>

የዚህን ሰውዬ እንጨት እንጨት የሚል ቀልድ ላለመስማት የት ልሂድ? (ዳግማዊ ጉዱ ካሣ)

የዚህን ሰውዬ እንጨት እንጨት የሚል ቀልድ ላለመስማት የት ልሂድ?

ዳግማዊ ጉዱ ካሣ

የአእምሮ ህመም ዓይነቱና መጠኑ ብዙ መሆኑን የዘርፉ ምሁራን ይናገራሉ፡፡ ወደምሁራን ሰፈር ሳንዘልቅ እኛ የሙያው ባይተዋሮችም በተሞክሮና በተጨማሪ ንባቦች በዚሁ በአእምሮ ህመምና በሌሎችም አካላዊና ሥነ ልቦናዊ(አእምሯዊ) ደዌያት ዙሪያ የማይናቅ ዕውቀት እንደሚኖረን ግልጽ ነው፡፡ ስልሣና ሰባ ዓመታትን በምድር ላይ ኖሬ ስለበሽታዎች ምንነትና ጉዳት አላውቅም ማለት በመሠረቱ ትናንት ኅልውናውን ያገኘውን ዘመናዊ ትምህርት ብቸኛ የዕውቀትና ግንዛቤ ምንጭ ማድረግ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ስህተት ነው፡፡ እንደሚባለው ከሆነ አንድ ሰው 25 መቶኛውን ዕውቀቱን ከትምህርት ዓለም ሲያገኝ 75 መቶኛ የሚሆነውን ደግሞ ከሕይወት ተሞክሮው ያገኛል፡፡

ስለአጠቃላይ አካላዊና መንፈሣዊ የህመሞች ዓይነትና መፍትሔያቸው አሁንና እዚህ አናወራም፡፡ ስለጀመርነውና በአሁኑ ወቅት ሀገራችንን ከሞላ ጎደል በሁሉም አቅጣጫ እያመሳት ስለሚገኘው የአእምሮ ልክፍት ግን በመጠኑ እንዳስሳለን፡፡ እርግጥ ነው መድኃኒቱ ይበልጡን ከታች ሳይሆን ከላይ ነው፡፡

የአንድ ሰው አእምሮ መቃወሱን ወይንም ጤናማነቱ መጓደሉን በምን እናውቃለን?

ይህ ጥያቄ በራሱና መልሱ እንደየመላሹ አስተሳሰብና ፍልስፍና አንጻር ከባድ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ ምክንያቱም የአስተሳሰብ አድማሳችን በተለያዩ ገጠመኞችና የሕይወት ተሞክሮዎች ሳቢያ የአንዳችን ከሌላኛችን በተለያዬ መጠን እምነታችንና አስተሳሰባችን ስለሚለያይ ለዚህ ጥያቄ የምንሰጠውም መልስ ለዬቅል መሆኑ አይካድም፡፡ በዚያ ላይ የሀገሮች ሥልጣኔና ዕድገት፣ የዜጎች ባህላዊና ሃይማኖታዊ እሳቤዎች ከቦታ ቦታና ከሀገር ሀገር መለያየት ወዘተ. በእምነታችንና ግላዊ ፍልስፍናችን ላይ የሚያሳርፈው ጥላ ቀላል አለመሆኑን መረዳት ተገቢ ነው፡፡

