ተጠርተው ሰለባ መሆናቸውን የተረዱት አባወራዎችም በደመ-ነፍስ ከመቀመጫቸው እየተነሱ በበር ሾልከው ለማምለጥና ታጣቂዎቹን ለመጋፈጥ ሲያስቡ ግንባራቸው እየተቦደሰ ከምድር ይዘረሩ ያዙ፡፡
ያልታደሉት እናቶች ደግሞ የታቀፏቸውን ሕጻናት ከጥይት ለመታደግ እላያቸው ላይ ወድቀው የሚያስገድላቸው መንግሥት እንድደርስላቸው እሪታቸውን ሲያቀልጡት፣ የተወሰኑት ደግሞ እንዲህ ያለውን ግፍ ላለማየት እራሱን በሰባት ሰማይ የጋረደውን አምላክ ‹‹እባክህ አድነን›› እያሉ ይማጸኑት ጀመር፡፡
.
ታጣቂዎቹ በማያባራ ተኩሳቸው አብዛኛውን ከገደሉ በኋላ ምላጭ የሚስቡበት ጣታቸው ስለደከመ ወደ ውጭ ወጥተው በወረወሯቸው ቦንቦች አማካኝነት በጥይት ቆስለው የጣር ድምጽ ሲያሰሙ የነበሩትን አማራዎች ጨረሷቸው፡፡
ከዚያም ተመልሰው ወደ አዳራሹ ሲገቡ አረንጓዴ ቀለም ተቀብቶ የነበረው ግድግዳ ቀይ ቀለም ተቀብቶ አገኙት፡፡ ከወለሉም ላይ የሰው ደም እንደ ውሃ ታቁሮ ማየት ቻሉ፡፡ ይሄንንም ሲመለከቱ በእርካታ እየተሳሳቁ አካሉ የተቆራረጠውንና በደም የጨቀየውን አስከሬን እያገላበጡ በኪሳቸው የያዙትን ገንዘብ እየተሻሙ ከዘረፉ በኋላ ወጥተው ሊሄዱ ሲሉ የሕጻን ልጅ ለቅሶ ሰሙ፡፡ አንዱ ታጣቂም ለቅሶውን ወደሰማበት ቦታ በማምራት የእናቱን አስከሬን ተሸክሞ የሚያለቅሰውን ሕጻን አንገት በጥምብ ጫማው በመጨፍለቅ ጸጥ አሰኘው፡፡
.
ከጭፍጨፋውና ከዝርፊያው በኋላም፣ ይሄን ሁሉ ሕዝብ በአንድ አዳራሽ አጉረው ልፋታቸውን ከቀነሱላቸው አመራሮች ጋር ተቀላቅለው ‹‹ገለቶማ›› እየተባባሉ የሟቾችን ቤት ለማቃጠልና ከብቶቻቸውን አርደው ለመብላት መንቀሳቀስ ጀመሩ፡፡
Filed in: Amharic