የኀዘን መልእክት
| ዛሬ የሚፈፀመውን የአምባሳደር ዶክተር ካሣ ከበደን ዕረፍት በማስመልከት የቀድሞው የኢህዲሪ ፕሬዝዳንት ሌ /ኮ መንግሥቱ ኃ/ማርያም የሚከተለውን የኀዘን መልእክት አስተላልፈዋል::
” የጓድ ዶክተር ካሣ ከበደን ሕልፈተ ሕይወት በመስማቴ ጥልቅ ኀዘን ተሰምቶኛል:: ጓድ ካሣ በሥራ ዘመናችን ሁሉ አንድም ቀን ያልተለየኝ የትግል አጋሬ ወንድሜ ነበረ:: እሱን የመሰለ ድንቅ የፈጠራ ችሎታ ያለው ታታሪ ሠራተኛና ሀገሩን የሚወድ ወንድማችን ሲለየን ኀዘኑ ከባድ ነው:: በቅርቡ የተለዩንን ጓዶቼን በማስታወስ ዛሬም ጓድ በማጣታችን በእጅጉ አዝኛለሁ” ::
ሌ/ኮ መንግሥቱ ኃይለ ማርያም
Via ገነት አየለ
ባለ ብሩህ አእምሮው አምባሳደር ካሣ ከበደ ….!!!
ገነት አየለ አንበሴ
![](https://ethioreference.com/wp-content/uploads/2021/12/FB_IMG_1640939026409-208x300.jpg)
የመንግሥቱ ወንድም ናቸው የሚባለው ሹክሹክታም በየጊዜው የምንሰማው ስለነበረ መንግሥቱን ጠይቄያቸው ከሰጡኝ መልስ በተጨማሪ እሳቸውም እንዲነግሩኝ ፈለግሁና ወደ ዋሽንግተን ዲሲ አቀናሁ:: ወዳጄ ነአምን ዘለቀ ነበረ ቃለ መጠይቁን እንዳደርግ ያመቻቸልኝ::
ቨርጂኒያ ሜሪላንድ የሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው ሄጄ አነጋገርኳቸው:: የተደላደለው ምቹ ወንበር ላይ ተቀምጠው አንድ በአንድ ጥያቄዎቼን ሲመልሱ በጣም ብልህ ሰው መሆናቸውን ተረዳሁ:: በተለያዩ ጉዳዮች ላይ የሚሰጡት ትንታኔ የሚገርም ነበር :: ስለሚናገሩት ነገር በቂ ዕውቀትና ግንዛቤ እንዳላቸው ከሚሰነዝሯቸው ሃሳቦች ጥልቀት መረዳት ይቻላል:: የተዋጣላቸው ዲፕሎማት ነበሩ የደጃዝማቹ ልጅ ጓድ ካሣ :: የማህበረ ሰብ ሳይንስ ምሩቅ ብቻ ሳይሆኑ በባለሥልጣንነታቸው ባበረከቱት አስተዋፅኦ ሳይወሰኑ እንደ ተራ ሶሻል ሠራተኛ ሆነው ይሰሩ ነበር :: ዕረፍት የማያውቁ ታታሪ ሰው መሆናቸው ተመስክሮላቸዋል:: የታጠቅ ጦር ሠፈርን ከምስረታው ጀምረው የለፉበት ሲሆን የሕፃናት አምባን ሃሳቡን ከማፍለቅ ጀምሮ ተግባራዊ እንዲሆን ደክመዋል::
መጽሐፉ ከታተመ ከጥቂት ጊዜ በሁዋላ ሳገኛቸው የመጽሐፉን ገፆች እያገላበጡ ሲያዩ ቆዩና
“እነዚህ ጓድ ቁጥር እከሌ ያልሻቸው እነማናቸው? አሉኝ ትንሽ ምፀት ያለባት ፈገግታ እያሳዩኝ::
እኔም አፀፋውን ለመመለስ “ባውቀው ምን አስደበቀኝ?” አልኳቸው እየሳቅሁ::
“ቆይ እንግዲያው እኔ ልንገርሽ” አሉና
ቁጥር …ያልሽው እከሌ ነው:: ይሄ ደግሞ እንትና ነው:: ጓድ እከሌን ነው ቁጥር .. ያልሺው? እያሉ አንድም ሳይሳሳቱ ነገሩኝ:: ማንም እንዳያውቀው የማዕረግ ቅደም ተከተላቸውን ሁሉ አዛብቼ የሰጠሁዋቸውን ቁጥር ወደ ጎን ትተው ከንግግራቸው ብቻ ግንዛቤ በመውሰድ ቁጭ ሲያደርጉልኝ ድካሜ ውሃ በላው ብዬ ክው አልኩ:: ሁሉም ሰው ሁሉ የሚያውቃቸው መሰለኝ:: ድንጋጤዬን ለመደበቅ የማደርገውን ጥረት ከፊቴ እያነበቡ ከት ብለው ሳቁብኝ:: ” እውነትም እኚህን ሰው ሞሳድ ነው ያሰለጠናቸው ” አልኩኝ በልቤ::
ነፍስዎ በአፀደ ገነት ትረፍ ጓድ ካሣ: