>

የአማራ ሕዝብና ያጭቤ ዜናው አባት አማራ ጠሉ ቢቢሲ! (መስፍን አረጋ)

የአማራ ሕዝብና ያጭቤ ዜናው አባት አማራ ጠሉ ቢቢሲ!

መስፍን አረጋ


Ethiopia’s government has launched a crackdown against a powerful and increasingly autonomous regional security force, in a bold, and potentially risky move to extend central control over a fractious nation …These new measures by Ethiopia’s prime minster are designed to clip the wings of an increasingly strident nationalist movement in Amhara …” (BBC, “Ethiopia unrest: Sudden arrest of 4,000 spells fear in Amhara”, May 27, 2022).   

የኢትዮጵያ መንግሥት ኢትዮጵያን ከመፈራረስ ለመታደግ ሲል ከቁጥጥሩ ውጭ ይበልጥና ይበልጥ እያፈነገጠ ያለውን ጠንካራውን የአማራ ክልል የፀጥታ ኃይል ለመደቆስ ዘመቻ ከፍቷል … የዐብይ አሕመድ መንግሥት ይህን ድፍረትን የሚጠይቅ አደገኛ ዘመቻ የከፈተው ቅጥ ያጣውን የአማራ ብሔርተኝነት ቅጥ ለማስያዝ ነው …”  (ቢቢሲ)    

የአጭቤ ዜናው አባት (father of fake news) የእንግሊዙ ቢቢሲ (BBC) የለየለት ፀራማራ (anti-Amhara) ወይም አማራጠል (Amharaphobic) መሆኑን ከዚህ የበለጠ ቁልጭ አድርጎ መግለጽ አይችልም፡፡  በቢቢሲ ዕይታ መሠረት ዐብይ አሕመድ በአማራ ሕዝብ ላይ የከፈተው መጠነ ሰፊ የጅምላ ጭፍጨፋ ዘመቻ ኢትዮጵያን ከመፈራረስ ለመታደግ ስለሆነ፣ ባስፈላጊው መንገድ ሊደገፍ የሚገባው ተገቢ ዘመቻ ሲሆን፣ በትግሬ ሕዝብ ላይ የሚደረግ ተመሳሳይ ዘመቻ ግን በጽኑ ሊወገዝ የሚገባው የዘር ማጥፋት (ethnic cleansing) ዘመቻ ነው፡፡ 

በዚሁ በቢቢሲ እይታ መሠረት የአማራ ቤታደሮች (civilians)፣ ፖለቲከኞች፣ ጋዜጠኞች እና ወታደራዊ አዛዦች ከመላው ኢትዮጵያ እየተለቀሙ በጅምላ መታሠር ቅጥያጣውን የአማራኝ ብሔርተኝነት ቅጥ ለማስያዝ (to clip the wings of an increasingly strident nationalist movement in Amhara) ሲሆን፣ የትግሬወች በአዲስ አበባ መታሠር ግን ዘርን መሠረት ያደረገ የዘፈቀደ የምጅላ እስር (ethnically targeted arbitrary mass arrest) ስለሆነ በተባበሩት መንግስታት ደረጃ በጥብቅ መወገዝ አለበት፡፡  የምዕራባውያን ጉዳይ አስፈጻሚ የሆነው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ደግሞ እነ ቢቢሲ አውግዝ ያሉትን በጽኑ በማውገዝ ትግሬወች በትግሬነታቸው እየተለቀሙ በአዲስ አበባና በሌሎች ከተሞች በጅምላ እየታሠሩ ነው (arbitrary mass arrests target Tigriayans, says UN rights office, November 16, 2021) የሚል መግለጫ አውጥቷል፡፡         

የአማራ ልዩ ኃይል በብዛትና በትጥቅ ከሁሉም የክልል ልዩ ኃይሎች እጅግ አናሳ ከመሆኑም በላይ አዛዦቹን ዐብይ አሕመድ በፈለገው ጊዜ እንደፈለገው የሚሾማቸውና የሚሽራቸው ቢያንስ ባመራር ደረጃ በዐብይ አሕመድ ሙሉ ቁጥጠር ሥር የሆነ ኃይል መሆኑን አገር ያወቀው ፀሐይ የሞቀው ነው፡፡  የወያኔ ኃይል ደግሞ ያገር መከላከያን ኃይል ባያስንቅ እንኳን የሚገዳደር ከመሆኑም በላይ አዛዦቹ ደግሞ ትግራይን እንገነጥላለን እያሉ በማናለብኝነት ስሜት በግልጽ የሚዝቱ ናቸው፡፡  በቢቢሲ እይታ መሠረት ግን የአማራ ኃይል ከዐብይ አሕመድ ቁጥጥር ይበልጥና ይበልጥ እያፈነገጠ ያለ ጨፍጫፊ ኃይል ስለሆነ (increasingly autonomous regional security force) ዐብይ አሕመድ ያለ ርህራሄ ሊደቁሰው (crackdown) የሚገባ እኩይ ኃይል ሲሆን፣ የወያኔ ኃይል ግን የአማራ ኃይል በትግራይ ሕዝብ ላይ የሚፈጽመውን የዘር ጭፍጨፋ (ethnic cleansing) የሚከላከል ሰናይ ኃይል ስለሆነ ዐብይ አሕመድ ሊያከብረውና በቅን መንፈስ ሊደራደረው ይገባል፡፡  

በቢሲ እይታ መሠረት ፋኖ ማለት በትግራይ ጦርነት ወቅት የዘር ጭፍጨፋ ፈጽሟል ተብሎ በሰብዓዊ መብት ድርጅቶች የሚከሰሰው የታጠቀ የጎረምሶች ስብስብ (“a collection of armed youth groups accused by human rights organizations of atrocities during the unresolved civil war in Tigray”, BBC, May 27, 2022) ሲሆን፣ ወያኔ ማለት ደግሞ ክብራቸውን ለማስጠበቅ ሲሉ ከሁሉም ማሕበራዊ ዘርፎች የተውጣጡ ትግሬወች የመሠረቱት ኃይል ነው (“Tigrayans from all sections of society joined to protect their diginity”, BBC, November 18, 2021). 

በቢቢሲ አጭቤ ዜና (fake news) መሠረት ትግሬወችን አምረረው የሚጠሉት የአማራ ኃይሎች፣ ትግሬወችን ባሰቃቂ ሁኔታ ከጨፈጨፏቸው በኋላ፣ ለትግሬወች ሬሳ ግን ከፍተኛ ክብር በመስጠት ትግሬወች ከማናቸውም ቅዱሳን በላይ በሚያከብራቸወች በአቡነ አረጋዊ ቤተክርስቲያን ቅጽር በጅምላ ቀበረዋቸዋል (“On the morning of 10 April, the Amhara militias dug up the four mass graves in St. Abune Aregawi Church”, BBC, May 7, 2022)::  

በዚሁ በቢቢሲ ዘገባ መሠረት ምዕራብ ትግራይን የወረሩት የአማራ ኃይሎች የጅምላ መቃብሮችን እየቆፈሩ አስከሬኖችን ካቃጠሉ በኋላ ቅሪቶቹን ወዳልታወቀ ቦታ ወስደዋቸዋል (“People belonging to security forces from neighboring Amhara region, which are occupying western Tigray, have been identified as digging up fresh mass graves, exhuming hundreds of bodies, burning them and then transporting what remains out of the regio”, BBC, May 7, 2022)፡፡  ስለዚህም በቢቢሲ ፍረጃ መሠረት ወልቃይት የአማራ ክልል አለመሆን ብቻ ሳይሆን፣ የትግሬነቱ ምንም አጣራጣሪነት የሌለው የምዕራብ ትግራይ አካል ነው፡፡  

የእንግሊዙ ቢቢሲ በዚህ ደረጃ ዓይን ያወጣ ፀራማራ የሆነው ለምንድን ነው?  የዚህ ጥያቄ መልስ የሚገኘው አፍሪቃን ማዕከሉ አድርጎ ጥቁር ብሔርተኝነትን ከሚያቀነቅነው (Africa centered black nationalism)፣ በዚህም ምክኒያት ምዕራባውያን ቅኝናፋቂወች (neocolonialists) በፍቅር ከሚጠሉት (love to hate) ከአማራ ብሔርተኝነት ነው፡፡  

የአማራ ብሔርተኝነት የጦቢያ ብሔርተኝነት ሌላኛው ስሙ ነው፡፡  ምክኒያቱ ደግሞ የአማራ ሕዝብ ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ጦቢያዊነቱን ካማራነቱ የሚያስቀድም፣ ከአረንጓዴ-ቢጫ-ቀይ በቀር ሌላ ዓልማቅ (ዓላማ ሰንደቅ) የሌለው፣  ልጆቹን ጦቢያ፣ ኢትዮጵያ ብሎ የሚሰይም፣ አምላኩን የጦቢያ አምላክ እያለ የሚጠራ፣ በጦቢያ አምላክ እያለ የሚማጸን ጽኑ የጦቢያ ብሔርተኛ ስለሆነ ነው፡፡  የአማራ ሕዝብ ጽኑ የጦቢያ ብሔርተኛ ከመሆኑ የተነሳ፣ የትግሬና የኦሮሞ ጎጠኞች እንዲሁም የነዚህ ጎጠኞች ደጋፊወች የሆኑት ምዕራባውያን ጦቢያን ለማጥላላት ሲፈልጉ የሚጠሯት ያማራ ጦቢያ (Amhara Ethiopia) በማለት ነው፡፡  ለምሳሌ ያህል የኦሮሞ ጽንፈኞች መፈክር ጦቢያ ከኦሮሚያ ትውጣ (Ethiopia out of Oromia) ሲሆን፣ የወያኔ ጽንፈኞች ደግሞ መንጋቸውን የሚቀሰቅሱት ኢትዮጵያዊን ሰላም እንዳትሉ (Donot greet an Ethiopian) እያሉ ነው፡፡  

ሐቁ ግን የዚች ያማራ ጦቢያ የምትባለው ሀገር አብዛኞቹ አስተዳዳራዊና ወታደራዊ መሪወች እንዲሁም ባለስልጣኖች በከፊል ወይም ሙሉ በሙሉ አማራነት የሌላቸው አልአማራ (non-Amhara) ከመሆናቸው በተጨማሪ የአማራ ሕዝብ ከዚች ያማራ ጦቢያ ከምትባለው አገር ያገኘው ኢኮኖሚያዊ ጥቅም አልአማራወቹ ኦሮሞወችና ትግሬወች ካገኙት ጥቅም እጅግ ያነሰ መሆኑ ነው፡፡  የአማራ ሕዝብ ጦቢያን የሚያፈቅራት በል ብሎት ስለሚያፈቅራት እንጅ የተለየ ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ስላገኘባት አይደለም፡፡  ይህን ለመረዳት ደግሞ ጤናንና ትምህርትን ጨምሮ በሁሉም የእድገት መሥፈርቶች ውራ የሆነው የአማራ ነው የሚባለው ክልል መሆኑን መታዘብ ብቻ በቂ ነው፡፡  በሌላ በኩል ግን ባንጻራዊ ደረጃ ከኢትዮጵያ ይበልጥ የተጠቀሙት የኦሮሞና የትግሬ ጎጠኞች ሲያሻቸው ኢትዮጵያን ያማራ ጦቢያ ናት በማለት ባፍንጫችን ትውጣ የሚሉ፣ ሲያሻቸው ደግሞ ጦቢያና በጦቢያ የሚገኝ ነገር ሁሉ የኛ ብቻ እንጅ አማራ የሚባል ሕዝብ የለም የሚሉ፣ ዕይታቸው አለቅጥ የተሳከረባቸው የዕይታ ሰካራሞች ናቸው፡፡ 

