>

መንግስት እራሱን በራሱ እራሱን እያሸበረ ነው፤ ያም ሆኖ እንዳይወድቅ አንድ ነገር አግዞታል...ምን??? (ሸንቁጥ አየለ)

መንግስት እራሱን በራሱ እራሱን እያሸበረ ነው፤ ያም ሆኖ እንዳይወድቅ አንድ ነገር አግዞታል…ምን???
ሸንቁጥ አየለ

አንድ መንግስት ለሚመራዉ ህዝብ በጣም የሚጠነቀቅ:የሚጨነቅ እና የህዝቡን ስነልቦና ላለመጉዳት የሚችለዉን ሁሉ ማድረግ የሚችል ከሆነ ብቻ ረዥም ጊዜ በህዝብ ልብ ዉስጥ የመቆዬት እድል ይኖረዋል::
የብልጽግና መንግስት ግን ለሚመራዉ ህዝብ የማይጨነቅ: ለራሱ መንግስት የማይጠነቀቅ:ግዴለሽ እና በራሱ ላይ ሽብር ያወጀ መንግስት ነዉ::በዚህም እራሱን ከዉስጡ ቦርቡሮ የበላ መንግስት ነዉ::ሆኖም የብልጽግና መንግስት እንዳይወድቅ አንድ ቁልፍ ነገር ደግፎ ይዞታል::ይሄዉም ሀገራዊ ተቃዋሚ ሀይል የለዉም::
————-
የአማራ ተቃዋሚ  ፓርቲ ነን የሚሉት
——————
የብልጽግና ተቃዋሚዎች በአጠቃላይ ሲታዩ ቀልደኛ ተቃዋሚዎች ናቸዉ::የአማራ ተቃዋሚ ነን የሚሉት በአንድ ገበታ ከብአዴን ጋር ቁጭ ብለዉ እየበሉ በሌላ እጃቸዉ ደግሞ ብልጽግናን/ኦህዴድን እንቃወማለን ባዮች ናቸዉ::አንዳንዶቹ አክራሪ ተቃዋሚ ነን ቢሉ እንኳን ከብአዴን ጋር ያላቸዉ ግንኙነት ከመረቁ አዉጡልኝ ከስጋዉ ጾመኛ ነኝ የሚል አይነት ነዉ::ሁለተኛዉ የአማራ ተቃዋሚዎች ትልቁ ድክመት ደግሞ እራሳቸዉን ባህርዳር ላይ የወሰኑ መሆናቸዉ ነዉ::
ትግላቸዉ ከምኒሊክ ቤተመንግስት የተቆረጠ ራዕይን ያነገበ ነዉ::የሚሰባሰቡት እና የሚፎክሩት አማራ ክልልን እያሰቡ መሆኑ ነዉ::ስለዚህ የአማራ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በአንድ ወገን ብአዴን በጎን አንቆ በርቀትም በቅርበትም ስለያዛቸዉ ከዚያም በላይ ከመረቁ አዉጡልኝ ከስጋዉ ጾመኛ ነኝ አይነት ከብአዴን/ብልጽግና ጋር የደም ትሥስር ይሁን የአስተሳሰብ ትሥስር ዉስጥ ስለገቡ የስነመንግስት ጥያቄያቸዉ ጎሃ ጺዮንን የሚያሻገር አልሆነም::ግፋ ቢል በደሴ አቅጣጫ ተጎዞ ፍላጎታቸዉ የሚያርፈዉ ደብረብርሃን ከተማ ላይ እየሆነ ተቸግረዋል::
ሌላዉ ቀርቶ በዉጭ ሀገር የሚነጫነጩት የአማራ ልዩ ልዩ ተቃዋሚዎች የደም ነገር እየሆነባቸዉ ይሁን ወይም የብአዴን የተራቀቀ የድርጅት ጠለፋ አስቸግሯቸዉ ወይም ከብአዴን ጋር የሚያስተሳስራቸዉ ቀጭን የዓላማ አንድነት እየኖረ ይሁን በማይታወቅ መልኩ ብዙዎቹ ከብአዴን ጋር ያላቸዉ ግንኙነት ከመረቁ አዉጡልኝ ከስጋዉ ጾመኛ ነኝ የሚል አይነት ነዉ::
