>
5:13 pm - Wednesday April 19, 8541

የአምሓራ ማህበረሰባችን የመጨረሻው መጀመሪያ የሆነው መንታ መንገድ (ብርሃኑ ድንቁ)

የአምሓራ ማህበረሰባችን የመጨረሻው መጀመሪያ የሆነው መንታ መንገድ

ብርሃኑ ድንቁ


አሁን የሐገራችን ሁኔታ እጅግ በፈጠነና በከፋ መልኩ በኦሮሙማው ቡድን እኩይ እቅድ እጅ ላይ ወድቋል። በተለይ የኣምሓራ ማህበረሰባችን ላይ በቀጥታ በአነጣጠረ  የዘር ጥቃት  ከኦሮሚያ ማጽዳቱን እያገባደዱ በዚህ ያላበቁት ኦሮሙማዎች የሰሜን ሸዋንና የወሎን መሬቶች በከፋ ሠው ጨራሽ በሆነ ጥቃት ለመጠቅለል እንዲያመች የወቅቱን የሰላም ስምምነትን ተገን በማድረግ ማህበረሰባችንን መፈናፈኛ በማሳጣት ላይ ይገኛሉ። ወደፊት፤ የከፋና ምናልባትም ከተቻለ ከምድረ ኢትዮጵያ በችግር፣ በህክምና እጦት፣ በትምህርት የሚጎለብት ትውልድን በማሳጣት፣ በመግደል፣ በማሳመም ገዳይ በሽታዎችን በማሰራጨትና ትክክለኛ ያልሆኑና ጊዜያቸው ያለፈ መድሃኒቶችን በማሰራጨት፣ መሃን በማድረግ ወዘተርፈ  የመጨረሻውንና እረፍት ነሽውን እቅድ እውን ለማድረግ ከወያኔው ጋር መስጥረው እየተደራጁብን ባለበት እጅግ የከፋ ወቅት የእኛ እንደባለጉዳይ ዝምታና የእርምጃ መዘግየት አፋጣኝ እርማትና መስተካከል ተደርጎበት ወደ ሞት ሽረት ትግሉ መግባት ግድ ይላል። በእኛ በኩል እንደ ግለሰብም ሆነ እንደ ቡድን በጋራ፤ ፈጠን ያለና ውጤት ተኮር ሥራ መሠራትና ምላሽ መሰጠት እንዳለበት መታወቅ አለበት። ለዚህም ከዚህ ቀደም ያሉንን ተሞክሮዎችና ዝግመቶች መሰረት አድርጎ በመነሳት ርብርብ ካልተደረገ የመጣንበት መንገድ ዘገምተኛና ወደ ባሰ አዘቅት የሚወስደን በመሆኑ በፈጠነና በበሰለ ርምጃ ብንታገል ለመልካም ውጤት ለመድረስ አንዘገይም። ውጤት ተኮር ሥራን በማሰብ መበርታት፣ መፍጠን፣ መታገል ግድ ይለናል። 

