>

አሄሄሄ... ስናውቃችሁ...?!? (ሙሉአለም ገብረመድህን)

አሄሄሄ… ስናውቃችሁ…?!?

ሙሉአለም ገብረመድህን

*…. “ኦሮሙማ ፥ ኦሮሞነት ማለት ነው። ኦሮሙማ ይውደም ማለት ኦሮሞ ይውደም እንደማለት ነው” በሚል ነው ደረቅ ሙግት ያቀረቡት። መቼም እዛ ሰፈር የፈጠራ ታሪክን እና የጥላቻ ፖለቲካን ታንጎ ማስደነስ ተክነውበታል። አሁን በምን ተአምር ነው ጃራ አባገዳና ባሮ ቱምሳ በኦሮሙማ አጀንዳ በአንድ የታሪክ ገጽ ሊጠቀሱ የሚችሉት? አጠፊና ጠፊ!
ከአማራ ጭፍጨፋ በላይ “አማራ ምን አለ?” ማለት የሚቀላቸው የጃራ አባ ገዳ ውርስ አስቀጣይና ከፖለቲካ መርህ ይልቅ የአማራ ጥላቻ ያዛመዳቸው ኦነጋዊ ኃይሎች፣ የተቆጣው ትውልድ አደባባይ ላይ ወጥቶ ባሰማው ቁጣ ውስጥ “ተደፈርን” ብለው አጀንዳ ሊያሲዙ ሲጋጋጡ እያስተዋልናቸው ነው። በእውነቱ ከገጠመን ሕዝባዊ ቀጥተኛ የህልውና አደጋ አኳያ ለዚህ መልስ መስጠት ባይገባም ብዥታን ለማጥራት፣ ሰዎቹ ሀሠት ወልዶ ማሳደግ የመቻል የድርቅና መንገዳቸውን ለማሳየት ደግመንም ቢሆን ይህን ለማለት ተገደናል።
 
“ኦሮሙማ ይውደም 
ኢትዮጵያ ትቅደም” የሚለው መፈክር ነው ጸረ-ኢትዮጵያ የሆነውን ኃይል ያስቆጣው። ይህችን ምክንያት አድርጎ ነው የተቃውሞ ሰልፉን መሠረታዊ አጀንዳ ሊገለብጥ አሰፍስፎ የመጣው።
ካመጣህውማ እነሆ  ባንተው ጅራፍ ተገረፍበት! 
*
“ኦሮሙማ ፥ ኦሮሞነት ማለት ነው። ኦሮሙማ ይውደም ማለት ኦሮሞ ይውደም እንደማለት ነው” በሚል ነው ደረቅ ሙግት ያቀረቡት። መቼም እዛ ሰፈር የፈጠራ ታሪክን እና የጥላቻ ፖለቲካን ታንጎ ማስደነስ ተክነውበታል። አሁን በምን ተአምር ነው ጃራ አባገዳና ባሮ ቱምሳ በኦሮሙማ አጀንዳ በአንድ የታሪክ ገጽ ሊጠቀሱ የሚችሉት? አጠፊና ጠፊ!
