>

ግልጽ ደብዳቤ በዐብይ አሕመድ ላይ ተስፋችሁ ላልተሟጠጠ አማሮች (መስፍን አረጋ)

ግልጽ ደብዳቤ በዐብይ አሕመድ ላይ ተስፋችሁ ላልተሟጠጠ አማሮች

 

መስፍን አረጋ


  1. ይህ ግልጽ ደብዳቤ ተደራሽነቱ ዐብይ አሕመድን በተመለከተ አሁንም ድረስ ተስፋቸው ላልተሟጠጠ አገር ወዳድ ቅን አማሮች፣ በተለይም ደግሞ ዐብይ አሕመድ ለአማራ ሕዝብ የችግር ምንጭ እንጅ የችግር መፍትሄ እንዳልነበረ፣ እንዳልሆነና መቸም ሊሆን እንደማይችል ገሃዱን ሐቅ ማየት ላልቻሉ፣ ወይም ደግሞ ዓይኔን ግንባር ያርገው በማለት ማየት ላልፈለጉ አማሮች ነው፡፡  ይልቁንም ደግሞ የአማራ ሕዝብ በሕልውናው ላይ የመጣበትን ትልቅ አደጋ መመከት የሚችለው በአማራነቱ በመደራጀት ብቻና ብቻ መሆኑን ሳይገነዘቡ፣ በኦነጋዊው ዐብይ አሕመድ ሙሉ በሙሉ ተማምነው ላታቸውን እውጭ በማሳደር እየታረዱ ወይም ደግሞ ወገናቸውን እያሳረዱ ላሉ የአማራ በጎች ነው፡፡   
  2. ዐብይ አሕመድ የጦቢያ መሪ እስከሆነ ድረስ በሱ ዘመን በአማራ ሕዝብ ላይ ለተፈጸሙ፣ እየተፈጸሙ ላሉና  ወደፊትም ለሚፈጸሙ ወንጀሎች ሁሉ በቀጥታም ሆነ በተዛዋሪ ዋናው ተጠያቂ እሱ ራሱ ነው፡፡   ስለሆነም፣ ዐብይ አሕመድ በአማራ ሕዝብ ላይ ከእስካሁን ከፈጸማቸውና ካስፈጸማቸው ወንጀሎች በላይ ምን ቢፈጽምና ቢያስፈጽም ነው፣ እናንተ አማሮች በዐብይ አሕመድ ላይ ያሳደራችሀት ተስፋ ተሟጦ የሚያልቀው?  
  3. ዐብይ አሕመድ ባለፉት ሦስት ዓመታት በአማራ ሕዝብ ላይ የፈጸመውና ያስፈጸመው ወንጀል፣ ወያኔ በሃያ ሰባት ዓመታት ባማራ ሕዝብ ላይ ከፈጸመውና ካስፈጸመው ወንጀል በቁነናም በዝግነናም አያሌ እጥፍ አይበልጥም ወይ?  የዐብይ አሕመድ የመከራ ዘመን፣ የጣልያንን የመከራ ዘመን ከሕጻን ጨዋታ የሚያስቆጥር አይደለም ወይ?  ኦሮሞ ሲያነጥሰው ጉንፋን የሚይዘው ዐበይ አሕመድ፣ ኦነግ ሸኔ የተጫወተባትን አጣየን እስካሁን ድረስ ዞር ብሎ አለማየቱ ብቻ የለየለት ፀራማራ ኦነጋዊ መሆኑን ቁልጭ አድርጎ አያሳይም ወይ?  
  4. ያማራ ፋኖ፣ ሚሊሻና ልዩ ኃይል በከፈለው ከፍተኛ መስዋዕትነት ድባቅ ተመትቶ የነበረው ወያኔ ባጭር ጊዜ ውስጥ አንሰራርቶ ያማራን ሕዝብ ፍዳ ለማስበላት የበቃው በዐብይ አሕመድ ጠቅላይ አዛዥነት፣ በብርሃኑ ጁላ ኢታማዦር ሹምነት፣ በቀንዓ ያደታ መከላከያ ሚኒስተርነት፣ በይልማ መርዳሳ አየር ኃይል አዛዥነት በሚመራው መከላከያ ውስጥ የተሰገሰጉት ፀራማራ ኦነጋውያን በሚፈጽሙት አሻጥርና ደባ አይደለም ወይ?  ዐብይ አሕመድ ሆን ብሎ መንገድ ከፍቶለት እንጅ ወያኔ ከተንቤን እመር ብሎ ሐይቅ በመድረስ የደሴን በር ለማንኳኳት እንዴት ይቻለዋል?  አፋር ክልል ላይ ወያኔን የሚያደባየው የይልማ መርዳሳ አየር ኃይል፣ አማራ ክልል ላይ ዝር የማይለው ለምንድን ነው? 