በዚህ በእኛ ዘመን የአምሓራው ችግር  በአብዛኛዎቻችን ዝምታ፣ ቸልተኝነት ወይም በሌላም በሌላ የየግልም ሆነ የቡድን ድክመቶቻችን ገፈቱን በግንባር የሚጋፈጠውንና እየተጎዳ ያለውን ማህበረሳብችንን አሁን ላለበት ሁኔታ ከማጋለጣችን ባለፈ በአሁኑ ሰዓት ማህበረሰባችን በመንታመንገድ ላይ አማራጭ ፍለጋ ላይ እንዲቆም ዳርገነዋል። ይህም አንደኛው አማራጭ፤ የመጥፋትና የመዋጥ ወይም በሌሎች የዓለማችን ሐገራት ተግባራዊ እንደሆነው ለምሳሌ እንደ ኩርዶች በአረብ ሃገራት ተበትኖ መዋጥ፣ ሳሚዎችን በሰሜን አውሮጳ ሐገራት ተበትኖ መዋጥ ወዘተ አሜን በሎ መቀበልና መገደልን ቤት ቁጭ ብሎ መጠበቅ ወይም ሁለተኛው አማራጭ በጥልቀት የተደራጀና ከብዶ አግጥጦ የመጣውን ችግርና ኃይል በአንድ አምሓራነት ብሂል ተጋፍጦ አሸንፎና ህብረትን አሳይቶ ጠላትን አምበርክኮና አስገድዶ በእኩልነትና እና በመከበር ውጤት ለመጭው ትውልድ ለልጅ ልጆቻችን የሚተርፍ ሥራ ለመሰራት ወንዱ ቀበቶውን ሴቷ መቀነቷን አጥብቀው መነሳትን የመምረጥ ሁኔታ ላይ ወድቀናል። ይህም ሲጠቃለል ወይ ዝም ብሎ ቁጭ ብሎ ሞትን፣ መበተንን መጠበቅ ወይም አለበለዚያ ጀግንነቱ በእጁ ነውና ተባብሮ፣ አንድ ሆኖ ጠላቱን አምበርክኮ ወደ ማማው መመለስና በመከባበር መኖር። በጋራ ድካም በቀጣይ ከሌሎች ጋር ኢትዮጵያን መገንባት።

አሁን ለደረስንበት ውጥንቅጥ ችግሮች ያበቁንን ድክመቶቻችንን ብናይ ለውርደትና ለበለጠ ንቀት ዳረጉን እንጂ ምንም ጠብ የሚል ነገር ለማህረሰባችን እንዳላመጣለት እንዲያውም አዘቅት ውስጥ እየጣለው እንደሆነ መርዶ አርጂ አያስፈልገንም።  ከገጠመን ወረርሽኝ በዋናነት ብዛት ቁጥር ያለው የማህበረሰቡ ክፋይ አምሓራው ላይ የሚደርሰውን ሰቆቃ ዝም ብሎ መቀበልና ሐገር እንዳይፈርስ በሚል ደካማ እሳቤና እኛ በዘር አናምንም ኢትዮጵያዊ ነን ስለዚህ መንግስት መፍትሄ ይሰጠናል ብሎ አምሓራውን እንደዘር ሊያጠፋው ከሚፈልግ መንግስት መፍትሄ መጠበቅ ነው። ሌላውና ዋናው ችግራችን ደግሞ ሃገር ቤት ያለውን የአብራካችን ክፋይ ውስን ቁጥር ያለው ዜጋችንን ጠላት በተባዛ የሃሰት ገንዘብ በመግዛት በባንዳነት የሚሰራ አስገዳይ አቃጣሪ ቡድን መፈጠርም ሌላውና ሊናቅ የማይገባው ትኩረት የሚሻ ችግር ነው። ያም ሆነ ይህ ችግር ከዚህ በኋላ ወደቀልባችን ተመልሰን ለውስጣችን ምለን ለማህበረሰባችን ቃል በራሳችን ገብተን የሞት ሽረት ትግሉን በጋራ መጀመር ወይም ከጀመሩ የቁርጥ ቀን ልጆች ጎን መቆም ግድ ይለናል።   መንገዳችን አቀበት አለውና ጥንካሬ ይጠይቃል እንዲሁም ምራቅ ዋጥ ማረግ ያስፈልጋል። አማራጭ የለንምና መደራጀት ይጠበቅብናል፣ መደራጀታችን ትብብር ይፈልጋል፣ በስሜት ሳይሆን ትዕግስት መኖር አለበት፣ ጠላትን መለየት ይጠይቃል፣ ብልጠትም ይፈልጋል። ቆፍጠን ብሎ ጥሶ መውጣት ራስን ማዳን ብሎም ማስከበር ግድ ይላል።  ትላንት ዝም ያልነው ጭረት ዛሬ አመርቅዞ ቁስል ሆኖ አሞናል ስለዚህ ነገ ጋንግሪን ሆኖ ሳይጨርሰን ሊታከም በደንብ ሊወገድ ይገባዋል። በዚህም አልን በዚያ ወደድንም ጠላንም አምሓራ ነን የምንል ሁሉ ትግሉን መምረጥ አለብን፦ ሌላ ምርጫም የለንም ጊዜም የለንም። 

የአምሓራን ጠልነት ከመሰረቱ ማወቅ ለምፍትሄው ይረዳልና ማወቁ ለትግሉ ይረዳል ብየ አስባለሁ። አምሓራውን እዚህ ደረጃ ያደረሰው ምንድነው?