የሆነው ይሁንና ከፍ ሲል የተጠቀሰውን አስቸጋሪ ጥያቄ ለመመለስ የብዙኃንን ገዢነት መቀበል ሊኖርብን ነው፡፡ ይህም ማለት አብዛኛው የሚቀበለውን የአእምሮ ጤንነትና በሽተኝነት ሳንወድ በግዳችን ከተቀበልን – ለአብነት ያህል – መቶ ሰዎች ዕብድ ሆነውበት አንድ ሰው ጤነኛ የሆነበትን ጉዳይ ገለባብጠን ዕብዱ አንዱ ሰው እንደሆነ መቶዎቹ ግና ጤናማ እንደሆኑ ልናምን እንገደዳለን እንደማለት ነው፡፡ ሌላ ምርጫ እምብዝም የለንም፡፡ ከብዙዎች አሠራር፣ ከብዙዎች እምነት፣ ከብዙዎች አስተሳሰብ፣ ከብዙዎች የባህል፣ የወግ፣ የታሪክ፣ የሞራልና የዕሤቶቻችን ቅቡል ትውፊታዊ ሥርዓት የሚያፈነግጥ ሰው ስናይ ለአእምሮ ቀውስ እንደተጋለጠ ልንረዳና ወደሥነ አእምሮ ሐኪም ወይም ወደሚቀርበን ጠበል ወስደን ልናሳክም እንገደዳለን፤ ሊያውም ሰውዬው ፈቃደኛ ከሆነ፡፡ ሰውዬው ፈቃደኛ ካልሆነና የሚያሳክመው ዘመድ አዝማድም ከጠፋ የሚያስከትለው ጉዳት ከራሱ አልፎ ለማኅበረሰቡም ይተርፋል፡፡

ሀገራችን በአሁኑ ወቅት በአእምሮ ህሙማን ተጥለቅልቃለች፡፡ የዚህ ህመም ጠንቅ በግለሰብ ደረጃ ቢሆን ዕዳው ቀላል ነው፡፡ ችግሩ የሚጎላው ታማሚው ሰው በሥሩ የሚያስተዳድረው ቤተሰብ ወይም ድርጅታዊ አካል ካለ ነው፡፡ ከዚህ አኳያ በተለይ የሀገራችንን ፖለቲካዊ ድባብ ስንመለከት በከፍተኛ አእምሯዊ ደዌ የሚሰቃዩ ዜጎች ስለተቆጣጠሩት ሀገራችን ጣር ላይ ለመገኘቷ ዋና ሰበብ ሆኗል፡፡ የአእምሮ ጤንነት ደግሞ በተፈጥሮው ፀረ-ዕውቀትና ፀረ-ማስተዋል ነው፡፡ የአእምሮ ህመም ሆድን ሲያሰፋ የማስተዋልንና ትምህርትን በአግባቡ ጨርሶ የመመረቅን ሂደት ያጨናግፋል፡፡ ለዚህም ነው በ1996 ዓ.ም 12ኛ ክፍልን የጨረሰ ሰው በ1994 ዓ.ም ቢኤውን እንደያዘ የምንሰማው፡፡ በአእምሮ ህመም የተለከፈ ሰው የማይጥሰው የምድርና የሰማይ ህግ የለም፡፡ ህገ-ወጥነት የበሽታው መገለጫ ነውና፡፡

ጠቅለል ባለ አነጋገር አእምሯዊ ህመሞችን በሁለት ጎራ ከፍለን ልናያቸው እንችላለን፡፡ እነሱም በራሴው አገላለጽ በውስጣዊ ግፊት መያዝ (obsession/ኦብሴሽን) እና በውጫዊ ግፊት መያዝ (possession/ፖሴሽን) ሊባሉ ይችላሉ፡፡ ኦብሴሽን ማለት ከራስ የውስጥ እጅግ የተጋነነ ፍላጎት መርካት አለመርካት ጋር የተገናኘ በሽታ ሲሆን ፖሴሽን ማለት ደግሞ ከውጫዊ የእርኩስ መንፈስ ቁርኝት ጋር በተዛመደ መልኩ ይበልጡን የክፋት ድርጊቶችን የመፈጸም ዝንባሌ ነው፡፡ ማንም ቢሆን በአንድ ወይ በሌላ መንገድ ከነዚህ በአንዱ ወይ በሌላው ወይም በሁለቱም የመጠቃት ዕድሉ ዝግ አይደለም፡፡ ህመምን በጊዜው ተረድቶ ህክምና ለማግኘት መሞከር ግን ለሁሉም ጠቃሚ ነው፡፡ አለበለዚያ ከነዚህ ህመሞች በአንዱ የተጠቃ ሰው ለምሣሌ እንደሂትለር ወይንም እንደሞሶሊኒ ወይም እንደ አፄ ቦካሣና ኢዲ አሚን ዳዳ አለዚያም ልክ እንደኛው ጉድ እንደ አቢይ አህመድ በሽዎች ለሚቆጠሩ ጂኒዎች ዋሻ ይሆንና አገርን መቀመቅ እስከመክተት ሊደርስ ይችላል፡፡ የአእምሮ ህመም በመሪዎች ላይ ሲከሰት በዘዴ ዘወር ካላደረጓቸው ጣጣው ብዙ ነው፡፡ በአእምሯዊ በሽታዎች ሳቢያ በርካታ ሀገሮች ጠፍተዋል፡፡ ኢትዮጵያም ከነዚህ አገሮች ተርታ ተሰልፋ ግብኣተ መሬቷ እየተጠበቀ የምትገኝ አሳዛኝ ሀገር ሆናለች፡፡ እግዚአብሔር በቶሎ እንዲደርስላትና ቃል የተገባላትን ትንሣኤ ፈጥኖ እንዲልክላት በርትተን እንጸልይ፡፡ 