  5. የዐብይ አሕመድ የትግራይ ዘመቻ ዓላማ ወያኔን ለማጥፋት ሳይሆን፣ የአማራ ሕዝብ እንደ ሕዝብ በሚከፍለው ከፍተኛ መስዋዕትነት አማካኝነት ኦነግ በወያኔ ላይ ሙሉ የበላይነት ተቀዳጅቶ፣ ወያኔን የፀራማራ አጀንዳው አስፈጻሚ ሎሌ ለማድረግ የመሆኑ ጉልህ ሐቅ የሚያንቃችሁ መቸ ነው?  በሌላ አባባል የዐብይ አሕመድ ዓላማ ወያኔን ለኦሮሞ የማያሰጋ፣ አማራን የሚወጋ ታዛዥ አሽከር ለማድረግ መሆኑን የምትረዱት መቸ ነው? 
  6. ዐብይ አሕመድ ቢያደፋፍራት እንጅ፣ አሜሪቃ የዲፕሎማሲ ደንቦችን በመጣስ በኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ ገብታ ያማራ ልዩ ኃይል ከወልቃይትና ከራያ ይውጣ ለማለት እንዴት ትደፍራለች?  ወያኔና ኦነግ በዘር ማጥፋት ወንጀል ባልተከሰሱበት ምድር ላይ ያማራ ልዩ ኃይል ያለ ኃጢያቱ በዘር ማጥፋት ወንጀል እንዲከሰሰ ለማድረግ ዐብይ አሕመድ ካንቶኒ ብሊንከን ጋር የሚመሳጠረው ለምን ይመስላችኋል?  ያማራ ክልል አመራሮችን ሄግ ትቀርበላችሁ እያለ በማስፈራራት ሲጠራቸው አቤት፣ ሲልካቸው ወዴት የሚሉ ፍጹም አሽከሮቹ እንዲሆኑለት ለማድረግ አይደለምን?  
  7. አሜሪቃ የአማራን ልዩ ኃይል በዘር ማጥፋት ወንጀል ከመውቀሷ በፊት፣ በዐብይ አሕመድ የሚመራው የኦሮሞ ብልጽግና ፓርቲ የአማራ ልዩ ኃይል ሰሜን ሸዋ ላይ የዘር ማጥፈት ወንጀል ፈጽሟል የሚል ውንጀላ በመግለጫ መልክ መጋቢት 6 (2013) ላይ ማውጣቱን ለምን ትረሳላችሁ?  በማግስቱ ደግሞ ይሄው የኦነጋውያን የሐሰት ውንጀላ፣ የፓርላማን ደንብ በጣሰ መልኩ ባብይ አህመድ የይስሙላ ፓርላማ ውስጥ ቃል በቃል እንዲነበብና ለመላው የኦትዮጵያ ሕዝብ በቀጥታ እንዲተላለፍ መደረጉን ለምን ዘነጋችሁት?       
  8. የዐብይ አሕመድ ዋና አማካሪ፣ አዲሳባን የኦሮሞና የኦሮሞ ብቻ ለማድረግ ምሎ የተገዘተው፣ የኦነጉ መሥራች፣ ቀንደኛው ፀራማራ ዲማ ነገወ አይደለም ወይ?  ዐብይ አሕመድ ፊንፊኔ ኬኛ እያለ አዲሳባን ቢያስውብና ቢያሳምር እናንተ አማሮች የምታመሰግኑት ለምንድን ነው?  የደቡብ አፍሪቃ ነጮች ደብረዮሐንስን (Johannesburg) ከዓለም ውብ ከተሞች ተርታ ስላስቀመጧት መመስገን ነበረባቸው እንዴ?  ጣልያንስ ቢሆን ወረራውንና ምዝበራውን ለማሳለጥ ሲል ብቻ በመከራ ዘመን ለሠራቸው መንገዶች ሊመሰገን ይገባዋል እንዴ?  