ለሁሉም ኦሮሙማ የቃሉ መነሻም ሆነ የአፈጣጠሩ ታሪካዊ ሁነት የብዝሃ ሃይማኖት ተከታይ ከሆነው የኦሮሞ ሕዝብ ጋር አብሮ የማይሄድ፤ ጠባብ ብሄረተኝነትንና አንድን ሃይማኖት መሰረት ያደረገ  ስያሜ ነው። የማንነት መጠሪያ ነው ሲሉ የየትኛው ብሎ መጠየቁ ተገቢነት አለው። ቀጥሎ የቀረበውን መልስ ላስተዋለ ጤናማ ኢትዮጵያዊ “ይውደም” መባሉን ይደግፋል።
**
“ኦሮሙማ” (Oromumma) የሚለውን ቃል የፈጠሩት አብዱል ከሪም ኢብራሂም አሚድ [ጃራ አባ ገዳ] እና የትግል አጋሩ ሳሚር ጂሳ ናቸው። ቃሉ የተመሰረተው ሁለት ቃላትን በማዳቀል ነው፤  “ኦሮሞ/Oromo” እና “ኡማ Ummah” የሚሰኙትን ቃላቶች አዳቅለው [ኦሮሙማ Oromumma] የሚሰኝ ቃል ፈጠሩ፤ “ኡማ Ummah” የአረበኛ ቃል ነው፤ የቃሉን ትርጉም “በአንድነት መቆም” በሚል የትርጉም ማዕቀፍ ላይ ሊያርፍ ይችላል። አንድነት ሲባል ደግሞ ኦሮምኛ ተናጋሪ ኢስላማዊ አንድነት መሆኑን ልብ ይሏል።
የስያሜው ታሪካዊ መሠረት ይኼው ነው❗️
በኢትዮጵያ የፖለቲካ ታሪክ ብቻ ሳይሆን በአለም የፖለቲካ ታሪክ ተጠቃሽ ሊሆን የሚችለው፣ ጠባብ ብሔርተኝነትን እና ሀይማኖትን በአንድ ላይ አጋምዶ  ወደ “ትግል” የገባው ድርጅት በአብዱል ከሪም ኢብራሂም ሐሚድ (በትግል ስሙ “ጃራ አባ ገዳ”) የተመሰረተው “እስላማዊ የኦሮሞ ነጻነት ግንባር” (Islamic Front for  Liberation of Oromo_IFLO) የተሰኘው ድርጅት ነው፡፡ በርግጥ መስራቹ የመጀመሪያው የኦነግ አባል የነበረ ቢሆንም የኦነግ ቀዳማይ መሰንጠቅ (አንጃ) ሲፈጠር የወለጋውን ተወላጅ ባሮ ቱምሳንና የባሮን የቅርብ ጓዶች (የወለጋ ተወላጆችን) ገድሎ የራሱን እስላማዊ ድርጅት መስርቷል፡፡ ዋና ማህበራዊ መሠረቱንም እስላሙማ የሚል ቀጣናዊ ስያሜ በሰጡት ሐረርጌ፣ ባሌ፣  ከፊል አርሲ አካባቢ አድርጎ ነበር።
የዚህ “ድርጅት” ግብ በሸርዒ ሕግ የምትተዳደር “እስላማዊ ኦሮሚያን (Islamic State of Oromia)” መመስረት ነበር፡፡ የዚህ ድርጅት መስራች ሼኽ አብዱል ከሪም ኢብራሂም (ጃራ አባ ገዳ) እ.አ.አ 2012 ላይ ሰነዓ [የመን] ውስጥ መሞቱ ይታወቃል። ስለዚህ የ1980s የኢትዮጵያ ISIS ለማወቅ የሐይጋይ ኤርሊክን Saudi Arabia & Ethiopia Islam, Christianity & Politics Entwined  የተሰኘውን መጽሐፍ ማንበብ ይጠቅማል። በይበልጥ The United Command of Oromo Jihad በሚል ይጠራ ስለነበረው ወታደራዊ ዕዝ መጽሐፉ ላይ የተጻፈውን ታሪክ ማንበብ ስለትናንቱ ኦሮሙማ ምንነት ይገልጥልሃል።
መቼም ጉድ ነው!