የኦሮሞ ጽንፈኛ የሆነው ኦነጋዊው ዐብይ አሕመድ በአማራ ሕዝብ ላይ የጅምላ ጭፍጨፋ ዘመቻ የከፈተው ቢቢሲ እንደሚለው ኢትዮጵያን ከመፈራረስ ለመታደግ ሳይሆን፣ በጦቢያ ፍርስራሽ ላይ የኦሮሞን አጼጌ (Oromo empire) ለመገንባት ብቻና ብቻ ነው፡፡  ዐብይ አሕመድ ጦቢያን አፈራርሶ በፍርስራሿ ላይ የኦሮሞን አጼጌ መገንባት የሚችለው ግን በጦቢያዊነቱ የማይደራደረውን የአማራን ኃይል ከደቆሰ (crackdown) ብቻና ብቻ ነው፡፡  ይህን የአማራን ኃይል መደቆስ የሚችልው ደግሞ ምዕራባውያንን ከጎኑ ካሰለፈ ብቻና ብቻ ነው፣ ወያኔም ሆነ ኦነግ ያለ ምዕራባውያን ድጋፍ የአማራን ኃይል ማሸነፍ አይችሉምና፡፡  ለቅኝ ገዥወች መቅጸፍት መሆኑን በተግባር ያስመሰከረ የጦቢያ ብሔርተኛ በመሆኑ ሳቢያ አማራን አምርረው የሚጠሉት ምዕራባውያን ቅኝናፋቂወች (neocolonialists) ካብይ አሕመድ ጋር በግልጽ በመሰለፍ አማራን መደቆስ የሚችሉት ደግሞ አሳማኝ ምክኒያት ሲፈጠርላቸው ብቻና ብቻ ነው፡፡  ቢቢሲና መሰሎቹ የዘር ጭፍጨፋ ትርክቶችን በባዶ ሜዳ እየፈበረኩ የአማራን ሕዝብ ስም ለማጉደፍ አጭቤ ዜናወችን (fake news) በየዕለቱ የሚነዙት ደግሞ የኔቶ (NATO) ቦንቦች በሰርብያ (Serbia) ሕዝብ ላይ በዘነቡበት ዓይነት፣ በአማራ ሕዝብ ላይ የሚዘንቡበትን አሳማኝ ምክኒያት ለመፍጠር ነው፡፡  

ቢቢሲ የአማራን ብሔርተኝነት ቅጥያጣ ብሔርተኝነት (increasingly strident nationalist movement in Amhara) ያለው፣ ፀራማራው ኦነጋዊ ዐብይ አሕመድ ባንድ ወቅት ያማራ ብሔርተኝነት የኢትዮጵያ ስጋት ነው በማለት የተናገረውን ይዞና ተመርኩዞ ነው፡፡  የአማራ ብሔርተኝነት ግን ሁሉንም ኢትዮጵያውያን በዙርያው በማሰባሰብ የአውሮጳ ቅኝ ገዥወችን አድዋ ላይ አይቀጡ ቅጣት በመቅጣት የኢትዮጵያን ቀጣይነት ያረጋገጠ፣ ቅኝ ገዥወችን ካፍሪቃ አህጉር ሙሉ በሙሉ ጠራርጎ ለማስወጣት በር የከፈተ፣ በመላው ዓለም ለሚገኙ ጥቁሮች የማንነት ኩራት (black pride) እና የጥቁር ብሔርተኝነት (black nationalism) መሠረት የሆነ፣ ያማራ ብቻ ሳይሆን የሁሉም ጦቢያውያን ገንዘብ የሆነ ጦቢያዊ የጥቁር ብሔርተኝነት ነው፡፡  በመሆኑም የምዕራባውያን ቅኝነፋቂወች (neocolonialists) የቱልቀዳ (propaganda) መሣርያወች የሆኑት አውራወቹ መገናኛ ብዙሃን በተለይም ደግሞ የእንግሊዙ ቢቢሲ የለየለት ፀራማራ አጀንዳ ቢያራምድ ምንም አያስገርምም፡፡  የአማራ ሕዝብም ከቢቢሲና ከመሰሉቹ የሚነዛን ማናቸውንም አማራን የተመለከተ ዜናም ሆነ ትርክት መመልከት ያለበት ከጠላት እንደተነዛ አጭቤ ዜና (fake news) ወይም አጭቤ ትርክት (fake narration) ነው፡፡