  9. ዐብይ አሕመድ ጦቢያን በሚያንቆለጳጵስባቸው ባዶ ንግግሮቹም ሆነ እነ ዳንኤል ክብረት በሚጽፉለት አማራን መፎገሪያ ጽሑፎች እናንተ አማሮች ዐብይ አሕመድን አሻጋሪ የምትሉት ለምንድን ነው?  የነዚህ ንግግሮችና ጽሑፎች ብቸኛ ዓላማ የአማራን ሕዝብ ለማሻገር ሳይሆን፣ በሰበካ አስክሮ ለሃቹ ለመቅበር እንደሆነ ጠፍቷችሁ ነውን?  አፈቅርሻለሁ እያለ የሚገድል ወይም የሚያስገደል ሰው፣ ነፍሰ ገዳይ እንጅ አፍቃሪ ይባላል ወይ?
  10. ዐብይ አህመድን ማመስገን ማለት በማር የተለወሰ መርዝ የሚሰጥን ሰው ለማሩ ማመስገን ማለት አይደለም ወይ?  መርዝም ቢኖረው፣ ለማሩ ሲባል የግድ መመስገን አለበት ከተባለ ደግሞ ኢቲቪ፣ ኢሳት፣ ዜና ቲዩብ … ቀን ከሌት የሚያመሰግኑት አይበቃውም ወይ?  አሁን፣ አሁን ደግሞ ያንዳርጋቸው ጽጌ ሚዲያወችና ባልደረቦች ብቸኛው አማራጫችን ዐብይ አሕመድ ነው የሚሉበት አንዱ ምክኒያት፣ ዐብይ አሕመድ እንዳይታጠቅና ራሱን እንዳይከላከል ያደረገው የአማራ ሕዝብ በአነግና በወያኔ መጨፍጨፉ የዩቲዩብ ገበያቸውን ስላደራላቸው አይመስላችሁም ወይ?  በደቂቃ በሺ የሚቆጠሩ ተመልካቾችን የሚያፈራላቸው ጦርነት በአማራ አሸናፊነት በፍጥነት ቢቆም ጥቅማቸው ስለሚቀርባቸው፣ የጦርነቱን መቀጠል አጥብቀው የሚፈልጉት አይመስላችሁም ወይ?  መቶ ሚሊዮን ሕዝብ በሚኖርባት አገር አንድን ግለሰብ ብቸኛ አማራጭ ማለት ድፍን ጦቢያን መሳደብ አይደለም ወይ?  
  11. ድፍን የጦቢያ ሕዝብ ከልሂቅ እስከ ደቂቅ በነቂስ ሲደግፈው ጦቢያዊነትን መርጦ በጦቢያ አልጋ ላይ እድሜ ልኩን ሊተኛበት ሲችል፣ የኦነጋዊነት ዐመዱን የመረጠው ዐብይ አሕመድ፣ አብዛኛው የጦቢያ ሕዝብ ዓይንህን ላፈር ባለው በዚህ ፈታኝ ወቅት ጦቢያዊነትን ይመርጥ ይሆናል ብላችሁ እንዴት ታስባላችሁ?  የዐብይ አሕመድ ነገር ያህያ ሥጋ ባልጋ ሲሉት ባመድ መሆኑ ጠፍቷችሁ ነው ወይ?  ዐብይ አሕመድ ይሄን ያድርግ፣ ያን አያድርግ እያላችሁ አውቆ የተኛውን ኦነጋዊ ለመቀስቀስ መሞከራችሁን የምታቆሙት መቸ ነው?
