>

አብይ አህመድ ሆይ በእስክንድር ላይ የከፈትከውን ጦርነት አቁመው ለማንም አይጠቅምም … (ዘመድኩን በቀለ)

አብይ አህመድ ሆይ በእስክንድር ላይ የከፈትከውን ጦርነት አቁመው ለማንም አይጠቅምም …  

ዘመድኩን በቀለ

 

 *…. እስክንድር ላይ የሚፈጸም አደጋ ለማንም አይበጅም። ለኢትዮጵያም ለአዲስ አበባም አይጠቅማትም። እስክንድር በህወሓትም ጊዜ እስረኛ ሆኖ እናውቀዋለን። ፍፁም ሰላማዊና ምስጉን እስረኛ ነው። ሃይማኖተኛም ነው። አስክንድርን ማስወገድ ብቻ ሳይሆን የተፈለገው እስክንድር ነጋን የኦሮሞ እስረኞችና የትግሬ ህወሓት አስረኞች ናቸው የጎዱት በማስባል በቀጣይ አደገኛ የሆነ ፈንጂ በኢትዮጵያውያን መካከል ማስቀመጥ የፈለጉም ይመስለናል ነው የሚሉት።  
…በሃጫሉ ሁንዴሳ የግድያ ወንጀል ተጠርጥራ መያዟ የተነገረላት የአምቦዋ ጉብል “ተጠርጣሪት” ወይዘሪት ላምሮት ከማል በዚያው የሃጫሉን ግድያ ተከትሎ በተነሣው ብጥብጥ በአዲስ አበባና በኦሮሚያ በሰውና በንብረት ላይ ለደረሰውም ውድመት ተጠርጣሪ ተደርጋ ወደ ዘብጥያ የመጣችውን የባልደራሷን የጎንደር ዐማራ የአርማጨሆዋን አስቴር ስዩምን ካልገደልኩ ሞቼ እገኛለሁ እምቧከረዩ ብላ አስቸግራ በታራሚዎች ከፍተኛ ርብርብ አስቴር ከጥቃት ማምለጧ ገና ድሮ ወንጀል ምርመራ ሳሉ ነበር የተሰማው።
… ያ አልፎ በቅርቡ የተሰጠውን “በምርጫ ይሳተፉ” የሚለውን የፍርድ ቤቱን ውሳኔ ተከትሎ ሰሞኑንም በሴቶቹ እስር ቤት ውስጥ በአስቴር ስዩም ላይ የድብደባ ሙከራ መፈጸሙም የተሰማው በዚሁ ሰሞን ነው። ይህችን ልጅ አደጋ ሁለቴ አልፏታል። በሦስተኛው ምን ሊገጥማት እንደሚችል የሚያውቀው የዐቢይ አሕመድ መንግሥት፣ የመንግሥቱ አማካሪ ኢዜማና እና ፈጣሪ ብቻ ነው።
 ( በነገራችን ላይ አስቴር ስዩም የኢዜማ አባል የነበረችን ኢዜማ በአንድ ብሔር በጉራጌ እና በደቡቦች ብቻ መሞላቱንና ፀረ ዐማራ ድርጅት መሆኑን አይታ ወደ ባልደራስ መምጣቷን የሚናገሩ አሉ። በዚህ ነው የመንግሥቱ ሮድማፕ ሰጪዎች በስጭተውባት ዘብጥያ ያስወረወሯት የሚሉ አሉ)
… አሁን ደግሞ የመከራው ዶፍ ተራ ወደ አስክንድር ነጋ ነው የዞረው። ከላይ የወረደ ትእዛዝ ነው በተባለ መመሪያ መሠረት እስክንድር እስከአሁን ከቆየበት ዞን አሁን ወደ 80 ያህል የህወሓት ባለ ሥልጣናት ወደታሰሩበት አደገኛና ለህይወቱ ወደሚያሰጋው ዞን ያስገቡት። እዚህ ዞን ባስገቡት ማግስት ነው ኮሎኔል የማነ የሚባል እስረኛ” እስክንድርን ካልገደልኩት ሞቼ እገኛለሁ” በማለት ሲቀወጥ ያደረው። ” አንተ ነህ ህወሓት በህዝብ ዘንድ እንዲጠላ ያደረግከው፣ አንተ ነህ ለእኛ መውደቅ አንደኛው ሳንካ፣ አንተን ሳናጠፋ የቀረን እንደሁ ቱ ታያለህ ነው የሚሉት አሉ። አስክንድር ከመጣ ጀምሮ በዞኑ ውስጥ ወደሚገኘው ቤተ ጸሎት ህወሓቶቹ ከእሱ ጋር ቆመን አንጸልይም ብለዋልም ነው የሚባለው። ህወሓቶች ጸሎት ሁሉ ነው ያቆሙት።