በኤርትራ የተገንጣዮች ቡድን ተጀምሮ በተማሪዎች እንቅስቃሴ እየጨመረ የመጣውና እንዲሁም በሌሎች የትግራይ፣ የኦሮሞ፣ የኦጋዴንና የሲዳማ ነጻ አውጪ ድርጅቶች የሚቀነቀነው የተንሸዋረረ አስተሳሰብ፤ ሰፊውን የአምሓራ ህዝብ እንደገዢ መደብ መውሰድ፣ አማርኛ ቋንቋ የእሱ ብቻ እንደሆነ ማሰብ፣ የኦርቶዶክስ ክርስትና ዕምነትን እሱ ብቻ እንደሚከተል ማሰብ፣ አረንጓዴ ቢጫ ቀዪ ባንዲራ የእሱ በቻ እንደሆነ ማሰብ፣ ነፍጠኛ እሱ ብቻ እንደሆነ ማሰብና ኢትዮጵያ ኢትዮጵያ የሚለው ለሱ ስለሚጠቅመው ነው በሚል የድኩማን አስተሳሰብ ስለሚመሩ አምሓራውን በጠላትነት ከፈረጁት ብዙ ዐመታት ተቆጠሩ። ታዲያ ወያኔ ኢትዮጵያን ሙሉ በሙሉ ከተቆጣጠረበት  1983 ዓም ጀምሮ ይሄ የአምሓራ ጥላቻ እጅግ እያደገ መጥቶ ካለፈው አምስት ዓመት ጀምሮ አምሓራ ከምድረ ገጽ መጥፋት አለብት ብለው ቀን ከሌሊት እየሰሩ ነው። ይሄንንም በኦሮሚያ ውስጥ፣ ደቡብ ክልል ውስጥ፣ ቤኒሻንጉል ውስጥ እንዲሁም የትግራይና የአምሃራ ክልል ጦርነት ጊዜ አይተነዋል።የንቀታቸው ብዛት አዲስ አበባ ውስጥ መኖር እንጂ፣ ልክ እንደ ውጭ አገር ዜጋ፣ ሌላ መብት የለህም ተብሏል። ከአምሓራ ክልል ወደ አዲስ አበባ መግባት አትችሉም ተብሎ መንገድ ተዘግቷል። ከኦሮሚያ ልዩ ዞን ተነስተው አጣዬን ዶግ አመድ እንዲያረጉት ተደርጓል። እዛው አምሓራ ክልል ውስጥ ቅማንት፣ አገው፣ ወዘተ እያሉ አምሓራውን ግደል ብለው አስታጥቀው እያስገደሉት ነው። በወልቃይት ህዝብ ላይ የደረሰውንማ ግፍ ተብሎ ተብሎ ያለቀለት ስለሆነ እዚህ ማንሳት አያስፈልግም።

