>

የፓርቲያችን አመራሮች  ከተባበሩት መንግስታት የጀኖሳይድ እና የሰብዓዊ መብት ኃላፊዎች ጋር ተነጋገሩ! (ባልደራስ)

የፓርቲያችን አመራሮች  ከተባበሩት መንግስታት የጀኖሳይድ እና የሰብዓዊ መብት ኃላፊዎች ጋር ተነጋገሩ!

ባልደራስ


*…. በኦሮሚያ ክልል በአማራ ላይ ስለሚፈጽሙ የዘር ፍጅት ቀጥተኛ ምስክርነት አሰምተዋል!

 

በአሜሪካ ዋሽንግተን ዲሲ የሚገኙት የባልደራስ ፕሬዘዳንት እስክንድር ነጋ፣ የሰብዓዊ መብት ተከራካሪዎቹ  ፅጌረዳ ሙሉጌታ፣ ዶ/ር ዮሐንስ ገ/መስቀል እና ስቴፋን ቦርነር በኦሮሚያ ክልል በንፁሃን አማሮች ላይ እየተፈፀመ ስለሚገኘው የዘር ፍጅት በኒውዮርክ ከሚገኘው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ኃላፊዎች ጋር ተወያይተዋል፡፡

በመንግስታቱ ድርጅት ዋና ጽ/ቤት በተደረገ ውይይት የጀኖሳይድና የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን የሚከታተሉ ኃላፊዎች ተገኝተዋል፡፡

እነ እስክንድር ነጋ ጉዳዩን ሲያስረዱ፣ “እኛ የምንለውን ከመስማት ይልቅ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ የጥቃቱ ሰለባዎችን በቀጥታ ልታዳምጡ ይገባል” በማለት፣ ወደ ኢትዮጵያ ደውለው አንድ ተፈናቃይ በቀጥታ የደረሰባቸውን በአስተርጓሚ አስረድተዋል፡፡

የጥቃት ሰለባው ሲናገሩ፣ አንዲት እርጉዝ ሴት ተኝታ የነበረችበት ቤት ውስጥ በመግባት የኦነግ ሸኔ ታጣቂዎች ሆዷን ተርትረው እንደገደሏት፣ አንድ ሙስሊም አማራ በአሰቃቂ ሁኔታ ከተገደለ በኋላ እሬሳውን እንዳቃጠሉት፣ አንዲት እናትም በጉርብትና በሚያውቁት አንድ የኦነግ ሸኔ ታጣቂ በአሰቃቂ ሁኔታ መገደላቸውን አስረድተዋል፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን የኦሮሚያ ክልል መስተዳድር ባለስልጣናት በጥቃቱ እንደሚተባበሩ ገልፀዋል፡፡

ከዚህ በኋላ አስተያየት የሰጡት እነ እስክንድር ነጋ፣ “በእነዚህ ጥቃቶች የመንግስት ኃላፊዎች እጅና ጓንት ሆነው ጥቃት ባይሰነዝሩ ኖሮ፣ ወደ እናንተ መምጣት ባላስፈለገን፡፡  ለመንግስት አቤት ማለት ባለመቻላችን  ግን ወደ እናተ ለመምጣት ተገደናል፡፡ ሁኔታዎች በዚህ ከቀጠሉ፣ እንደ ሩዋንዳ በመንግስት ኃይሎች የታገዘ መጠነ ሰፊ የዘር ጭፍጨፋ (genocide) በኦሮሚያ ክልል መፈፀሙ አይቀሬ ነው፡፡ ጄነኖሳይድ በኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች ተፈፅመዋል ወይም እየተፈፀሙነው ቢባልም፣ በኦሮሚያ ያለው ግን እጅግ አደገኛ መሆኑንና መጠነ ሰፊ ጉዳት ሊያደርስ የሚችል መሆኑ ሊታወቅ ይገባል፡፡ የኦሮሚያ በተለየ መንገድ ታይቶ በተለየ ሁኔታ ጉዳዩ ተመርምሮ አፋጥኝ ሁኔታ እርምጃ ሊወሰድ ይገባል፡፡ ይህንን ስናመለክት ለሁለተኛ ጊዜ መሆኑ ነው፡፡ ጉዳዩ ከቀን ወደ ቀን እየተባባሰ ነው” ብለዋል፡፡

የተባበሩት መንግስታት ኃላፊዎች በበኩላቸው የጥቃት ሰለባውን የምስክርነት ቃል፣ ስምና አድራሻ እንዲሁም የስልክ ቁጥር ከተቀበሉ በኋላ፣ በራሳቸው መንገድ አጣርተው ሪፖርት እንደሚያቀርቡ ቃል ገብተዋል፡፡  እነ እስክንድር በበኩላቸው፣  “በሺዎች የሚቆጠሩ ምስክሮች አሉ፡፡ እነሱን ሁሉ ማቅረብ እንችላለን” ብለዋል፡፡

Filed in: Amharic