ከአእምሯዊ በሽታዎች የተወሰኑት እነዚህ ናቸው፡፡ አንድን የሚነገር ነገር በጭፍን ከማመንና በዚያም ላይ ተመሥርቶ ቂም በቀልና ጥላቻን ከመቋጠር የሚመነጭ አእምሯዊ በሽታ፣ በልጅነት በሚደርስ ጥቃት ሳቢያ ውስጥ ለውስጥ እያሸተና እየጎመራ የሚያድግ አእምሯዊ በሽታ፣ ከትውልድ ወደ ትውልድ በዘር የሚተላለፍ የዕብሪት፣ የኩራት፣ የማንአለብኝነት፣ የ“ከኔ በላይ ላሣር” ትዕቢትና ትምክህት፣ “እኔ ከማንም በታች የሆንኩ የማልረባ ፍጡር ነኝ” ዓይነት የበታችነት ስሜት የሚወልደው አእምሯዊ ልክፍት፣ የራስ ወዳድነትና የአልጠግብ ባይ ስግብግብነት በሽታ፣ የመዋሸትና የማስመሰል በሽታ፣ ከእውነተኛው ተጨባጭ ሁኔታ እጅግ ባፈነገጠ መልኩ በምናባዊ ዓለም የመኖርና ሌሎችንም በዚያው የምናብ ዓለም የማስመጥ በሽታ፣ ምንም የሚያስፈራ ነገር በሌለበት ሁኔታ በፍርሀት ቆፈን መቀፍደድና አልባሌ ነገሮችን የማድረግ ደዌ፣ በአንድ ጊዜ የብዙ ሰዎችን የተለያዩ ባሕርያት ተላብሶ ክፉም ደግም፣ ብልጥም ሞኝም የመሆን ሥነ ልቦናዊ አባዜ፣ ወዘተ. በዋነኝነት ሊጠቀሱ የሚችሉ የአእምሮ ህመሞች ናቸው፡፡ ይህ ዘመን ደግሞ የተለዬ ሆኗል፡፡ ዕብዱን ከጤናማው ለመለየት የተቸገርንበት እጅግ ፈታኝና ክፉ ዘመን!!

ስለአቢይ አህመድ የአእምሮ ህመሞች ጎተራ መሆን ብዙ ጊዜ ተነግሯል፡፡ ዋና ተልእኮው ኢትዮጵያን ማፍረስ መሆኑ ሳይዘነጋ ይህ ሰው በዋናነት በ“MPD (Multiple Personality Disorder), delusion, megalomania, ‹Amharophobia›, ‹Ethiophobia›, paranoia, bipolar disorder, pathological lying…” እና በመሳሰሉት ሥነ ልቦናዊና አእምሯዊ በሽታዎች የተጠቃና እነዚህን በሽታዎቹን ለዓለም ሕዝብና መንግሥታት በተግባር ለማሳየት 120 ሚሊዮን ምሥኪንና ከርታታ ዜጎችን ከፈጣሪ የተቸረው “ዕድለኛ” የዐውሬው 666 ልዑክ ነው፡፡ ከሃይማኖት አኳያ አንድ መገንዘብ ያለብን ነገር ደግሞ ከሁለቱ ኃይላት መካከል (ከፖሲቲቭ ኢነርጂና ከኔጌቲቭ ኢነርጂ ማለቴ ነው) አፍራሹን ሚና የሚወክለውና እውን የሚያደርገው ሣጥናኤል የሚባለው ከሃዲ ሲሆን አወንታዊውን ኃይል ተግባራዊ የሚያደርገው ደግሞ ክርስቲያኖች እግዚአብሔር ብለን የምንጠራው የሰማይና የምድር ፈጣሪ ነው፡፡ ትልቁ ጦርነትም የቀረበ ይመስለኛል፡፡

