>

ጦርነት እልቂቱ ፣ ርሀብ ጠኔው ፣ በሽታው ወረርሽኙ ... ሁሉም የፖለቲከኞቻችን የሴራ ድምር ውጤት ነው...!!! (ዘመድኩን በቀለ)

ጦርነት እልቂቱ ፣ ርሀብ ጠኔው ፣ በሽታው ወረርሽኙ … ሁሉም የፖለቲከኞቻችን የሴራ ድምር ውጤት ነው…!!!
ዘመድኩን በቀለ

… እርስበርስ ጦርነት ባለበት ሃገር ይህን መሰል ራብ የሚጠበቅ ነው። እንዲያውም ከመጪው መስከረም እና ጥቅምት በኋላ ይብሳል። 24/7 ጦርነት ላይ ያለ ህዝብ ባይራብ ባይጠማም ነው የሚደንቅ የነበረው። እንዳየነው ዘንድሮ ገበሬ አላረሰም። የምን ማረስ እንዲያውም ገበሬው ራሱ ዘምቷል። በዚያም ሞቷል፣ ቆስሏል። ተማርኳልም። ስለዚህ እሸት ከጓሮ፣ እህል በጎተራ በገፍ መሰብሰቡ የማይታሰብ ነው።
… አማሪካ ለምስኪኖቹ የትግራይ ችግረኞች የምትረዳው ብስኩት ሳይቀር በህወሓት ተሰርቋል። ለህጻናት ኃይል የሚሰጠውን ምግብ የሂዊ ኮሎኔል እየበላ ጭምር ነው የሚያዋጋው የሚዋጋውም። ህፃናት ያለ አባት፣ ያለ ወንድም ቀርተዋል። እናት እህት በሙሉ ዘመቻ ላይ ናቸው። ሽማግሌ ያለጧሪ፣ ያለ ቀባሪ በባዶ ቤት በራብ እየረገፈ ነው። 100 ለማይሞሉ ወመኔ የወያኔ ጋንግስተሮች ሲባል 5 ሚልዮን ትግሬ እንደ ቅጠል እየረገፈ ነው። ስልክ፣ መብራት፣ መድኃኒት ህክምና ብሎ ነገር የለም። ነገርየው ከምታስቡት፣ ከምትገምቱትም በላይ ዘግናኝ ነው።  በትግራይ በኩል በገጠሩ በሴፍቲ ኔት ይኖር የነበረው ህዝብ አሁን ምን ዓይነት ስቃይ ላይ እንዳለ ለማወቅ አይቻልም። የትግሬ አክቲቪስት እዚህ ገባን፣ እዚያ ወጣን ፉከራ ላይ ስለሆነ ስለ ራብ ሞቱ አያወራም።
… የዐቢይ አሕመድ መንግሥት ደግሞ ጦርነቱ በቶሎ አልቆ ከዐማራ ክልል እንዲወጣ አይፈልግም። ዐማራም እንደ ትግሬ በደንብ መድቀቅ አለበት። ሁለቱ የሚያሰጉት ነገዶች በደንብ ተቀጣቅጠው ወደ ኋላ ረጅም ዘመናትን ካልተመለሱ በቀር ለአዲሱ የኦሮሙማ መንግሥት ሳንካ ነው የሚፈጠርበት። ስለዚህ እንዲያና እንዲህ እየተባለ “የለገመ መርፌ ቅቤ እንደማይወጋው ሁሉ የለገመ መከላከያ ወደ ዐማራ ክልል በመላክ ጦርነቱ በቶሎ እንዳይቋጭ፣ እዚያው በዚያው እየተርመጠመጡ፣ በተያዘ፣ ተለቀቀ፣ ፕሮፓጋንዳም ህዝቡን እያደነዘዙ እምሽክ እያደራረጉ ያዳቁሷቸዋል። የትግሬው የፖለቲካ መሪዎች ደግሞ ለዚህ ሁሉ ስቃይ የዳረገኝ፣ ፏ ብዬ እኖርበት ከነበረው የተደላደለ ኑሮ ወደ ቀበሮ ጉድጓድ የመለሰኝ የዐማራው የፖለቲካ ኃይል ነው ብሎ ስለሚያምን “እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል” በሚል ሂሳብ የዐማራ የሆነውን በሙሉ እያወደመ መጓዝን መርጧል። ዐማራም በለስ ቀንቶት ወደ ትግሬ ሲሻገር እንዲሁ ከማድረግ የሚያግደው ኃይል እንደሌለ ማለት ነው። ውኃ ቅዳ ውኃ መልስ።