አምስት ሆነዉ ቢሰበሰቡ ሶስቱ ግዴለም ዛሬ ብአዴን እናግዘዉ እና ወደፊት ብአዴን ሲጠነክር እኛም ጠንከር ያለ ተቃዋሚ እንሆንበታለ የሚሉ ግራ ግብት ያላቸዉ ብዙሃን ናቸዉ::እናም ብልጽግና ከአማራ ተቃዋሚዎች በኩል የሚመጣ የስነመንግስት ግፊያ ከቶም አያሰጋዉም::የስነ መንግስት ይገባኛል ጥያቄ የሚያነሳበት እስካሁን ከአማራ ተቃዋሚዎች በኩል ከቶም አልደረሰዉም::የብልጽግና መንግስትም ይሄን በደንብ የተረዳዉ ይመስላል::
——————
ሀገራዊ ተቃዋሚ ፓርቲ  ነን የሚሉት
————————-
ሌላዉ ብልጽግና እድለኛ የሆነበት ነገር ሀገራዊ ተቃዋሚ ፓርቲ ፈጽሞ መጥፋቱና መዳከሙ ነዉ::ቀድሞ ኦነግ መር የሆነዉን ግንቦት ሰባት እየደበላለቀ የሀገራዊ አንድነት ፓርቲ ነኝ ሲል የነበረዉ ግንቦት ሰባት/አሁን ኢዜማ በአስተማማኝ የብልጽግና ዋና ክንፍና አካል ሆኗል::
አሁን በራሱ እግር የቆመ: አጠቃላይ ኢትዮጵያዉያንን ሊያንቀሳቅስ የሚችል(የብልጽግና ደጋፊዎች:የህዉሃት ደጋፊዎች:የኦህዴድ ደጋፊዎች: እና የብአዴን ንክኪዎችን ሳይጨምር ማለት ነዉ) ኢትዮጵያዊ ሀገራዊ ፓርቲ አለመኖሩ ለብልጽግና ቁልፍ ምቹ ሁኔታን ፈጥሮለታል:: ቢጠቀምበት ይሄ ለብልጽግና ትልቅ ከሰማይ የወረደ ጸጋ እና አጋጣሚ ነበር::በዚህ ረገድ ብልጽግና ላይ ምንም የሚያሰጋዉ አንዳች ስጋት አልነበረም::እዚህ እና እዚያ ተበታትነዉ የሚገኙት እኢትዮጵያ አንድነት አቀንቃኞች በራሳቸዉ ክፋት እና ምቀኝነት እንዲሁም ለሰላሳ አመታት እርስ በርሳቸዉ ስለተቆሳሰሉ እንኳን ተሰባስበዉ ህዝብ ሊሰበስቡ ይቅርና እራሳቸዉ ተሰባስበዉም ለመነጋገር ተቸግረዋል::
ይሄን ሁሉ ጸጋ የተላበሰዉ የብልጽግና መንግስት ግን በራሱ ጊዜ ትግሉን ከራሱ መንግስት ጋር በማድረግ ኢትዮጵያዉያንን ማስከፋት:ማሸበር:ማዋከብ እና ማስጨነቅን እንደ ቁልፍ የስነ መንግስቱ ማስቀጠያ መሳሪያነት እየተጠቀመበት ይገኛል::በአጭሩ በራሱ መንግስት ላይ እራሱ ሽብር እያደረገ ማንኛዉም ተቃዋሚ ሊያደርስበት ከሚችለዉ የመናጋት ጫና የከፋ ጫናን እያደረገ የሚገኘዉ የብልጽግና መንግስት የስነ መንግስት ሚስጢር ገና ምንም አልተገለጠለትም::
ጠቅለል ሲደረገ የራሱን መንግስት በራሱ እጅ የሚያሸብረዉ እና በራሱ ላይ ጫና በማድረግ እራሱን ለማፍረስ እየተወራጨ ያለዉ የብልጽግና መንግስት ያልተረዳዉ የስነ መንግስት ሚስጢር ብዙ ነዉ::የስነ መንግስትን ሚስጢር ለመረዳት እና ለመማር ባለመፈለጉም የራሱን መንግስት በራሱ እጂ ቦርቡሮ የሚጥለዉ እራሱ ብልጽግና ይሆናል::ይሄም የሚሆነዉ ህዝቡን ፈጽሞ በማስከፋት እና ህዝባዊ የመተፋት ቁጣን በራሱ ላይ በማዝነብ ይሆናል::በተቃዋሚ በኩል ግን ብልጽግና እድለኛ ነዉ::
Filed in: Amharic