ቢቢሲንና መሰሎቹን የምዕራብ ሚዲያወች እጅግ አደገኛ የሚያደርጋቸው ቅጥፈትን ኪን (art) ያደረጉ ኪነኛ ቀጣፊወች (artistic liars) በመሆናቸው አያሌ ሰወችን ሊያጭበረብሩ መቻላቸው ነው፡፡  በሌላ አነጋገር የምዕራብ ሚዲያወች የሚነዟቸው አጭቤ ዜናወች ሰፊ ተአማኒነት ሊያገኙ የቻሉት ሚዲያወቹ በአጭቤ ዜናወች ጥርሳቸውን የነቀሉ በመሆናቸው ነው፡፡  ለምሳሌ ያህል የቢቢሲ አጭቤ ዜነኛነት በሕዝብ ድምጽ የተመረጠውን፣ ለኢራን ሕዝብ ጥቅም የቆመውን፣ የኢራኑን ጠቅላይ ሚኒስቴር ሙሐመድ ሞሳዴቅን (Mohammed Mossadeq) አስገልብጦ የምዕራባውያን ቡችላ የሆነውን ሙሐመድ ፓህላቪን (Mohammed Reza Phalavi) በኢራን ሕዝብ ላይ በመጫን ላይ ወሳኝ ሚና እስከተጫወተበት እስከ 1947 ዓ.ም ድረስ ወደኋላ ይሄዳል፡፡  የኛኑ ልጅ እያሱን በ1909 ዓ. ም ለማስገልበጥ አጭቤ ፎቶ (photoshop) በመልቀቅ ከፍተኛ ሚና የተጫወቱት ደግሞ በ1915 ዓ.ም ቢቢሲን የመሠረቱት የጊዜው አጭቤ ዘኔኞች  ነበሩ፡፡  ባጭሩ ለመናገር አጭቤ ዜናን ወልዶ፣ አሳድጎ  ከፍተኛ ደረጃ ላይ ያደረሰው የእንግሊዙ ቢቢሲ (BBC) ሲሆን፣ ያሜሪቃው ሲኤንኤን (CNN) እና መሰሎቹ ደግሞ የቢቢሲ ደቀመዝሙሮች ናቸው፡፡       

በሌላ በኩል ግን ያምባገነኖች ሚዲያወች ቀጣፊወች ቢሆኑም፣ በቅጥፈት ኪን (art of lying) ያልተካኑ ኪነኛ ቀጣፊወች ባለመሆናቸው ምክኒያት ቅጥፈታቸው ዓይን ያወጣ ቅጥፈት ስለሚሆን አጭበርባሪነታቸው እጅግም ነው፡፡  በዚህም ምክኒያት ያምባገነኖች ሚዲያወች አደገኛነታቸው እጅግም ነው፡፡  ለምሳሌ ያህል ያምባገነኑን የዐብይ አሕመድን ኢቲቪ (ETV) የሚያምን ሰው፣ ቲቪው አሳማኝ ሁኖበት ሳይሆን ሰውየው ያየውንና የሰማውን ሁሉ የሚያምን የዋህ ወይም በግ (naive) ስለሆነ ብቻ ነው፡

ምዕራባውያን ኪነኛ ቀጣፊወች ግን ውሸታቸው ዓይን ያወጣ ውሸት ሳይሆን በውነት የተቀባባ ውሸት ነው፡፡  ለምሳሌ ያህል ቢቢሲ ኢትዮጵያን ልትፈራርስ የደረሰች አገር (fractious nation) ሲላት ውነቱን ነው፡፡  ኢትዮጵያን እያፈራረሳት ያለው ያማራ ብሔርተኝነት ነው ሲል ግን ቢቢሲ ውሸቱን ነው፡፡  ኢትዮጵያን እያፈራረሷት ያሉት አግላዮቹ የኦሮሞና የትግሬ ጎጠኝነቶች እንጅ፣ ጦቢያዊነትን የሚያስቀድመው አቃፊው ያማራ (የጦቢያ) ብሔርተኝነት አይደለም፡፡     

Email: mesfin.arega@gmail.com

Filed in: Amharic