  12. ዐብይ አህመድ የጭቆናን ምንነት በቅጡ ሊረዳ በማይችልበት ለጋ እድሜው “ያማራ ጨቋኞችን” ለመታገል ጫካ ገብቶ የወያኔን ጡት እየጠባ ባማራ ጥላቻ ተመርዞና ተሰቅዞ ያደገ፣ አማራዊ ናት የሚላትን ጦቢያን አፈራርሶ በሷ መቃብር ላይ የኦሮሞ አጼጌ (Oromo empire) ለመመሥረት ቆርጦ የተነሳ አክራሪ ኦነጋዊ ነው፡፡  ይልቁንም ደግሞ ዐብይ አሕመድ ማለት አክራሪ ኦነጋዊ እንዲሆን በወያኔ ተጠፍጥፎ የተሠራ የወያኔ ሥሪት ወይም ቅጥቅጥ ነው፡፡    የለየለት ፀራማራ ለመሆኑ ደግሞ ጦቢያን ከሚያሞካሽባቸው ዲስኩሮቹ ጋር ሐራምባና ቆቦ (እንጦጦና የረር) የሆኑት ኦነጋዊ ተግባሮቹ ሊስተባበሉ የማይችሉ ማረጋገጫወች ናቸው፡፡  ዐብይ አህመድ አሊ የኦነጉ ኦቦ፣ አፉና ምግባሩ ሓራምባና ቆቦ፡፡ 
  13. ዐብይ አሕመድ ካማራ መወለዱና አማራ ማግባቱ አክራሪ ፀራማራ ከመሆን አያግደውም፡፡   ሙሉ ኦሮሞ ያልሆነው ዐብይ አሕመድ የኦሮሞ አክራሪነትን ስለመረጠ፣ የእናቱ አልኦሮሞ (non-oromo) መሆን አክራሪነቱን ያከርረዋል እንጅ አያረግበውም፡፡  ያንድ ብሔር አባል አለመሆኑ የሚጠረጠር ግለሰብ የዚያ ብሔር ጽንፈኛ ከሆነ፣ በብሔር አባልነቱ ሊጠረጠር እንደማይገባው በግልጽ ለማስመስከር ሲል ያማያደርገው ድርጊት የለም፡፡  ለዚህ ደግሞ የግራኝ አሕመድ አባት የተዋህዶ ካህን ነበር የሚባለውን አፈታሪክ ጨምሮ አያሌ ተጨባጭ ምሰሌወችን መጥቀስ ይቻላል፡፡  ሂትለር ይሁዳወችን ያለ ርኅራኄ የጨፈጨፈበት አንዱ ምክኒያት የይሁዳ ደም አለበት የሚባለውን ጭምጭምታ ለማስተባበል ነበር፡፡  ጌታቸው አሰፋ በላኤአማራ የሆነበት አንዱ ምክኒያት አባቱ አማራ ቢሆኑም ‹‹ከሙሉ ትግሬወች›› በላይ አማራጠል መሆኑን ለማስመስከር ነበር፡፡  ጌታቸው ረዳ የአማራን ሕዝብ ቀን ከሌት የሚዘልፈው፣ ባማራነቱ እንደሚጠረጠር ስለሚያውቅ ጥርጣሬውን ለማጥፋት ሲል ነው፡፡ (በሌላ በኩል ግን ደብረጽዮን በትግሬነቱ ስለማይጠረጠር፣ ትግሬነቱን ለማስመስከር አማራን መሳደብ አያስፈልገውም)፡፡  አብዛኞቹ ያሜሪቃ ነጭ ልዕለኛወች (white supremacists) አንግሎ-ሳክሶኖች ከነጭ የማይቆጥሯቸው የደቡብና የምሥራቅ አውሮጳ መደዴወች ወይም ደግሞ የጥቁር ደም አላቸው ተብለው የሚጠረጠሩ ግማሽ ነጮች ናቸው፡፡  ሙሉ ጥቁር ነን ከሚሉ አሜሪቃውያን ይልቅ፣ የነጭን ዘረኝነት በጽኑ የታገሉት እነ ፍሬድሪክ ዳግላስ (Frederick Douglass)፣ ዊልያም ድቧ (W.E.B Du Bois)፣ እና ማልኮም ኤክስን (Malcolm X) የመሳሰሉ ግማሽ ጥቁሮች ነበሩ፡፡  ዐብይ አህመድ ደግሞ ግማሽ አማራ ከመሆኑ በተጨማሪ ካማራ ጋር የተጋባ በመሆኑ፣ ፀራማራ ልሁን ካለ ፀራማራነቱ ከጌታቸው አሰፋና ከጌታቸው ረዳ ቢብስ እንጅ አያንስም፡፡   
