>
5:13 pm - Wednesday April 19, 6682

ያብይ አሕመድ ውሃ ቅዳ ውሃ መልስ (መስፍን አረጋ )

ያብይ አሕመድ ውሃ ቅዳ ውሃ መልስ

 


  1. ወያኔ በሰሜን እዝ ላይ ለፈጸመው ጭፍጨፋ ዋናው ተጠያቂ ወያኔ ሳይሆን የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ የሆነው ዐብይ አሕመድ ነው፡፡  ተጠያቂ የሆነበት ምክኒያነት ደግሞ ወይም ከወያኔ ጋር በመመሳጠር ጭፍጨፋውን በማመቻቸቱ ወይም ደግሞ ግድግዳው ላይ የተጻፈውን ግልጽ ማስጠንቀቂያ አይቶ እንዳላየ በመሆን አስፈላጊውን ጥንቃቄ ባለመውሰዱ ነው፡፡  ግራም ነፈሰ ቀኝ በሰሜን እዝ ላይ በተፈጸመው ጭፍጨፋ አማካኝነት፣ ኦነጋዊው ዐብይ አሕመድ ወደ ኦነጋዊ ግቡ በሚያመራው ጎዳና ላይ አንድ ትልቅ ርምጃ ተራምዷል፡፡  እርምጃውም ኦነጋዊ እቅዱን ሊያኮላሹበት የሚችሉ የአማራ መኮንኖች በአማራነታቸው እየተለዩ በወያኔ መጨፍጨፋቸው ነው፡፡  
  2. ኦነጋዊው ዐብይ አሕመድ በሕግ ማስከበር ሰበብ ጦርነት ከፍቶ መቀሌን ሲቆጣጠር፣ ወደ ኦነጋዊ ግቡ በሚያመራው ጎዳና ላይ ሦስት ትላልቅ ርምጃወችን ተራምዷል፡፡  የመጀመርያው ርምጃ፣ የወያኔ ኃይል ከሞላ ጎደል ሙሉ በሙሉ ባማራ ልዩ ኃይል ላይ እንዲያርፍ በማድረግ፣ ያማራ ልዩ ኃይል ከፍተኛ መስዋእትነት እንዲከፍል ማድረጉ ነው፡፡  ሁለተኛው ርምጃ አያሌ ያማራ አርሶ አደሮችን ፈንጅ ረጋጭ በማድረግ አሰጨፈጭፎ፣ የአማራን የወታደር ምልመላ ምንጭ በተወሰነ ደረጃ ማመንመኑ ነው፡፡  ሦስተኛው ርምጃ ደግሞ ኦነግ በወያኔ ላይ የበላይነት መቀዳጀቱንና ጊዜው የኦነግ መሆኑን በተግባር ማረጋገጡ ነው፡፡  
  3. ኦነጋዊው ዐብይ አሕመድ ትግራይን ለስምንት ወራት በተቆጣጠረበት ጊዜ፣ ወደ ኦነጋዊ ግቡ በሚያመራው ጎዳና ላይ ሦስት ትላልቅ ርምጃወችን ተራምዷል፡፡  የመጀመርያው ርምጃ፣ ከነ አንቶኒ ብሊንከን ጋር በመመሳጠር ያማራ ልዩ ኃይል ያለ ኃጢያቱ በዘር ማጥፋት ወንጀል እንዲከሰስ ማድረግ ነው፡፡  ሁለተኛው ርምጃ ትግሬወች አማራን እንደ መሪር ጠላት፣ ኦሮሞን እንደ ልብ ወዳጅ እንዲያዩ ያደረገው ጥረት በከፍተኛ ደረጃ መሳካቱ ነው፡፡  ሦስተኛው ርምጃ በጦርነቱ ክፉኛ የተዳከመው ወያኔ ባጭር ጊዜ ውስጥ እንዲያንሰራራ ማስቻል ነው፣ የኦነጋውያን እቅድ ወያኔ የኦነግን የበላይነት አሚን ብሎ ተቀብሎ አማራን ሰቅዞ የሚይዝ ጎጠኛ ሎሌ እንዲሆን እንጅ እንዲጠፋ አይደለምና፡፡   
  4. ኦነጋዊው ዐብይ አሕመድ በተኩስ ማቆም ሰበብ፣ ያማራን መሬት ለወያኔ ሲያስረክብ፣ ወደ ኦነጋዊ ግቡ በሚያመራው መንገድ ላይ ሁለት ትላልቅ ርምጃወችን ተራምዷል፡፡   የመጀመርያው ርምጃ ከጦርነቱ ቁስል ማገገም የጀመረውን የአማራን ሚሊሻና ልዩ ኃይል እያስከበበና እያስቆረጠ ማስጨፍጨፉ ነው፡፡  ሁለተኛው ርምጃ የደግሞ አማራን የትግሬን ቅራኔ የበለጠ ማክረሩ ነው፡፡  
  5. ኦነጋዊው ዐብይ አሕመድ ወያኔን እንደገና ሊወጋው የተነሳ የሚያስመስልበትን የቁጩ መግለጫ ያወጣው ግን በሚከተለው ምከኒያት ነው፡፡  በዐብይ አሕመድ አመቻችነት ወያኔ አማራን ሲወር፣ የአማራ ሕዝብ በዐብይ አሕመድ መንግስት ላይ የነበረውን ዕምነት አሽቀንጥሮ ጥሎ የራሱን እድል ራሱ ለመወሰን ሆ ብሎ ተነሳ፡፡  አማራ ባማራነቱ ሆ ብሎ ከተነሳ ደግሞ ለወያኔና ለኦነግ የሸዋ አማራ ብቻ እንደሚበቃቸው ዐብይ አሕመድ አሳምሮ ያውቃል፡፡  ስለዚህም ዐብይ አሕመድ ራሱ ያስታጠቀውን ወያኔን ትጥቅ ለማስፈታት መመሪያ ቢጤ ያስቀመጠው፣ እውነትም ትጥቅ ሊያስፈታው አስቦ ሳይሆን፣  ያማራ ሕዝብ በራሱ መተማመኑን ትቶ በፌደራል መንግስት ላይ በመተማመን እንዲዘናጋና ለዳግም ጭፍጨፋ እንዲመቻች ለማደረግ ብቻና ብቻ ነው፡፡      
  6. ስለዚህም ሰፊው ያማራ ሕዝብ ሆይ፣ ወያኔና ኦነግ ጠባቸው የሰልጣን እንጅ አንተን በተመለከተ የልብ ወዳጅ መሆናቸውን አውቀህ፣ የኦነጋዊው የዐብይ አሕመድ ዲስኩር ብቸኛ ዓላማ አንተን ለማዘናጋት ብቻና ብቻ መሆኑን ተረድተህ፣ ሒሳብ ሊያወራረድብህ ያሰፈሰፈውን፣ በህልውናህ ላይ የመጣውን ወያኔን ላንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ማጥፋት የምትችለውና ማጥፋት ያለብህ አንተና አንተ ብቻ መሆነህን ተገንዝበህ፣ አሁን በያዝከው ወያኔን በራስህ ዘዴ፣ በራስህ ልጆች፣ በተባበረ ክንድህ መደቆስህን አጠናክረህ ቀጥልበት፡፡  
  7. አማራ ከኦነጋዊው ዐብይ አሕመድ አፍዘ አደንግዝ ከተላቀቀ፣ ወያኔና ኦነግ እዳቸው ገብስ ነው፡፡  

መስፍን አረጋ  ⇓

mesfin.arega@gmail.com  

Filed in: Amharic