እንግዲህ ኢትዮጵያ በምን እጆች ውስጥ እንዳለች እያየን ነው፡፡ አሁን ሥልጣን ላይ ከሚገኙት የየትኛውም ነገድና ጎሣ አባላት መካከል ለዋናው የአራት ኪሎው ብዔል ዘቡል እስከታዘዙ ድረስ ሚናቸው የሰይጣን ወይንም የአፍራሹ ወገን ነው፡፡ አወንታዊ ኃይል ሰውን በነገዱ እየለዬህ በጥላቻ ፖለቲካም ተመርዘህ ግደለው፣ አሰቃየው፣ አፈናቅለው፣ ቤቱን አፍርሰው/አቃጥለው፣ ቀማው፣ ዝረፈው፣ አሳደው … አይልም፡፡ ይህ ከማንኛውም ዓይነት የብዙኃንን ተቀባይነት ካገኘ ሃይማኖት ያፈነገጠ ዕኩይ ድርጊት መንግሥታዊ ቅርጽ ይዞ እውን ሲሆን ስታይ መንበረ መንግሥቱን የያዘው ሊቀ ሣጥናኤል መሆኑን በግልጽ ትረዳለህ፡፡ የወል መንግሥትነትን ሥልጣን ይዘህ ስታበቃ በ40 እና በ50 ሚሊዮን የሚገመትን ነገድ ከምድረ ገጽ ለማጥፋት ሌት ተቀን መሥራት ዓለማችን እስካሁን ያላየችው መርገምታዊ በሽታ ነው፡፡ በሰይጣን መንፈስ ተይዘው ራሱን ሊገድሉት ለከበቡት ጻፎችና ፈሪሣውያን የራራው ክርስቶስ አሁን ቢመጣ እነዚሀ ደናቁርት ኦሮሙማዎች በሚሠሩት ሥራ ተበሳጭቶ የአባቱን የእግዚአብሔርን ሰውን የመፍጠር የስድስተኛውን ቀን ሥነ መለኮታዊ ክንዋኔ አጥብቆ በተቃወመ ነበር፡፡ አንድዬ ይቅር ይበለኝና ስድስተኛዋን ቀን ብዙም አልወዳት፡፡

በነገራችን ላይ ወያኔና ኦሮሙማ ለአማራ ጨፍጫፊ ጀሌዎቻቸው በጫካም ሆነ በቤተ መንግሥት ውስጥ የሚሰጡት ሥልጠና አንድ ዓይነት ነው፡፡ ይህንን እውነታ ደግሞ ጨፍጫፊዎቹ እጅ ሲሰጡ ወይንም ሲያዙ ከሚናገሩትና ከተግባራቸውም መረዳት ይቻላል፡፡ አንድ ፊደል የቆጠረ “ሰው” በምን ሥሌትና የጥላቻ ፕሮፓጋንዳ ሰክሮ ይሆን ሠልጣኞችን ከፊቱ አሰልፎ እንዲህ የሚላቸው፡- “አማራን ስታገኙ ምንም አትራሩለት! ነፍሰ ጡሯን አማራ ሆዷን ዘርግፋችሁ ጽንሱን ስትፈልጉ ብሉት ወይም ቦጫጭቃችሁ ጣሉት፡፡ ሴት ወንድ ሳትሉ ድፈሯቸው፡፡ አንገት አንገታቸውን ቁረጧቸው፤ ቤት ንብረታቸውን ዝረፉ ወይም አውድሙ፡፡ ከያሉበት አፈናቅሉ፡፡ አማራ እንደሰው የማይቆጠር አህያ ነውና በሉት፡፡ ሰው እንደገደላችሁ አትቁጠሩ፡፡ ለዚህም መንግሥታችንና ክልላችን ከጎናችን አሉ፡፡…” ከዚህ በላይ መረገም ይኖር ይሆን ወገን?

