>
5:13 pm - Monday April 20, 9372

የአብይ መንግስት የሱዳኑ ወረራ ላይ በህወሀት ልክ ቁጣ እና ቁጭት ያላሳየው ለምን ይሆን ...??? ጎዳና ያእቆብ

የአብይ መንግስት የሱዳኑ ወረራ ላይ በህወሀት ልክ ቁጣ እና ቁጭት ያላሳየው ለምን ይሆን …???
ጎዳና ያእቆብ

Self reliance (እራስን መቻል) በጣም የሚማርክ እሳቤ ሆኖ ሳለ አምባገነኖች ሁሌም ይህንን እሳቤ የሚጠቀሙበት እኔ በምፈፅማቸው በሰብአዊነት: በዲሞክራሲያዊ እና በማህበራዊ መብቶች (civic) መብቶች ጥሰት አገር ላይ በሚመጣው ማእቀብ እና መገለል ለሚመጣ ሀገራዊ ሰቆቃ: የኢኮኖሚ ድቀት: ረሀብ: እና መሰል ችግሮችን ሕዝብ እንደ ሕዝብ ይቻለው የኔም ዙፋን ይፅና የስልጣን ዘመኔም ይራዘም ማለታቸው እንደሆነ እጅግ ብዙ ማሳያዎች አሉ:: የሰሜን ኮሪያው እና የኤርትራው ኢሳያስ አፈወርቂም አዘውትረው ከሚጠቀሙባቸው ቃላት መካከል <<self reliance >> ዋናዎቹ ናቸው::
ቶማስ ሳንካራ <<የሚያበሏችሁ ይገዟችኃል>> ሲል ምናልባት የዘነጋው ነገር የሚገዙን በረሀብ እንደሚገድሉን ነው:: ረሀብና ጉስቁልናን እንደ ጦር መሳሪያ መጥቀማቸው ነው:: ምርጫው እየገደለ ከሚገዛ እና አብልቶ በሚገዛ መካከል መሆኑ የአፍሪካ ታሪካዊ ውድቀት ነው::
አምባገነኖች ስልጣናቸውን ለማፅናት የማይጠቀሙበት ነገር የለምና ኢትዮጵያዊያን ለሀገር ያለንን ፍቅር በመጠቀም ጣልቃ ገቡብን:: ሊገዙን ነው:: ሊያዋርዱን ነው:: በሚል ፕሮፖጋንዳ እንደእንዝርት ሊያሾሩን ሲሞክሩ ማየት ፈገግ አሰኝቶኛል:: ኤርትራን በኢትዮጵያ ፓለቲካ ውስጥ ሲያስገባ ጣልቃ ገብነት የክብር ጉዳይ እንዳልሆነበትና ለቅስቀሳ ብቻ እንደሚጠቀምበት ያስረዳናል:: እኔም እንዲህ አይነቱ ቅስቀሳ እጅ እጅ ስለሚል አልበላውም እላለሁ::
ሱዳን የኢትዮጵያን መሬት ወሮና ይዞ እያለ በትግራይ በኩል ወልቃይት በህግ ምእራብ ትግራይ ነችና  ከአማራ ተነጥቃ ይመለስልኝ ሲል በአማራው በኩል ደግሞ በታሪክ ወልቃይት የአማራ ነበረች አሁን ደግሞ በመራራ ትግላችን የዛሬ ዘጠኝ ወር መልሰን ይዘናልና በእጃችን ወደፊትም ትቆያለች የሚል የወንድማማቾችን የእርስ በርስ ጦርነት እየተካሄደ ይገኛል:: የሱዳኑ ወረራ ላይ በዚህ ልክ ቁጣ እና ቁጭት ለምን አላየንም የሚለው የዘውር ጥያቄዬ ነው::
የአማራው ትግል የኢትዮጵያ ህልውና ትግል ነው ተብሎ ከታመነ ስለምን ከንግግር ባለፈ ለአማራ ክልል የሎጅስቲክና የሰው ሀይል ድጋፍ አልተሰጠም የሚለውም የዘውትር ጥያቄዬ ነው::
እውነታው ማእከላዊ መንግስቱ ከህዋሃትና ኦነግ በላይ የተደራጀና እስከ አፍንጫው የታጠቀ አማራ ያስፈራዋል:: ከጠላትነት አንፃር በጠላትነት የሚያየው ጨቋኝ ትምክህተኛ ምናምን የሚለውን አማራ እንጂ በስልጣን ብቻ ፀብ ያላቸውን ህዋሃትን ወይም አቅፎ ደግፎ እና አስታጥቆ ያመጣውን ኦነግን አይደለም::
ስለዚህም ማእከላዊ መንግስቱ አማራን አያስታጥቀውም:: አያደራጀውም:: የኢትዮጵያ የህልውና አደጋ ለመቀልበስ በተባለው ኦፕሬሽን ላይም ትርጉም ያለው የሰው ሀይል ድጋፍ አያደርግም::