ከጃራ የተወሰደው ስያሜ “ኦሮሙማ” = ”ኦሮሞነት” በሚል ትርጉም ታጅሎ በ Oromo Studies Association_OSA በኩል ብዙ ተጽፎበታል።
በጎሳ ባህሪያታቸውና በማህበራዊ ውቅራቸው የሚጠፋፋ ህልም ያላቸውን ወለጋን Vs አርሲ/ሐረርጌ ባሌን ወደ አንድ ለማቀራረብ፤ ወለጋ Vs ከሸዋ ኦሮሞ ለማዋሃድ፣ ፍጹም የማይተዋወቁትን ሰላሌን ከጉጅ ጋር በትርክት ለማዋሃድ አያሌ ጆርናሎች ላይ ብዙ ተደክሟል። በተጋነነ የጠላት ፈጠራ ትርክት ሕዝቡን አንድ ለማድረግ ቢሞክሩም ልሂቃኑ በተናጠል የሚጠፋፋ ፍላጎት ያላቸው በመሆኑ የፖለቲካ መርህ የማያውቁ፣ በየወንዙ የሚማማሉና መልሰው የሚጠፋፉ ሆነው እዚህ ደርሰዋል። ከአንድ ዓመት በፊት የተቋቋመው Gaaddisaa Hogganttotaa Oromo (የኦሮሞ መሪዎች ጥላ) የሚባለው ስብስብ ጥላው ተገፎ የተበታተነው የሚጠፋፋ ፍላጎት ስላላቸው ነው።
ልሂቃኑ በአማራ ጥላቻ አብሮ ከመሰለፍ በስተቀር ሕዝባቸውን ማዋሃድ ተስኗቸው እንዴውም ሃይማኖታዊና አውራጃዊ ምሽጎች ሲቆፍሩ ውለው የሚያድሩ ሆነዋል።
ሰማይ ዝቅ ምድር ከፍ ቢል እንኳ ወለጋ ውስጥ ረሃብ ይከሰታል ተብሎ አይገመትም ነበር። ትርፍ አምራቹ ወለጋ አሁን ላይ ለረሃብ የተጠጋ የምግብ እጥረት አጋጥሞታል። ይህ ለማመን እንኳ የሚከብድ መረጃ ከወለጋው ተወላጅ ታምራት ነገራ አንደበት (ተራራ ኔትወርክ ላይ) ባልሰማው ለማመን እቸገር ነበር። በነገራችን ላይ ቀላል የማይባሉ የወለጋ ልሂቃን አሁን ሥልጣን ላይ ካለው ኃይል ጋር ጥልቅ ቅራኔ ውስጥ ገብተዋል። ወለጋ ክልል ካልሆነ ይህ ቅራኔ በቀላሉ ይፈታል ብሎ መገመት የሚቻል አይደለም።
የሆነው ሆኖ አሁን የኦነግ መንፈስ ወራሹ ገዥም ተቃዋሚም የሆነው ኃይል ከአማራ ጭፍጨፋ ይልቅ ዛሬም የእርሱ ጭንቀት “አማራ ምን አለ?” የሚል ሆኗል። ‘የኦሮሞ ሕዝብ በጅምላ ኦነግ ተብሎ ተፈርጇል፣ ስሙ ጠፍቷል’ የሚል መከራከሪያ ነው ያላቸው። በእውነቱ ሰፊው የኦሮሞ ሕዝብ ከኦነግና ከአመለካከቱ ወራሾች መከራን እንጅ ጸጋን እንዳላገኘ ከወለጋ አርሶ አደር በላይ ምስክር የለም።
***
መዋቅሩ በተናደበት፣ የሰው ልጆች ከሕግ ቁጥጥር ውጭ በሆኑበት በዚያ አካባቢ፣ የጉጅ ኦሮሞና በየጫካው የሚርመሰመሰው ሸኔ በየዕለቱ እርስ በርስ እንደሚጨፋጨፉ፣ የቦረና አባ ገዳዎች የሸኔው የግድያ ኢላማ ሆነው ስለመርገፋቸው፣ የጎሳው መሪ የተገደለበት ሌላኛውን አሳዶ ሲገል እንደሚውል እንኳንስ እኛ የኬኒያ ዘላኖችም ያውቃሉ። የወለጋ ቆላማ ክፍል ከአይን የተሰወረ የእርስ በርስ መበላላት ደቡብ ሱዳኖችን ያሰጋ ከጀመረ ውሎ አድሯል።