አቢይ በትናንትናው ምሽት ይሁን ቀን አሻንጉሊቶቹን ሰብስቦ መጽሐፉን ያስመርቅ ነበር፡፡ ይህ በራሱ ዓለም የሚኖር የአእምሮ በሽተኛ በአንድ መጽሐፍ ሽያጭ የጎንደርን የፋሲለደስ ቤተ መንግሥትና የሶፎሞርን ዋሻ ሊያሳድስ እንዲሁም በአዲስ አበባ በርካታ ስቴዲየሞችን ሊያስገነባ የነዚህን አካባቢዎች መሪዎችን ወደ መድረክ ጠርቶ እንደሕጻን ይጫወትባቸው ነበር፡፡ ለነገሩ ይልቃል የተባለው የአማራው ክልል መሪ ተብዬ ነው እንጂ መቀለጃ የሆነው ሌሎቹ የኮንቪንስና የኮንፊውዝ ኬኛ ፖለቲካ ድራማ ተዋንያን ስለሆኑ እየሣቁ ማለቴ እየገለፈጡ በትወናው ቢታዩ ለነሱ ምንም ማለት አይደለም – ከዚያ ከጉማሬ አሣሣቅ የተረዳሁትም ይህንኑ ፌዝ ነው፡፡ አቢይ መቼም ቀልዱ አያልቅበትም፤ ለብዙዎቻችን ግን እንጨት እንጨት ካለን ቆየን፡፡ ችግሩ የት እንድረስ? ይህን መሰል የጠነዛ ቀልድ ላለመስማትስ እምን ውስጥ እንግባ? ያገራችን ፖለቲካዊ ዕብድ ደግሞ አጃቢውና አጨብጫቢው  ብዙ ነው፡፡ (“አጨብጫቢ ነኝ” የሚለውን ዘፈን እባካችሁን ተጋበዙልኝ፡፡)

ለማንኛውም ኦሮሙማ በርትቷል፡፡ ኢትዮጵያን ሰልቅጦ ሊውጥ ወይም የዋጠውንም ሳይቀር አንቅሮ ሊተፋ የቀረው ጊዜ ግፋ ቢል ከአሁን በኋላ አራት ወይ አምስት ወራት ብቻ ናቸው፡፡ በነዚህ ወራት ውስጥ የመጨረሻው ፊሽካ ይነፋና ሁሉም ነገር ይለያል፡፡ አዲስ አበባ ከሞላ ጎደል ሁሉም ቦታና ሁሉም ሥልጣንና ኃላፊነት የተያዘው በኦሮሙማዎች ነው፡፡ ይህም የልብ ልብ ሰጥቷቸው አማራን ከአማራ ክልል ወደአዲስ አበባ ላለማስገባት ብቻ ሣይሆን የአማራን ክልል ራሱን በሞግዚት እያስተዳደሩት ይገኛሉ፡፡ ጅል ሰው አያሸንፍህ ወዳጄ፤ ሞኝ አይንገሥብህ ወንድማለም፡፡ ኦሮሚያ ውስጥ ማንኛውም ታጣቂ በፌዴራሉና በክልሉ መንግሥት ቀጥተኛ የበጀት ድጋፍ ሲሰለጥንና ፀረ-አማራ ዘመቻውን አማራ ክልል ድረስ ዘልቆ ሊያፋፍም ዝግጅት ላይ እያለ ተላላኪው የአማራ ክልል መንግሥት ግን አማራ ያለቺውን አንድዬዋን የፋኖ አደረጃጀትም ሊያጠፋ ጥረት ላይ ነው፡፡ ብዙ የሚገርሙ ነገሮችን እያየን ነው፡፡ እኔማ መጨረሻውን ባላውቀው ኖሮ ሦስት ሜትር ገመድ አንጠልጥዬ ወደሚቀርበኝ ዛፍ በሮጥኩ ነበር፡፡ ነገር ግን ዕድሜ ለዕድሜየ ብዙ ነገር ተምሬያለሁና ይብላኝ ለደናቁርቱ ኦሮሙማዎች እንጂ ሀገሬማ ልትነሣና ታላቅቷን ለናቋት ሁሉ ከፍ ብላ ልታስመሰክር ተቃርባለች፤ የፈለግኸውን ብትለኝ ግዴለኝም፡፡ ለዚህ ሁሉ ውጥንቅጥ ችግር የዳረጓት የውጪዎቹም የሥራቸውን ሊያገኙ ጣር ላይ ናቸው፡፡ ስለሀገሬ መጨረሻ የማውቀውን ያህል ጧት የበላሁትን ቁርስ አላውቅም፡፡ ይልቁንስ አማራና አማራውያን ለሁሉም ተዘጋጁ!! ፍልሚያው ቀላል አይደለም፡፡