  14. ዐብይ አህመድ፣ ፀጋየ አራርሳና የመሳሰሉት ግማሽ አማራ አነጋውያን በኦሮሞነታቸው ስለሚጠረጠሩ፣ ባይነ ቁራኛ እንደሚጠበቁና እያንዳንዷ ድርጊታቸው ባጉሊ መነጽር እንደምትመረመር አሳምረው ያውቃሉ፡፡  ትንሽ ቢሳሳቱ ግዙፍ ውለታቸው መና ቀርቶ ከሃዲወች እንደሚባሉ ነጋሪ አያስፈልጋቸውም፡፡  እስከጣፈጡ ድረስ ተላምጠው የሚተፉ አገዳወች እንደሆኑ በደንብ ያውቃሉ፡፡  ስለዚህም እነዚህ ግማሽ ኦሮሞወች፣ በኦሮሞነታቸው ሊታሙ እንደማይገባቸው ለማረጋገጥ ሲሉ ብቻ ከሙሉ ኦሮሞወች የጸነፉ ጽንፈኞች መሆን አለባቸው፡፡  ከለማበት የተጋባበት፡፡   ዐብይ አሕመድ እናቴ አማርኛ የማታውቅ ኦሮሞ ናት፣ ኦሮሙማነቴን ማንም አይነጥቀኝም … እያለ ሳይጠይቁት የሚለፈልፈው ከዚህ ጭንቀቱ የተነሳ ነው፡፡  
  15. ዐብይ አህመድ ለኦነግ ዓላማ መሳካት ሲል ማናቸውንም ጭራቃዊ ድርጊት ለማድረግ ቅንጣት እንደማያቅማማ በስካሁን ድርጊቶቹ በግልጽ ቢያሳይም፣ ግማሽ ኦሮሞ በመሆኑ ብቻ ኦነጋውያን መቸም ቢሆን በሙሉ ልብ አያምኑትም፡፡  ስለዚህም ኦነጋውያን ትናንት ከሚያምኑት የበለጠ ዛሬ እንዲያምኑት ከፈለገ ትናንት ካደረገው የከፋ ዛሬ ማድረግ አለበት፡፡  ስለዚህም አማሮችን በተመለከተ የበለጠ እና የበለጠ ጭራቅ እየሆነ ይሄዳል፡፡  ባጭሩ ለመናገር ዐብይ አህመድ በማንነቱ ምክኒያት እኩይ አዟሪት (vicious circle) ውስጥ የገባ የኦነግ አውሬ ነው፡፡  ካዟሪቱ ነጻ የሚያወጣው ደግሞ ሞቱ ብቻ ነው፡፡  በኦሮሞነቱ ኦሮሞወች ሙሉ በሙሉ ሚያምኑት ለማ መገርሳ በዐብይ አሕመድ ወንበር ላይ ቢቀመጥ፣ ዐብይ አሕመድ በአማራ ላይ የሚጨክነውን ያህል እንደማይጨክን በርግጠኝነት መናገር ይቻላል፣ ምክኒያቱም ኦሮሞነቱን ለማስመስከር ዐብይ አሕመድ እስከሄደው ርቀት ድረስ መሄድ አያስፈልገውምና፡፡  ለምሳሌ ያህል ያሜሪቃ ጥቁሮች በጥቁር ፓሊስ ከመያዝ ይልቅ በነጭ ፖሊስ መያዝን የሚመርጡት በዚሁ ምክኒያት ነው፡፡  
  16. የዐብይ አሕመድ የአማራ ጥላቻ እጅግ የመረረ ከመሆኑ የተነሳ፣ ዐማራ ተጠናክሮ ከሚያይ ይልቅ ወያኔ አዲሳባን ተቆጣጥሮ በስቅላት ቢቀጣው ይመርጣል፡፡  ሰባተኛው ንጉሥ ዐብይ አሕመድ የስልጣን ጥመኛ ቢሆንም፣ የስልጣን ጥሙ ግን ከአማራ ጥላቸው አይበልጥበትም፡፡  አለበለዚያማ ለዐብይ አህመድ ስልጣን ይጠቅም የነበረው በነቂስ ደግፎት የነበረውን አማራን ይበልጥ አጠናክሮ፣ ግማሽ አማራ በመሆኑ ምክኒያት የሚጠራጠሩትን ኦነጋውያን እንዲቆጣጠርለት ማድረግ ነበር፡፡  