 ይሄ ሁሉ መከራና ሰቆቃ እየደረሰበት አምሓራው እስካሁን እንደማህበረሰብ የመጣበት መንገድ ቀቢጽ ተስፋና ለጠላቶቹ መሳቂያና መሳለቂያ በሆነ የአህያ ባል ከጅብ አያስጥል እንዲሉ ምንም እርባና ጠብ ባላደረገለትና አምሓራነቱን አስከብሮ ኢትዮጵያዊነቱን ማስረገጥ ሲችል  በጎጥ ደረጃ ወርጄ አልደራጅም፣ እነሱ እሚፈልጉት ይሄንን ነው፣ መደራጀት ያለብን ኢትዮጵያን ያማከለውንም ህብረተሰብ ያቀፈ የፖለቲካ ፓርቲ ስር ነው፣ አክራሪ አንሁን፣ ጽንፈኝነት አገር ያፈርሳልና ሌሎችንም ሁኔታውን ያላገናዘቡ ጮርቃ ሀሳቦችን ይዞ መንገታገቱ አሁን ዝናብ አያንዠቀዠቀ ያለውን ድንኳናችንን አውሎ ነፋሱን ይታደገናል ብለን የመጠበቅ ያክል መጠለያ አልባ የሞት ሞትን ያመጣብናል እንጂ ጠብ የሚል ተስፋ አላየንበትም። ይሄ አስተሳሰብ ነባራዊ ሁኔታን ከግምት ውስጥ አያስገባም አለፍ ሲልም የአስተሳሰብ ድህነት አለው። መሬት ላይ ያለው ኩኔታ እንደሚያሳየን የአምሓራው ጠላት ፈርጀ ብዙ ነው። ሌላውን እንተወውና የራሱ ልጆች ባንዳ ሆነው እያቆሰሉት ነው። እስከ ማውቀው ድረስ ከሌላ ወገን ሆኖ ለአምሓራ ህዝብ ሲከራከር ያየሁት አንድ ታዲዮስ ታንቱን ነው። ስለዚህ አምሓራው መገንዘብ ያለበት እዚህ ደረጃ ላይ የደረሰው በራሱ ተደራጅቶ እንደሌላው ቆሞ ከሁሉም ነገር በፊት እራሱን አለመከላከሉ ነው። ዝንጀሮ እንኳን መጀመሪያ የመቀመጫዬን ብላ የለ።

 የአምሓራው ህብረተሰብ መገንዘብ ያለበት ኢትዮጵያዊነትን ማንም አይሰጠውም ማንም አይነጥቀውም። አገር ደሞ የጋራ ነው። ሃገር ሃገር የሚሆነው ሁሉም ሲጠብቀው ነው። የአምሓራው የግሉ አይደለችም ልትሆንም አትችልም። ኢትዮጵያ አሁን በያዘችው ጎዳና ከቀጠለች እንደ ሃገር እንደማትቀጥል ለመገመት የሮኬት ሳይንቲስት መሆን አይጠበቅብንም። አሁን የተያዘው በአንድ ቋንቋ ላይ ተሞርኩዞ ክልል የመሆን ባህሪ፣ ሆን ተብሎ ሰላም እንዳይኖር እዚህም እዛም ሰው ማረድ፣ የብልጽግና ኢትዮጵያዊ ነኝ የሚለውን ሙሁር ሁሉ በውድም፣ በኮንዶሚኒየምም ሆነ በገንዝብም ባንዳ የማረግ ዝንባሌ፣ አምሓራውን እንደ አርሜንያን፣ እንድ ኩርድ፣ እንደ ጂው ከምድረ ገጽ የማጥፋት ሂደት እንዲሁም ከወያኔ ጋር መታረቅ የሚያመለክተው ሁሉ በስልጣን ላይ ያለው ነፍሰ ገዳይ ቡድን የኦሮሚያን አገር የመመስረቱ ሂደት እንደሆነ ማንም አያጣውም። ታዲያ ይሄ ሀሳባቸው እንዲሳካ እንቅፋት ይሆነናል ብለው እሚያስቡት የአምሓራው ህብረተሰብ ስለሆነ እሱን ከምድረ ገጽ  ማጥፋት ቀዳሚ ተግባራቸው አድርገውት እየሰሩበት ነው።

