>

በዓላት የሰላምና የደስታ ቀን ናቸው፤ በዚህ ቀን ሕዝብ ላይ መተኮስ ምን የሚሉት እብሪት ነው? (ያሬድ ሀይለማርያም)

በዓላት የሰላምና የደስታ ቀን ናቸው፤ በዚህ ቀን ሕዝብ ላይ መተኮስ ምን የሚሉት እብሪት ነው?
ያሬድ ሀይለማርያም

 
* ….   በአዲስ አበባ፣ ወይብላ ማርያም የጥምቀትን በዓል ሊያከብሩ በወጡ ምዕመናን ላይ አስለቃሽ ጭስ እና ጥይት መተኮስ ሕግ ማስከበር ሳይሆን የለየለት እብሪት ነው። በተተኮሰው ጥይት ሁለት ሰዎች መገደላቸው ተገልጿል። መንግስት በእንዲህ ያለው ሕገ ወጥ የሆነ የነውር እና ጸብ አጫሪ ሥራ ላይ የተሰማሩትን የጸጥታ ጏይሎችና ትዕዛዝ የሰጡ አካላትን በቁጥጥር ሥር አውሎ ሕግ ፊት ማቅረብ አለበት። 
 
እግረ መንገዴን ግን ለመንግስት ጥያቄ ላቅርብ፤
– ለምንድን ነው በዓላት በመጡ ቁጥር ዜጎች ያሻቸውን ቀለም፣ ያሻቸውን ባንዲራ እንዳይዙ በፖሊስ ማስጠንቀቂያ የሚሰጠው?
– አንድ ሰው ያሻውን ባንዲራ ግምባሩ ላይ ቢያስር፣ በጁ ቢይዝ፣ ጥለት አርጎ ቢለብሰው፣ ወይም ባሻው መንገድ አሰፍቶ ቢለብሰው ለምን ሕገ ወጥ ይሆናል?  ያንንስ በማድረጉ ማንን ይጎዳል?
– የሀይማኖት በዓላት የአንድ ቀን ወይም ግፋ ቢል የሁለት ቀን ዝግጅቶች ናቸው። እንዴት ለዚህ አይነት አጭር ክስተት ምዕመናን ያሻቸውን ባንዲራ ቢያውለበልቡና በደስታ እንዲውሉ መፍቀድ ለመንግስት ከባድ ይሆናል?
– ይህ አይነቱ ዜጎችን የማሳቀቅ፣ የማሸማቀቅ እና በባዕላት ቀን እንኳ ነጻነት እንዳይሰማቸው አድርጎ ደስታቸውን መንጠቀ ለመንግስት ከመጠላት በቀር ምን ያተርፍለታል?
– እንዲህ ያለው የጥቃት  እርምጃ በተለይም በኦርቶዶክስ እምነት በዓላት ላይ ተደጋግሞ መከሰቱስ አገሪቱ ቶሎ የማትወጣው ሌላ ችግር ውስጥ አይከታትም ወይ?
በጥምቀትም፣ በኢድም ሆነ በኢሬቻ ሁሉም የወደደውን ይልበስ። የቀለም ምርጫ ለለባሹ ይተው። በዚህ ፖለቲካ መስራት የዜጎችን መብት ከመጣስም ባለፈ ሌላ አገራዊ መዘዝ ያስከትላል።
የፌደራል መንግስት ትላንት የወይብላ ማርያም ታቦት በሰላም እንዳይገባ ያወኩትን፣ ጥይት ተኩሰው የገደሉትን እና መመሪያ የሰጡት ፖሊሶች ላይ ሕጋዊ እርምጃ መውሰድና ታቦቱ ዛሬ  በሰላም እንዲገባ በቂ ጥበቃ ማድረግ ይኖርበታል።
Filed in: Amharic