… ለወትሮው በደህናው ጊዜ በትግራይ ይከሰት የነበረው የነዳጅ እጥረት አሁን ትግራይ ዙሪያዋን ተከርችማም… ተጠርቅማም የነዳጅ እጥረት ያለመኖሩን ስታይ ደግሞ እንዴት? ለምን? ብለህ ለመጠየቅ የማሰቢያ ፋታ እና ዕድል እንኳ አታገኝም። ማነው ለትግሬው ጦር ነዳጅ የሚያቀርበው? ማነው የመሳሪያ፣ የጥይት አቅርቦት በገፍ የሚሰጠው?  አይገርምልህም?
… በውጭ ያለው ዳያስፖራ ትግሬም “በራብ እና በጠኔ ስለሚያልቀው የትግሬ ወገኑ እንብዛም ግድ የሰጠው አይመስልም። “በሎም” እያለ በአሉላ ሰሎሞን የፌስቡክ ጥቅስ ሲፎክር ነው የሚውለው። የምነግራችሁ ነገር ግን የዐማራ ምድር በትግሬ ታጣቂዎች አስከሬን ተሞልቷል። ከራቡም በላይ በጦርነት እየሞተ ያለው ህዝብ ይልቃል። ከምር ዘግናኝ ነው። በቀጣይ አስከሬኑ በጊዜ ካልተቀበረ በዚያ ምክንያት ወረርሽኝ ሁላ ያሰጋል። በማያውቁት መልክዓ ምድር ላይ፣ በሰሜን ጎንደር በረዶአማ እና ብርዳማ ስፍራ ከትግራይ ሞቃታማ ክፍል በካኒቴራ እና በቁምጣ በባዶ ሆዱ ጭምር ሊዋጋ የመጣው ምስኪን የትግሬ ጦር በዐማራ ምድር እንደ ቅጠል እየረገፈ ስታይ ወደ ውስጥ እያነባህ ከመቀመጥ በቀር ምን ትላለህ።
… እንዳትተወው ሊገድልህ፣ ሊዘርፍህ፣ ሊያወርድህ ነው የሚመጣው፣ የሚሞተውን ስታየው ደግሞ ህፃን ነው። በጣም ያስዝናል። የጨነቀ ነገር እኮ ነው የገጠመው ህዝቡን። በዚህ ሁሉ መሃል ግን የተማረኩ የትግሬ ወጣቶች ገነት መንግሥተ ሰማያት እንደገቡ ያህል ነው የሚቆጠረው።
• ጦርነቱን መለኮታዊ ጣልቃ ገብነት ብቻ ነው የሚያቆመው። እንጂ የትግሬው የቦለጢቃ ልሂቅ ዐማራ በህይወት እያለ ዐማራን ከምድረ ገፅ ሳያጠፋ ማቆም አይፈልግም። ዐማራው ደግሞ መመከት፣ ላለመጥፋት፣ በትግሬው የቦለጢቃ ልሂቅ የታወጀበትን የዘር ማጥፋት ለመመከት በህይወትም የመኖር መብቱን ለማረጋገጥ ከትግሬ ጋር ሲዋጋ ይኖራል። ህወሓት ዐማራን ለማጥፋቱ ብቻዬን እንዳልሆን አግዙኝ ያለቻቸው ኃይሎችም እያገዟት ቢሆንም ዐማራው እስከአሁን የትግሬው የቦለጢቃ ልሂቅ በሚፈልገው መጠን ሊያልቅ አልቻለም። በዚህ መሃል ተረኞቹ የሃገሪቷን የፖለቲካ፣ የአስተዳደር፣ የኢኮኖሚ ኃይል እንደፈለጉት እየፐወዙት ይገኛሉ።
• ጦርነቱ መቆም አለበት። ጦርነቱን ለማቆም ደግሞ ህወሓት እጅ መስጠት አለባት። ሂዊ በቃኝ ብላ እጇን ካልሰጠች ደግሞ ጦርነቱም፣ ራቡም፣ ጠኔውም፣ እልቂቱም ይቀጥላል። ካንሰሯ ህወሓት ከኢትዮጵያ ቦለጢቃ ካልተወገደች የትግሬም፣ የዐማራም፣ የኦሮሞም፣ የዐፋር የመላው ኢትዮጵያ ህዝብ ጤና አያገኝም። ይኸው ነው።
… መጪው ጊዜ በጣም ያስፈራል። ፈጣሪም በጉዳዩ ጣልቃ ይግባበት።
Filed in: Amharic