… ተመልከቱ እስክንድር በህይወቱ ተወራርዶ ዕድሜ ዘመኑን የታገላቸውን ገዢዎች ጥሎም በእስክንድር የትግል ውጤት በብልጠት ሥልጣኑን የያዘው የህወሓት ልጅ ዐቢይ አሕመድ ” እንደ ሌሎቹ በቀላሉ ማስወገድ” ያልቻለውን እስክንድርን ወስዶ አለቆቹ ያስወግዱት ዘንድ አሳልፎ ሰጥቶታል። እስክንደር ለጊዜው በገላጋዮች ርብርብ ህይወቱ ሊተርፍ ችሏል። በቀጣይ ግን በቶሎ ከዚያ የሞት ቀጠና ካላወጡት…
… የፖሊስ የመረጃ ምንጮቼ እንደሚሉት ከሆነ” እኛ የእስክንድር ደጋፊ አይደለንም ነገር ግን ዘመዴ እስክንድር ላይ የሚፈጸም አደጋ ለማንም አይበጅም። ለኢትዮጵያም ለአዲስ አበባም አይጠቅማትም። እስክንድር በህወሓትም ጊዜ እስረኛ ሆኖ እናውቀዋለን። ፍፁም ሰላማዊና ምስጉን እስረኛ ነው። ሃይማኖተኛም ነው። አስክንድርን ማስወገድ ብቻ ሳይሆን የተፈለገው እስክንድር ነጋን የኦሮሞ እስረኞችና የትግሬ ህወሓት አስረኞች ናቸው የጎዱት በማስባል በቀጣይ አደገኛ የሆነ ፈንጂ በኢትዮጵያውያን መካከል ማስቀመጥ የፈለጉም ይመስለናል ነው የሚሉት።
ሰሚ ባይኖርም እንደ አንድ ኢትዮጵያዊ ዜጋነቴ ደግሞ ልምከር  !! 
… አሁን እንደሚታየው የትግራይ ጉዳይ መንግሥትን ዓለምአቀፍ ቅርቃር ውስጥ ከቶሃል። መውጫ መንገዱም እንጃ…። ሥርዓተ መንግሥቱ እየገደለው… እያወደመው… እየደፈረው… እያፈናቀለውም ዝም… ጭጭ ያለውንና ጭራሽ ገዳይ አስገዳዩ መሆንህን እያወቀ ወደ ክልሉ ስትመጣ እጁ እስኪላጥ ድረስ የሚያጨበጭብልህን የዐማራውንም ዝምታ እንደድል ቆጥረሃል። ዐቢቹ ሙት ዐማራውን ብዙም አትመነው። ይሄ ቅኔ የሆነ ህዝብ ለጊዜው “ጥቂት ሆዳም ዐማሮች” በሚያሳዩህ ማሽቃበጥ የምር መስሎህ የሸወድከው… ያቄልከው… ያሞኘኸውም እንዳይመስልህና በብዙ ራስህን እንዳትሸወድ። ዐማራ ማለት 27 ዓመት ሙሉ የገደለውን ወያኔን የታገሰ 3 ዓመት የገደልከውን አንተን ቢታገስህም አትደነቅ። የዐማራው ትእግስት መጨረሻ ወይ ወደ መቀሌ… ወይ ወደ ከርቸሌ ነው የሚዶልህ። ተናግሬአለሁ።
… ክቡር የብልጽግናው ፈጣሪ የዓሰሎጠሚዶኮ ዐቢይ አሕመድ ሆይ እግዚአብሔር ምስክሬ ነው እውነት እውነት እልሃለሁ ቃል ለሰማይ ለምድር በእስክንድር ነጋ ጉዳይ በህይወትህ አይተህ የማታውቀው ከባድ ኪሳራ ነው የሚደርስብህ። ኪሳራው በአንተ ብቻ ቢያበቃ መልካም ነበር። ከዚያም ያልፋል ይሻገራልም። እውነቴን ነው የምልህ በእስክንድር ጉዳይ ሃገሪቱም ትልቅ ኪሳራ ላይ ነው የምትወድቀው። በእንቅርት ላይ ጆሮ ደገፍ…
…ፍቱኝ ብሎ ያልተማጸናችሁን፣ ያላለቀሰባችሁን፣ ያልተለማመጣችሁን፣ አማላጅም ያልላከባችሁን ጨዋ አማኝና ሰለማዊ የሆነ እስክንድር ነጋን የመሰለ እስረኛ መፍታት ባትፈልጉ እንኳ ቢያንስ በእስር ቤት ውስጥ ከሕግ አግባብ ውጪ ህይወቱን እንዲያጣማ አታድርጉት። ከምር ደስስ አይልም። አዲስ አበባ የአዲስ አበባዎች ናት ያለን ሰው እንደ ኦሳማን ቢላደን ቆጥሮ ማንገላታቱም ግፍ ነው። ከዚህ ከሞት ምድብ ዞን ቀይሩኝ ብሏችኋል። ዐቢቹ ሆይ ቀይረው። ፍታኝ አላለህም። ቀይረው። ጦርነቱንም አብርድ።
… ባትሰሙኝም ምክሬ ነው።
ሻሎም !   ሰላም !
ሰኔ 2/2013 ዓም
ከራየን ወንዝ ማዶ።
()
      በሃሚድ አወል
Filed in: Amharic