>
5:13 pm - Thursday April 19, 4536

የጋዜጠኞችን እስር አስመልክቶ ከኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች ማህበርየተሰጠ መግለጫ...!

የጋዜጠኞችን እስር አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫ…!!!

ከኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች ማህበር የተሰጠ መግለጫ

ሀምሌ 8/2014 ዓ.ም

በዜጎች ላይ የሚፈፀሙ የመብት ጥሰቶችን ካልጻፈ ፣ ካልተናገረና እና እርምት እንዲያገኙ ካልወተወተ ጋዜጠኝነት ለምን ?

በኢትዮጵያ ውስጥ የዜጎች በሕይወት የመኖር መብት  እንዲከበር የሚሠሩ ጋዘጠኞች ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከእሥርና ከእንግልት ባለፈ አፈናና ስወራን የመሰሉ አደገኛ ልምምዶች እየተፈፀመባቸው ይገኛል፡፡

ጋዜጠኞችን በሥራቸው ምክንያት ብቻ የመሰወር፣ የማሰር፣ የማንገላታትና የመደብደብ ድርጊት ተባብሶ ታይቷል፡፡ ጋዜጠኞች በሰውነታቸው ጥፋት አያጠፉም የሚል ድምዳሜ ባይኖርም የሕዝብን ጥቅም ፣ መብት እንዲከበር እና ሙያውን ለማሳደግ ፣ አገር በሕግ እንዲመራ  በሚያደርጉት መሠረታዊ ሥራ የመንግሥት አካል ቁጡ ሊሆን የተገባ አይደለም።

ጋዜጠኞች በሕግ ጥሰት ከተጠረጠሩ እና ተጠያቂነት ካለባቸው ብሎም በወንጀል ከተፈለጉ በሕግ አግባብ መያዝ እና መጠየቅ ሲገባቸው፣ በጸጥታ አካላት በቁጥጥር ስር ውለው  ከቤተሰቦቻቸውና ከባልደረቦቻቸው እየተሰወሩ ቀናትን በጨለማ እንዲያሳልፉ መደረጉ መንግሥት ይህንን ዘርፍ ለማቀጨጭ ፍላጎት ብቻ ሳይሆን ሥራዬ ብሎ የያዘው አስመስሎበታል።

በበይነ መረብ የመገናኛ ዓውታር በዋናነት ሀሳባቸውን ለአድማጭ ተመልካቾቻቸው በማቅረብ ሲንቀሳቀሱ የቆዩት የአማራ ድምጽ ፣ የተራራ ኔትወርክ መሥራችና የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ታፍነው ቆይተው የተለቀቁበት ሁኔታ እጅግ አሳሳቢ እና አስደንጋጭ ነበር።

የፍትሕ መጽሔት ማኔጅንግ ዳይሬክተር ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ በተደጋጋሚ የዋስትና መብቱ እንዲከበር ፍርድ ቤት ቢወስንም ፖሊስ አልፈታም ብሎ ጋዜጠኛው አሁንም በእሥር ላይ ይገኛል፡፡

አሻራ ሚዲያ እና ንስር ሚዲያ የተባሉ የበይነ መረብ የመገናኛ ዐውታር ባለሙያዎችም ለረጅም ጊዜ ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ ቆይተው በኋላም ፍርድ ቤት ቀርበው ሲከራከሩ ከቆዩ በኋላ የአማራ ክልል ፍርድ ቤት በዋስ እንዲለቀቁ ቢወስንም የፌዴራል የፀጥታ አካላት ከባህር ዳር እሥር ቤት ከወጡ በኋላ ወደ አዲስ አበባ እንዲመጡ አድርጓቸዋል፡፡

የኢትዮ ፎረም አዘጋጅ ጋዜጠኛ ያየሰው ሽመልስ በሚኖርበት ቤት ታፍኖ ተወስዶ መለቀቁን ጋዜጠኛው የተናገረው ሀቅ ነው። በተመሳሳይ በቃሉ አላምረው፣ ሰለሞን ሹምዬ፣ መዓዛ መሐመድ፣ መስከረም አበራና ሌሎችም በበይነ መረብ የመገናኛ ዐውታር ሥራቸውን ሲያከናውኑ ለእሥር ተዳርገው ከእሥር ቢለቀቁም ፍርድ ቤት የሚወስናቸው ውሳኔዎች በቅንነት ተግባራዊ ባለመደረጋቸው ምክንያት በተደጋጋሚ ሲንገላቱ እና ሲጉላሉ መቆየታቸው ተስተውሏል፡፡  በተጨማሪም የአልዓይን ኒውስ ጋዜጠኛ አላዛር ተረፈ ሃምሌ 7 ቀን 2014 ዓ.ም በጸጥታ ሃይሎች በቁጥጥር ስር  መዋሉን ማህበራችን ለማወቅ ችሏል፡፡

በኢትዮጵያ ውስጥ ሕግና ሥርዓት እንዲከበር፣ ሕዝብ ከመንግሥት ጋር ተቀራርቦና ተሳስሮ አገርን እንዲያሳድግ ይተጋል ተብሎ የሚታመነው ጋዜጠኝነት ውስጥ መሰማራትና ጋዜጠኛ ሆኖ መሥራት በመንግሥት ከለላና ጥበቃ ማግኘት ሲገባው ድርጊቱ ግን ተቃራኒ እየሆነ መምጣቱን እየታዘብን ነው፡፡ ሕዝብ ግብር እየከፈለበቸው በሚተዳደሩ የሕዝብ መገናኛ ብዙኃን ውስጥ የሚሰሩ ጋዜጠኞችም ቢሆን ብዙዎቹ በፍርሃት ውስጥ ሆነው እንደሚሰሩ ለማህበራችን ይናገራሉ።

በሌላ በኩል እንዳንድ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ጋዜጠኞችንና የመገናኛ ብዙኃን ተቋማትን የአገር ችግር ፈጣሪ አድርጎ የመሳል አዝማሚያ በግልጽ እየታየ ሲሆን ይህም ከንግግር ባለፈ በተግባር እየተስተዋለ ይገኛል። የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ማሕበር በአሁን ወቅት ጋዜጠኞች የሚደርስባቸው ያልተገባ ወከባ እና እንግልት እንዲቆም ይጠይቃል።

ስለሆነም

ፍርድ ቤቶች ጋዜጠኞች በዋስትና እንዲለቀቁ የወሰኑት ውሳኔ በፖሊስ እንዳይተገበሩ መደረጋቸው የተቋሞቹን ታማኝነት ጥያቄ ውስጥ የሚከት በመሆኑ እንዲታረም፣ መንግሥት በጎ ሲሰራ አወድሰው ፣ ጥፋትና ያልተገቡ አካሄዶችን ሲመለከቱ የሚሞግቱትን ጋዜጠኞችን በማሰርና በመደበቅ ፣ በማፈንና በማሸማቀቅ የሚያመጣው ለውጥ ለአገር የማይበጅ በመሆኑ መሰል እርምጃዎች እንዲቆሙ ማህበራን ያሳስባል፡፡

Filed in: Amharic