እናም ያለ አንዳች መመጻደቅ የወለጋ አርሶ አደር ድምጽ አልባ ስቃይም ያሳስበኛል።  በአፈር ገፊነቱ ከአማራ አርሶ አደር ለይቶ ለማየት ያደኩበት ባህል አይፈቅድም። እውነታው  በስሙ የተሰለፉ ኃይሎች የመከራው ምንጭ ሆነዋል።
ትርፍ አምራቹ የሰሊጥና ቡና ጌታው ወለጋ ለወትሮው አፈሩ ላይ ወድቆ ለሚነሳ ዶላር፣ ፓውንድና ዬሮ አፍሶ ይነሳ ነበር። ዛሬ መሬቱን ሟች፣ ቁስለኛና ቀለሃ ነው የሞላው። የአማራ ደም በየጥጉ የፈሰሰበት ወለጋ ጩኸታቸው ያልተሰማላቸው ምስኪን ወለጌ አርሶ አደሮችም በኦነግና በአመለካከቱ ወራሾች (ሽሜና ሸኔዎች) መከራቸው በርትቷል። አይተውት የማያውቁት የምግብ እጥረት ሁሉ ያጋጠማቸው አሉ።
እውነታው ይኼ መሆኑን የሚያውቁ አስተዋይ የአማራ ልጆች አሉና በቀጣይ በሚያሰሙት የአደባባይ ቁጣቸው በሽሜና ሸኔ ሁለት ሰይፍ ለሚያርፍበት የወለጌ አርሶ አደር ጭምር ድምጽ ይሆኑታል። እኔ በበኩሌ በኦነግ የክፋትና የጥላቻ ፖለቲካ በተጠመቁ የኦሮሞ ፖለቲካ ኃይሎች በተለየ ሁኔታ ወለጌ አርሶ አደሮችን ማሳቃየታቸውን እቃወማለሁ። ከአማራው ጭፍጨፋ ባላወዳድረውም በአኗኗራቸው ከአማራ አርሶ አደር የተለዩ አይደሉምና ስለወለጌዎች መከራም ድምጽ መሆን ያስፈልጋል ባይ ነኝ።
አጠቃላይ የአማራው ትግል ሰብዓዊነት ላይ ነውና  በገዛ ልጆቻቸው መከራ እየዘነበባቸው ያሉ ወለጌ አርሶ አደሮችን በልዩ ሁኔታ እናስባቸዋለን። አስተዋይ የኦሮሞ ልጆችም የአማራ ጭፍጨፋ ህመማችሁ ሆኖ ለመፍትኄው በጋራ እንድንቆም አደራ ማለት እወዳለሁ።
*****
በተረፈ የተቆጣው ትውልድ አደባባይ ላይ ወጥቷል። ‘መታረድ በቃን’ ነው እያለ ያለው። በቀጣይ የሚተላለፉ መልዕክቶች ማዕከላዊ ነጥባቸው አማራ በሕይወት የመኖር መብቱን ተነጥቆ፣ ዘር ተኮር ጭፍጨፋ እየተካሄደበት በመሆኑ ፍጹም የህልውና አደጋ ውስጥ ከመሆኑ አንጻር ሲቃኝ፤ በኦነጋዊው ኃይል አሁንና ቀጣይ የሰብዓዊ ውድመት ኢላማ ውስጥ ላሉ ለሌሎች የማንነት ቡድኖችም ድምጽ መሆን ይኖርብናል።  በሌላ በኩል የትግሉ አጀንዳም ሆነ አቅጣጫ ሕዝባዊ እንጅ ቡድናዊ እንዳይሆን ጥንቃቄ ሊደረግ ይገባል።
(በዚህ ጉዳይና በከሚሴ የሸፈተ መዋቅር  ዙሪያ በሰፊው እመለስበታለሁ)
እስከዛው የብዝሃ-ሃይማኖትና ሰፊ የአኗኗር ልዩነት ያለው ሰላማዊው የኦሮሞ ሕዝብ ከሽሜና ሸኔ መንታ ሰይፍ ተጠብቆ ለአማራውና ለሌላው እንደምንመኘው በነጻነትና በእኩልነት ይኑር እያልኩ፦
የጃራ አባገዳውም ሆነ የአባስ ሐጂ ገናሞው ኦሮሙማ ይውደም፤ ኢትዮጵያ ትቅደም!
Filed in: Amharic