>
5:13 pm - Friday April 20, 9336

ህወሓትና ብልጽግና ከአንድ ጨርቅ የተቀደዱና ተጣብቀው የተወለዱ የኢትዮጵያ መርገምት ናቸው...!!! (ጎዳና ያእቆብ)

ህወሓትና ብልጽግና ከአንድ ጨርቅ የተቀደዱና ተጣብቀው የተወለዱ የኢትዮጵያ መርገምት ናቸው…!!!
ጎዳና ያእቆብ

ምንም እንኳን የአብይ አህመድ መንግስት እኔ ህጋዊ ስሜ የኦሮሞ ነፃነት ሰራዊት ነኝ የሚልን ቡድን አይ ስምህ አንተ ያልከው ሳይሆን እኔ ዳቦ ሳልቆርስ የማወጣልህ <ሸኔ>> የሚለው ስም ነው ብሎ በዛ መጠሪያ የሚጠራ የሌለ የድርጅት ስም እናም አላማው ድርጅቱን ከተጠያቂነት ነፃ ለማውጣት ቢሆንም በሁለት ምክንያት ጥረቱ አልተሳካለትም።
አንድ የአለም አቀፏ ማኅበተሰብ አብይ አህመድ ባወጣለት በዳቦ ስሙ ሳይሆን ነኝ ብሎ ድርጅቱ እራሱን በሚጠራበት ስሙ መጥራት መጀመሩ ሲሆን ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ ያ ድርጅት ከህዋሃት ጋር ጥምረት ፈጥሮ የአብይ አህመድን መንበር መነቅነቅ በመጀመሩ ነው።
የኦሮሞ ነፃነት ሰራዊት ብሎ እራሱን የሚጠራውንም የኦነግን የወታደራዊ ክንፍ ከህግ ተጠያቂነት ማንፃት እንደማይቻልና ህዋሃትን ማበልፀግ የከሸፈ ፕሮጀክት መሆኑ በማወቅ የፓለቲካ ችግርን በጠብ-መንጃ ለመፍታት መሞከሩ ያደረሰውንና እያደረሰ ያለውን የሰው፣ የቁስ፣ የእሴት እንዲሁም የሀገር ግዛት አንድነት አደጋን በማሰብ ችግሮቻችንን በጠረጴዛ ዙሪያ ለመፍታት ብንሞክር መልካም ነው ባይ ነኝ።
 ጦርነትና እልቂቱ አዝናኝ ፊልም የሆበላቸውና ጭር ሲል የማይወዱ ብዙ እንዳለ ባውቅም ለሀገር ሲባል፣ ለህዝብ ሲባል ከጦርነት መለስ የሆነ መዝናኛ ቢፈልጉ የህዝብን ሰቆቃ ይቀንሳል። ምናልባትም ሀገር ያድናል።
 እብደቱን ከአመት በላይ ሄድንበት። አላዋጣምና ለሰላም እድል ብንሰጥስ?! ሰላም ሰላም የምለው ብልፅግናም ይሁን ህወሃት ሰላም የሚገባቸው፣ የሰው ስቃይና እልቂት ግድ የሚላቸው ናቸው ብዬ ስለማስብ አይደለም።
 እነሱ ከአንድ ጨርቅ የተቀደዱና ተጣብቀው የተወለዱ የኢትዮጵያ መርገምት መሆናቸው ጠፍቶኝ አይደለም።
 ምናልባት  ምናልባት እናንተ ላለፋት ሰላሳ አመታት ይህቺን ታላቅ ሀገር የማስተዳደር እድሉን አግኝታችሁ ሳለ ህዝብና ሀገርን ወደተሻለ ደረጃ ማድረስ ሲገባችሁ እንደ አዳነች አቤቤ <<ከፈለጉ ይገንጠሉ>> የሚል ድንቁርና ሲናገሩ ምላሳቸው የማይደናቀፍባቸው፣ ሀላፊነት የሚባል ነገር ያልፈጠረባቸውና ለመስጠት ወይም ለመከልከል የነሱ ባልሆነው ነገር ላይ የሚያዙ ካድሬዎች ብቻ ማፍራት መቻላቸው ነው።
 እንዲጠብቋት  በአደራ በተጠቻቸውን ሀገር እንደ ባለቤት እከሌ ይቆይ፣ እከሊት ደግሞ ትሂድ የሚሉ ደፋሮች ናቸውና ህዝብ እንደ ህዝብ በቃችሁ ሊላቸው ይገባል ብዬ ስለማስብ ነው።
 ኢትዮጵያ የኛ ብቻ ሳትሆን የልጆቻችንና የልጅ ልጆቻችንም ጭምር ናትና እንደ አህያ እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል የምንል ከንቱዎች ነን ብዬ ማሰብ ስለተሳነኝ ነው።
ዛሬም እንደትላንቱ እንስከን፣ ነገሮችን ከአጉል እብሪት፣ ጥላቻ፣ ፍርሃት እና የስልጣን ጥም በዘለለ ለማየት እንሞክር።
በረሀብ በሰቀቀን እያለቀ ላለው ህዝባችን ርህራሄ ይኑረን።
የጥይት እራት እየሆነ ላለው ወጣት ግድ ይበለን።
አዛውንቶቹ እንደው ዛሬም እንደትላንቱ ምቾታቸውን ሳይለቁ እስር ቆመው ዘራፍ ማለት እንጂ ጦርነት በደረሰበት አይደርሱም።
 የቤተ መንግስት ባለሟሎቹም እንድንዘምት ይፈቀድል እያሉ በየመድረኩ ይለምናሉ እንጂ ፍርፋሪ ከሚያገኙበት ከቤተ መንግስት ደጃፍ አይርቁም።
እመኑኝ ይህ ጦርነት ሲያልቅ ከነሱ አንድም አይሞትም። የአንዳቸውም አካል አይጎድልም። ልጆቻቸውም እንደዛው።
 ይብላኝ አትግባ አብልታው የማታውቀውን ሀገር ወዶ ህይወቱን ለሚገብርላት የደሀ ልጅ። ጠግበው የሚያድሩትማ ሆዳም ሰው ፍቅር አያውቅም እንዲሉ እንኳን ሀገርን ቀርቶ እራሳቸውን እንኳን መውደድ አቅቷቸው ለመጣው ሁሉ ተላላኪ ባሪያና ሎሌ ሆነው መኖር ሁለተኛ ባህሪያቸው ሆኖ ነው ከወጣትነት እስከ ሽበት የምናያቸው።
እነሱ በስኳርና በደም ብዛት ይሙቱ እንጂ ምን በወይን ብለው በጦርነት ይሞታሉ!
 ስለዚህ እባካችሁ ቆም ብለን እናስብ።
ለውይይት እና ለምክክር እድል እንስጥና ችግሮቻችንን በጦርነት ዙሪያ መፍታት ካልቻልንና ጦርነት ብቸኛ መንገዳችን ከሆነ ነገ ከነገ ወዲያ ካቆምንበት መቀጠሉን ማንም አይወስድብንም።
Filed in: Amharic