  17. ሰካራም ባል ሚስቱን አመስግኖ እንደማይጠግብ የታወቀ ነው፡፡  ባገኘው አጋጣሚ ሁሉ የሚያወራው ስለሷ መልካምነት ነው፡፡  ይህን የሚያደርገው ደግሞ በሰካራምነቱ ሳቢያ በሚስቱ ላይ የሚደርሰው ዘርፈብዙ ጉስቁልና ሕሊናውን ስለሚሸነቁጠው ነው፡፡ እንዲህ ዓይነቱን ባሕሪ የስነልቦና ሰወች ማካካስ (compensation) ይሉታል፡፡  የዐብይ አህመድ ድርጊቶች ሁሉም የሚጠቁሙት ግለሰቡ በሥርሰደድ (chronic) የማካካስ በሽታ በጽኑ የታመመ የስነልቦና በሽተኛ ሳይሆን እንደማይቀር ነው፡፡  ስለ ሰላምና ስለ ፍቅር አውርቶ የማይታክተው ዐብይ አህመድ፣ የሰላምና የፍቅር ቀንደኛ ጠላት ስለሆነ ይሆናል፡፡  ባገኘው አጋጣሚ ሁሉ መግደል መሸነፍ ነው የሚለው ዐብይ አህመድ፣  ማሸነፍ መግደል ነው በሚል መርሕ የሚመራ ደም ጠማሽ ስለሆነ ይሆናል፡፡  አባቱን ስማችውን ሳይጠቅስ እናቱን አለመጥን የሚያሞግሰው ዐብይ አህመድ በናቱ ምንነት አለመጥን ስለሚያፍር ይሆናል፡፡  እስከቅርብ ጊዜ ድረስ የብቸነት ኑሮ ትገፋ የነበረቸውን እማወራ (single mother) ሚስቱን አለመጠን የሚክባት ደግሞ በጓዳ የሚያዋርዳት የቤት ቀጋ የውጭ አልጋ ስለሆነ ይሆናል፡፡ 
  18. የጎሳ ፖለቲካ ተወልዶ፣ አድጎ፣ ተመንድጓል እንጅ፣ ከያኒ ቴድሮስ ካሳሁን እንዳለው አርጅቶ አልሞተም፡፡  የስልጣን መጨበጫና የሐብት መሟጠጫ እስከሆነ ድረስ ደግሞ ይበልጥና ይበልጥ ይመነደጋል፣ አቀንቃኞቹም ይበልጥና ይበልጥ አክራሪወች ይሆናሉ፡፡  የጎሳ ፖለቲካን የሚገድለው፣ የጎሳ ፖለቲካ ከሚጠቅማቸው በላይ እንደሚጎዳቸው አቀንቃኞቹ ወያኔወችና ኦነጋውያን በግልጽ ከተገነዘቡ ብቻና ብቻ ነው፡፡  ይህ የሚሆነው ደግሞ ጦቢያዊነት ማተቡ የሆነው የአማራ ሕዝብ ባማራነቱ ተደራጅቶና ተጠናክሮ ለጎጠኞች ቀይ መስመር ሲያቀመጥና መስመሩን ባለፉ ቁጥር፣ ባለፉበት መጠን ሊቀጣቸው ሲችል ብቻ ነው፡፡  ጎጠኞች ራሳቸውን እያጠናከሩ፣ የአማራን መጠናከር እንደ ጦር የሚፈሩበትም ምክኒያት ይሄውና ይሄው ብቻ ነው፡፡  ዐብይ አሕመድም ያማራ ብሔርተኝነት የጦቢያ ስጋት ነው ያለው፣ የኦነጋውያንና የወያኔወች ስጋት ነው ለማለት ነው፡፡        
  19. ስለዚህም የአማራ ሕዝብ በአማራነቱ ተደራጅቶና ተጠናክሮ የጎጠኞች የበላይ መሆን፣ ለጦቢያ ሕልውና አስፈላጊም በቂም  (necessary and sufficient) ነው፡፡  በመሆኑም፣ በአማራ ሕልውና ላይ መምጣት ማለት በጦቢያ ሕልውና ላይ መምጣት ማለት ነው፡፡  ጣልያን ያደረገው፣ ወያኔና ኦነግ እያደረጉት ያለው ይሄንኑ ነው፡፡  
  20. የአማራ ሕዘብ ከዐብይ አሕመድ አፍዝ አደንግዝ ከተላቀቀ፣ ወያኔና ኦነግ እዳቸው ገብስ ነው፡፡  

 

መስፍን አረጋ

mesfin.arega@gmail.com

Filed in: Amharic