>
5:13 pm - Monday April 20, 5942

የአማራ ተወላጆች ወደ አዲስ አበባ እንዳይገቡ ስለመከልከላቸው (ባልደራስ)

ወቅታዊ መግለጫ

 

ጉዳዩ፡- 

የአማራ ተወላጆች ወደ አዲስ አበባ እንዳይገቡ ስለመከልከላቸው

 ከዚህ ቀደም በቄሮነት የተደራጁ ወጣቶች በኦሮሚያ የፀጥታ ኃይሎች በመታገዝ  ከአማራ ክልል ወደ አዲስ አበባ የሚጓጓዙትን ተሳፋሪዎችን በየቦታው እያስቆሙ ሲያጉላሉ እንደነበር ይታወሳል።   ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ቋሚ ፀረ-አማራ ፖሊሲ በሚመስል መልኩ ከአማራ ክልል ወደ አዲስ አበባ የሚጓጓዙ  ተሳፋሪዎችን በተለይ ደብረ ብርሃንን ካለፉ በኃላ በኦሮሚያ ልዩ ኃይል አውቶቡሶች እንዲቆሙ እየተደረገ የአማራ ክልል መታወቂያ ያላቸው እንዲወርዱና እንዲመለሱ እየተገደዱ ነው። ሁሉም የሀገራችን ዜጎች በሁሉም የሀገሪቱ ግዛቶች ያለምንም ቅድመ ሁኔታ የመንቀሳቀስ እና ሃብት የማፍራት የመማርና የመኖር ተፈጥሯዊም ሆነ ህገ- መንግስታዊ መብት አላቸው።

ነገር ግን ይህ ሆኖ ሳለ በቅርቡ ከአማራ ክልል ወደ አዲስ አበባ የሚመጡ አማራዎች ምንም ወንጀል ሳይፈፅሙ አማራ ስለሆኑ ብቻ በተረኛው የኦህዴድ መራሹ ብልፅግና  ስርዓት አስፈፃሚዎች ወደ አዲስ አበባ አትገቡም ተብለው  ከፍተኛ የሆነ መጉላላትና እንግልት እንዲሁም በደል እየደረሰባቸው ይገኛል። በመሆኑም ገዥው መንግስት ይህን የአፓርታይድ ድርጊቱን እንዲያቆም ዜጎች  ሰብአዊ መብታቸው ተከብሮ ከቦታ ቦታ ተንቀሳቅሶ የመኖር መብታቸውን እንዲያስከብር እናሳስባለን።  እንዲሁም መላው የሀገራችን ህዝብ ይህን ድርጊት በፅኑ እንዲያወግዝ እየጠየቅን ፓርቲያችንም ጉዳዩን እየተከታተለ የሚያሳውቅ መሆኑን በዚሁ አጋጣሚ እንገልፃለን።

Filed in: Amharic