>

“ቃል!”   (ለ“አሻግሬ”) - ጌታቸው አበራ

ቃል!”

        (ለ“አሻግሬ”)


…መጀመሪያ – ቃል ነበረ፣

ቃልም ፍጹም – ስጋ ሆነ፤

ጸጋ፣ እውነትን – ተጎናጽፎ፣

በልባችን ውስጥ አደረ…፤

 

..ቅዱስ ቃሉ የጥቅሳችን፣

እንዲህ ሆኖ እምነታችን፣

ለሃቅ አድረን ለቃል ታምነን፣

ብንከተል “ቃለ-ዐዋዲ”ን…፤

እምነት ከእኛ መች ጎደለ፤

ውርደት ሞቱ ለራሱ ነው…፣

ሕዝብን ንቆ ካታለለ። 

 

    ቃል ክቡር! ቃል ኃያል!…

    በአገሬ ምድር – በሐበሻ ባህል፤

    “ቃሌ ከሚዛነፍ – ያልኩት ከሚጠፋ፣

    ከአብራኬ የወጣው – የወለድኩት ይጥፋ፤”

    “ቃል ለምድር ለሰማይ…” ይላል በመሃላ፣

    ማተቡን ላይበጥስ – እምነቱን ላይበላ፤

 

“ቃል የእምነት ዕዳ ነው…” ይል ነበር ሎሬቱ፣

ሳትከፍለው ብትቀር – የሚያሰኝህ ከንቱ፤

ቃል ተግባር ካልሆነ ስጋ ካልለበሰ፣

ወናፍ ሆኖ ይቀራል – ባየር የነፈሰ፤

ተጸንሶ.. አድጎ..  – ቃል ካልሆነ ህይወት፣

ጨንግፎስ በቀረ – ሳይወጣ ካንደበት፤

 

   …ሕዝብን አንድ-ሁለቴ- ልታሞኘው ብትችል፣

   ሦስተኛው ዳገት ነው – ልትወጣው እማትችል።

   የመለኮት ምስጢር – ክቡር የገዘፈ፣

   “ቃል የእምነት ዕዳ ነው” – ከ”ቃል”ም ያለፈ።

 

               ጌታቸው አበራ

                                  ሚያዝያ 2013 ዓ/ም

                                   (አፕሪል 2021)

 

Filed in: Amharic