>
5:14 pm - Friday April 20, 6328

መቃብር ጠባቂውን ብአዴንን ከጫንቃህ ሳታወርድ የኦሮሙማን ዘመቻ ለመጋፈጥ መነሳቱ ውሀ ወቀጣ ነው...!!! ( አቻምየለህ ታምሩ)

መቃብር ጠባቂውን ብአዴንን ከጫንቃህ ሳታወርድ የኦሮሙማን ዘመቻ ለመጋፈጥ መነሳቱ ውሀ ወቀጣ ነው…!!!

 አቻምየለህ ታምሩ

የምር የሚደረግ የአማራ የኅልውና ተጋድሎ ቢኖር በቅድሚያ ማድረግ ያለበት በዐቢይ አሕመድ የሚመራው የኦሮሙማ አፓርታይዳዊ አገዛዝ በጅምላ የሚፈጀውን አማራ ከኋላ የሚወጉትን፣ ከአማራ ሕዝብ ባሕል፣ ታሪክ እና እሴት የተፋቱን፣ እንጥፍጣፊ ኢትዮጵያዊነት፣ ኅሊና እና ወገናዊነት የሌላቸውን ወያኔዎች “ገ’ለን ቀብረነዋል” ያሉት አማራ መቃብሩን ፈንቅሎ እንዳይወጣ መቃብር ጠባቂ እንዲሆኑ ተደርገው የተፈጠሩ ሆዳም አማራዎች ማኅበር የሆነውን ብአዴንን ማስወገድ ነው።
አባቶቻችን ጠላትን ለመፋለም ወደ ዘመቻ ሲሄዱ በቅድሚያ የኮሶ መድኅኒት ይጠጣሉ። አባቶቻችን ለዘመቻ ሲነሱ በቅድሚያ የኮሶ መድኅኒት የሚጠጡት ጠላታቸውን በሙሉ ኃይላቸው ሳይፋለሙ ለሕመም ወይም ለድካም የሚዳርጓቸው በውጣቸው የተደበቁ በሽታ አምጪ ተህዋሲያን ካሉ እነዚያን ተውሳኮች ጠራርጎ ለማስወጣ ነው። በመሆኑም አማራ የአማራ ርጉዝ ሴት ሳትሞት ሆዷ ተቀዶ ሽሏ የሚታረድበትና ለዘመናት የተገነባ ከተማ ሙሉ በሙሉ የሚጠፋበትን በዐቢይ አሕመድ የሚመራ የኦሮሙማ አውዳሚ ዘመቻ ለመጋፈጥ ሲነሳ ከሚገኝበት የቁም መቃብር መግነዙን ቀዳዶና በጣጥሶ የተጫነበትን የመቃብር ድንጋይና አፈር ፈነቃቅሎ እንዳይወጣ መቃብር ጠባቂ ሆነው የተፈጠሩ ብአዴን የሚባሉ የአማራ በሽታ አምጪ ተህዋሲያንን በቅድሚያ ከውስጡ ጠራርጎ ማስወጣት አለበት።
ብአዴን የሚባለውን የአማራ በሽታ አምጪ ተህዋሲያን ከአማራው ውስጥ ሳያስወግዱ በዐቢይ አሕመድ የሚመራውን አውዳሚ የኦሮሙማ ዘመቻ ለመጋፈጥ መነሳት የኮሶ መድኅኒት ሳይጠጡና በውስጥ የተደበቁ የአማራ በሽታ አምጪ ተህዋሲያን ጠራርገው ሳያስወጡ ወደ ዘመቻ እንደመሄድ አይነት ጅልነት ነው።
ብአዴን ሥልጣኑን ለአማራ ሕዝብ በአፋጣኝ በሰላም ያስረክብ ዘንድ በይፋ መጠየቅ ይኖርበታል!
አብን አማራው ዛሬ ለሚገኝበት የኅልውና አደጋ የሚመጥን አመራር በተግባር ለመስጠት ዝግጁ መሆኑን መግለጡ ጥሩ ነው
 አማራውም እነሱን መከተል አለበት። ተጋድሎው የሚጠብቀውን አመራርም በተግራር ለመስጠት የኅልውና ተጋድሎ የሚያደርገውን የአማራ ሕዝብ ከጀርባ የሚወጋውና የአውዳሚው ኦሮሙማ ማኅበርተኛ የሆነው ብአዴን ሥልጣኑን ለአማራ ሕዝብ በአፋጣኝ በሰላም ያስረክብ ዘንድ በይፋ መጠየቅ ይኖርበታል። በእውነቱ ብአዴን የተሰየመበትን የግፍ ሥልጣን በፍቃዱ ከአማራው መካከል ለተውጣጡ የአገር ሽማግሌዎች አስረክቦ መሄጃውን የፈለገ እንደሆን ለአማራም ሆነ ለአገራችን ትልቅ ውለታ እንደሰራ የሚቆጠርለት ነው። ግና ብአዴን አማራ የቁም መቃብር መግነዙን ቀዳዶና በጣጥሶ የተጫነበትን የመቃብር ድንጋይና አፈር ፈነቃቅሎ እንዳይወጣ መቃብር ጠባቂ ይሆን ዘንድ ትናንት የፈጠሩትና ዛሬ ደግሞ  አማራንና አማርኛን ለማጥፋት ቆርጠው የተነሱ የነ ዐቢይ አሕመድ «አደራ» አለበትና እንጥፍጣፊ የሕዝብ ወገናዊነት ተሰምቶት፤ የአማራ ርጉዝ ሴት ሳትሞት ሆዷ ተቀዶ ሽሏ የሚታረድበትና ለዘመናት የተገነባ ከተማ ሙሉ በሙሉ የሚወድምበት የደም እንጀራ ይቅርብኝ ብሎ የከተሰየመበት የግፍ ሥልጣን ወርዶ መንበሩን ከአማራው መካከል ለተውጣጡ የአገር ሽማግሌዎች በማስረከብ ለአማራና ለኢትዮጵያ ውለታ መስራትን አያደርገውም!
Filed in: Amharic