ነገ ከነገ ወዲያም አማራውን ክዶ ለድርድር እንደሚቀመጥ ምንም ጥርጥር የለኝም:: የወልቃይት ጉዳይንም በህገ መንግስቱ መሰረት ለመፍታት ስለሚነሳ ህገ መንግስታዊው የወሰን ውዝግብ የአፈታት መንገዶች ታሪክን ስለማይጨምር አማራውን የሚክድ የሚጎዳ ነው የሚሆነው:: በብሔር ብሔረሰብ እና ሕዝቦች (በአንቀፅ 39 ላይ የተሰጠው ትርጉም አንድ ስለሆነና ልዩነቱ በግልፅ ያልተለየ ነው) አማራውን ጠላት ጨቋኝ ሲባል ለ30 አመታት ሲሰበክ የኖረ ነውና ውግናው የሚሆነው ከአማራው ጋር አይሆንም::
ስለዚህም ነው ጦርነቱ በተነሳ ማግስት አማራው ያገኘው ድል የሞራል ድል ነው:: ለመደራጀት እና ሊመጣ ላለው ታላቅ ትግል አቅም የሚሆን ነው እንጂ ሌላ አይደለም:: በክህደት የሚጠናቀቅ ነው ብዬ የፃፍኩት:: ለዚህም ነው የፌደራል መንግስቱ መቀሌን ለቅቄ ወጥቻለሁ የተናጥል የተኩስ አቁምም አውጄአለሁ ቢልም አሁን ያለው ጦርነት ጦርነቱ የዛሬ 10 ወር የጀመረ እንጂ አዲስ ጦርነት አይደለም የሚለው::
አማራ ህልውናውን ለማስጠበቅ ሆ! ብሎ መነሳቱ የሚገባ ትክክል እና እንደውም የዘገየ ነው ባይ ነኝ:: ምንም እንኳን ከአብይ አህመድ ጋር እያየሁት ያለው ያልተቀደሰ ጋብቻ በርቀት እና በጥንቃቄ ሂደቱን እንድከታተለው አድርጎኛል:: የአማራውን ማኅበረሰብ cause በሙሉ ልቤ እደግፋለሁ:: ነገር አብይ አህመድና አገኘሁ ተሻገርን አሾልኮ አስገብቶ አይ እነሱን መቃወም የአማራውን ማኅበረሰብ ትግል መቃወም ነው መባል ሲጀምር ቀይ መስመሬ ታልፏል:: ተጥሷል::
ግፈኛው ብአዴንን በምንም መንገድ ልደግፍ አልችልም:: አስቴር (ቀለብ) ስዩምን አስሮ አሰቃይቶ ለህመም የዳረጋትና ወንድ ልጅን የሚይስለቅሰው የአብይ አህመድን መንግስት በዝምታም ቢሆን ለመደገፍ አይቻለኝም:: በሺዎች ያስረው የሚሰቃዩ እለት ከእለት በኦሮሚያ ለሚገደሉት priorityያቸው አብይ አህመድ እና ሽመልስ አብዲሳ ናቸው:: ነገሮች ቅደም ተከተል እንዳላቸው አምናለሁ በዛም መሰረት ቅደም ተከተሌ እንደሚከተለው ነው:: የኢህአዲግ ግንባር እና አጋራት በሙሉ ኢትዮጵያን የሚያፈርሱ የሀገር ጠላቶች ናቸውና በሙሉ መጥፋት አለባቸው:: ኢትዮጵያን የሚያድነው ያ እና ያ ብቻ ነው::
በጎጥኛነት እሳቤ ትነሳስቼ የትውልድ ቦታዬ የሆነችውን ነጌሌ ቦረናን ኦነግ ተቆጣጠረውና ከአጥፊው አብይ አህመድ ጋር ተሰልፈን አብይን አሽሞንሙነን እንደግፈው አብይ ያማልዳል እንበለው አልልም:: በኔ በኩል ነጌሌ ቦረና በኦነጉ አብይ አህመድ ስር ነበረች:: አሁን ደግሞ ሸኔ የሚል የዳቦ ስም በተሰጠውና ከአብይ አህመድ ጋር አንዲት ነጥብ የአስተሳሰብ ልዩነት በሌለው ኦነግ ስር ነች:: ትላንትም ሕዝብ ሰቆቃ ውስጥ ነበር:: አሁንም እንደዛው::
በስም እንጂ በግብር ልዩነት በሌላቸው የሰይጣን ማህበራት መካከል ምን የምትባለ ሰይጣን ነህ ብዬ አልዳክም::  ያው ናቸው! ከአንድ ጨርቅ የተቀደዱ ናቸው!!
ተጣብቀው የተወለዱና በሻቢያ ማህፀን ያደጉ ኢትዮጵያ ጠል ሰይጣኖች ናችው::
ትላንት አብይ አህመድ ኦነግ ጋር ጥምረት ፈጥረው ነበር::
የሻሸመኔ ከተማ ስትነድ ሽመልስ አብዲሳ ከንቲባውን አርፈህ ተኛ ሲለው ነበር:: ዛሬ ደግሞ ህዋሃት ከኦነግ ጋር ጥምረት ፈጠሩ ስባል ስልጣንህን አንነካብህ ብለው ዋስትና ቢሰጠው ኖሮ አብይ አህመድም አማራን ልማጥፋት ከህዋሃት ጋር ጥምረት ይፈጥር ነበረ:: አሁንም ጥምረቱ የለውም የሚያሰኘኝ አንድ እና ብቸኛ ነገር ለስልጣኑ ያለው ፍቅር ብቻ እንጂ ሌላ አይደለም::
Filed in: Amharic