>

እውነታው ይህ ነው...!!!! (ምኒልክ ሳልሳዊ)

እውነታው ይህ ነው…!!!

ምኒልክ ሳልሳዊ

በኦሮሚያ የሚፈጸሙ ወንጀሎችና የሽብር ድርጊቶች የሚመራው የኦሮሚያ ብልጽግና ነው። የኦነግ ጦር መንግስት ሸኔ የሚለው በቤንሻንጉል ጉምዝ ሳይቀር የማሰልጠኛና የማደራጃ ካምፕ አለው። የመንግስት ሚዲያዎች በተለመደው የቅጥፈት ዘገባቸው ሰንቀሌና ቀልቀልቲ ማሰልጠኛ እንደተደመሰሰ ነግረውናል። ቅጥፈት የማይሰለቸው መንግስት ምንም አልሰራም እንዳይባል ራሱ በሚያዘጋጀው ድራማ ጥይቶችንና የጦር መሳሪያዎችን በቁጥጥር ስር እንዳዋለ አድርጎ ይሰብከናል።
በወለጋ የሚገኙ የኦነግ ጦር ማሰልጠኛዎች እንዲሁም በሸዋና በቤንሻንጉል የሚገኙ ማሰልጠኛዎችና ማደራጃዎች ምንም አይነት ውድመትም ይሁን ጉዳት አልደረሰባቸውም። ጭራሽ ሮኬቶችንና የተለያዩ ከባባድ መሳሪያዎች እንዲታጠቅ ዝግጅቱ ተጠናቆ በአዲስ መልክ የሎጀስቲክ ስራው ሊጀመር ነው። ይሕን በቅርብ ካሉ የኦነግ ጦር ሰዎች ማረጋገጥ ተችሏል። ይህ በተቀናጀ መልኩ የሎጀስቲክ ድጋፍ የሚያገኘው የኦነግ ጦር ከበታች የኦሮሚያ ብልጽግና አመራሮች ጀምሮ እስከ ከፍተኛ የኦሮሚያ ብልጽግና አመራሮች ድረስ የጦር ጄኔራሎች ሳይቀሩ በተቀናጀ መልኩ በቂ ድጋፍ ይደረግለታል።
በኦሮሚያ ክልል በሚኖሩ የአማራ ተወላጆች ላይ እንደ ዜጋ በገዛ አገራቸው እንዳይኖሩ ከፍተኛ ስራ በመስራትና በማስገደል ላይ የተሰማራው በኢትዮጵያ ስም እየነገደ ተግባሩ ኝ ኢትዮጵያን ማጥፋት የሆነው የኦሮሚያ ብልጽግና ለሚሰራው የተንኮልና የደባ ስራው የሕወሓትን ጦርነት መክፈት እንደ ሽፋን ተጠቅሞበታል። አገር እንዳትፈርስ፣ ሃገር ለማፍረስ፣ ሃገር ልትፈርስ ነው ወዘተረፈ በሚል ፕሮፓጋንዳ በመርጨት በተግባር ግን አገር እያፈረሰ ያለው የኦሮሚያ ብልልፅግና የሚባለው አደገኛ ቡድን ነው።
የኦነግ ጦር በጉጂ፣ በወለጋ። በሸዋና በቤንሻንጉል የሚፈጽመው ሽብር ኃላፊነቱን መውሰድ ያለበት የገዢው ፓርቲ ሲሆን እንዲሁም ሃገሪቱ ባለፉት አራት አመታት ውስጥ በከፍተኛ መናወጥ እንድታሳልፍ እና ደርግ እና ሕወሓት በስልጣን ዘመናቸው ከገደሏቸው ዜጎቻችን እጥፉን የገደለውና ያስገደለው የብልጽግና አገዛዝ ኃላፊነቱን መውሰድና ተጠያቂ ሊሆን ይገባዋል።
ከዛሬ ነገ ሰላም ይሰፍናል። ሊረጋጋ ይችላል ። ችግሮች የለውጥ አካላት ናቸው። አና የመሳሰሉት ቅን ሃሳቦች የያዘው ሕዝብ ከመሻሻል ይልቅ እየባሰ መሄዱ ስላሳሰበው በመንግስት ላይ እምነቱን አጥቷል። የሕወሓት በአፋር በኩል መስፋፋቱና መንግስት አትኩሮት ላለመስጠት የሚያደርገው ጥረት በራሱ ሌላኛው የመንግስት ለዜጎች ያለውን ዴንታቢስነት ያሳያል። የመንግስት መዋቅር በራሱ የተበላሸ ስለሆነ መንግስት ራሱ ፈርሶ መሰራት አለበት ።
Filed in: Amharic