በጉዞ ላይ የነበሩ ከ100 በላይ የአባይግድብ ሰራተኞች በመተከል ተገድለዋል…!!!
ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ
*…. ቤንሻንጉል መስተዳድር በማንነት ላይ የሚፈፀሙ ጥቃቶችን ማስቅም አልቻለም ተባለ
ባለፈው የካቲት 23 ቀን 2014 ዓ.ም. ወደ አባይ ግድብ በአውቶብስ ሲጓዙ በነበሩ የግድቡ ሰራተኞች ላይ በደረሰ የሽብር ጥቃት ከመቶ በላይ ሰዎች ተገድለዋል። ግድያው በጉምዝ ታጣቂዎች፣ በኦነግ #ሸኔ እና በወያኔ የሦስትዮሽ ትብብር ተፈፅሟል የሚል ግምገማ እንዳለውም የመተከል አማራ ማንነት አስመላሽ ኮሚቴ አስታውቋል። በግፍ ከተገደሉት ንፁሃን መካከል 30ዎቹ አማሮች ሲሆኑ 40ዎቹ የሀገር መከላከያ ሰራዊት ሰራዊት አባላት መሆናቸውን የመረጃ ምንጮች አረጋግጠዋል።20 ተሽከርካሪዎችም ዳንጉር ወረዳ፤ አፍሪካ እርሻ ልማት አካባቢ ተቃጥለዋል።
የኦነግ-ሸኔ እና የጉምዝ ታጣቂዎች በአማራው ላይ በቤንሻንጉል ጉምዝ የሚያደርሱት ጥቃት አሁንም አለመቆሙንም፤ የመተከል አማራ ማንነት ኮሚቴ ገልጿል። የኮሚቴው የሕዝብ ግንኙነት ሓላፊ አቶ ደሳለኝ እጅጉ ከባልደራስ ጋዜጠኞች ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለፁት፣ የዘር ማጥፋት እንቅስቃሴው እየተደገፈ ያለው በአንዳንድ የቤንሻንጉል ጉምዝና #ኦሮሚያ መስተዳድሮች ባለሥልጣናት ነው።

በመሆኑም፣ በአካቢው ካለው የሀገር መከላከያ ሰራዊት በተጨማሪ የአማራ ልዩ ሃይል ወደ ሥፍራው ገብቶ ቦታዎችን ከአሸባሪው ቡድን እንዲያስለቅቅ እና ሰላም እንዲያስከብር የመተከል አማራ ማንነት አስመላሽ ኮሚቴ ጠይቋል። በአካባቢው የሚገኙ በርካታ አማሮች በተለያዩ ጊዜያት በጅምላ መጨፍጨፋቸውን የገለፀው ኮሚቴው በሕይወት የተረፉትም ከቀያቸው እየተፈናቀሉ መሆኑን አረጋግጧል።
የአማራ መስተዳድር ጉዳዩን በዝምታ ማየቱንም አጦብቆ ኮንኗል። አቶ ደሳለኝ ጋር ያደረግነውን ዝርዝር ቆይታ በቪዳዮ (ተንቀሳቃሽ ምስልና ድምፅ) የምናቀርብ ይሆናል።