አምሓራው መገንዘብ ያለበት ይሄ እኩይ ተግባራቸው እውን እንዳይሆን እራሱን ችሎ ተደራጅቶ በመጀመሪያ እራሱን ከእልቂት ካዳነ በኋላና ወደ ቀድሞው ዝናው ከተመለሰ በኋላ ከሌሎች ጋር በእኩልነት በመተባበር ኢትዮጵያን ማዳን ይችላል። ይሄ እራሱን አደራጅቶ በሰላማዊ መንገድም ሆነ በጦር መሳሪያ እርስ በራሱ በጎጥም ሆነ በሀይማኖት ሳይከፋፈል እራሱን የማዳን ተግባር ጊዜ የሚሰጠው ጉዳይ አይደለም ቀድሞ መሰራት የነበረብት ጉዳይ ነበር። ጅማሬው አለ ግን ሁሉም አምሓራ ነኝ የሚል ሁሉ ትኩረቱን እዚህ ላይ ሰጥቶ መስራት ያለበት ጉዳይ ነው። ባጭር ጊዜ ውስጥ ይሄ ካልሆነ ግን በዚህ ነፍሰ ገዳይ መንግስት በተያዘው አካሄድና ከወያኔው የተዳምሮ ቀጣይ እኩይ ተግባር ጋር ከሚመጣው ሲኦለ ምድር መከራራችን ተደራጅተን መመከት ካልቻልን ሌሎቹ ህዝቦች እንደጠፉት ሁሉ እናልቃለን። ትውልዳችን አንገት ደፊ ይሆናል።

 በመጨረሻም ለአምሓራ ህዝብ  ማህበረሰባችን ማስገንዘብ የምፈልገው ተኝተን ከምናየው ህልም ነቅተን ወደ ገሀዱ አለም መግባት አለብን ነው። እስኪ ልጠይቅ ምን ያህል አምሓራ መሞት አለበት በአምሓራ ላይ የሚደረገውን የዘር ፍጅት ለመመከትና ለመታገል? ይሄ ሁሉ አምሓራ በቤኒሻንጉልና በኦሮሚያ እየታረደና ባህሉን ባልጠበቀ ሁኔታ በአደባባይ  በዶዘር ቆፍረው እንደ እንሰሳ የሚቀብሯቸው ወገኖቻችንን እያየን እንዴት ጥቃቱ አይሰማንም? ይሄ ሁሉ ሰው ሲሞት ለምንድነው ለሚሞቱት የሚጮህላቸው የጠፋው? እንዳው ለመሆኑ አምሓራ ክልል ያለው አምሓራ እነዚህን ሰዎች ከሞት ማዳን ካልቻለ ምን ሆነናል? ህዝባዊ ተቃውሞን ለምን ማካሄድ ተሳነው? ሞታችን ካልቀረ ልጆቻችንን የሚታደግ የጀግንነት ሞት ምን አለ ብንሞት? ምኑ ላይ ነው ነገን የመዳናችን? የማህበረሰቡ አባት እናቶች በመሰረቷት አዲስ አበባ አትገቡም ሲባል ምን አይነት ኢትዮጵያን ነው ወደፊት ጠብቀን ዛሬ ስንገደል ዝም የምንለው? የምንፈልጋትን ኢትዮጵያን አብረን ሳናውቅ እያፈረስን ሟችም ሆኖ እርባነ ቢስ ኑሮ ከመኖር መውጣት አለብን። 

ከላይ ለተነሱት ጥያቄዎች መልሱ በቅጡ መደራጀት አለመቻላችን ነው። እራሳችን በመደራጀት እንመን፤ቤተሰቦቻችንን፣ ዘመዶቻችንን፣ ጓደኞቻችንን እንዲሁም የምናውቀውን አምሓራ ሁሉ በአላማው ዙሪያ እናሳምን፣ አብረን እንደራጅና ለማይቀረው የመጨረሻ ፍልሚያ እንዘጋጅ። መንገዱ አንድ ብቻ ነው ትግሉን አቀጣጥሎ ነጻነትን ማውጅ።

ብርሃኑ ድንቁ

ኦስሎ ኖርዌይ

Email: berhanu65@yahoo.com

Filed in: Amharic