በአእምሮ ህመም እንደጀመርኩ በዚያው ልውጣ፡፡ በዩቲዩብ፣ በቲክቶክና በመሳሰለው ማኅበራዊ ሚዲያ ከሚጃጃሉ የአእምሮ ህሙማን ተጠንቀቁ፤ ብዙ ናቸው፡፡ ገና ለገና ሣንቲም አገኘን ብለው የሆነ ያልሆነውን በወጣቶች ቋንቋ ልግለጽላችሁና የሚበጠረቁ ብዙዎች አሉና እነዚህን ገስጹ፡፡ አማራ መስለው ስለአማራም የታገሉ መስለው ነገር አማረልን ብለው ሃያ አራት ሰዓት የሀሰትና የጠብ ጫሪ ቱሪናፋ የሚለቁ አሉ፡፡ ከነዚህም አንዱ ሰሞኑን ወዳገር ቤት መጥቶ የዘባረቀውን ሁሉ ሰምተናል፡፡ አሣፋሪ ነው፡፡ ማይምነት ድፍረትን ይሰጣል፡፡ ያበጠ ኪስ አእምሮን ይቀማል፤ ማስተዋልንም ይነሳል፡፡ እጅ መንሻዎች አቅልን ያስታሉ፡፡ ሀገር ደግሞ በገንዘብም ሆነ በመኖሪያ ቤት ስጦታ አትሸጥም፡፡ እንደውነቱ ከአንድ እንጀራ ለማያልፍ ሆድ ይህን ያህል መውረድና መዋረድ ባልተገባ ነበር፡፡ ወዳገር ካልገቡት ውስጥም ተደማጭነትንና በዚያውም የሽቀላ ሣንቲምን ለማግኘት ሲሉ ኃላፊነት ሳይሰማቸው አማራንና ቀደምት የሀገራችንን ነገሥታት ባልተሞረደ አንደበታቸው የሚወርፉ አሉ፡፡ እዩኝ እዩኝ እንዳሉ ደብቁኝ ደብቁኝ የሚሉበት ዘመን ከመምጣቱ በፊት ከአሁኑ ንስሃ ገብተው ትክክለኛ መረጃ ይስጡ፡፡ የአሁን አድማጭና አሸርጋጅ ነገ አይኖርም፡፡ የዛሬ የዩቲዩብ ክፍያ ነገ አገር ስትስተካከል ድርቅ ይመታዋል፡፡ ያኔ አንገትን ከመድፋትና ከማፈር የዛሬ መራብ ብዙ ዋጋ አለውና አሽቃባጮችንና በአፋቸው የሚጸዳዱ የኢንተርኔት ተጧሪዎችን አሁን ምከሯቸው፡፡ ከኦሮሙማ ጋር ተሰልፈው ኢትዮጵያን እየሸጡ ያሉ ሀብታም ነጋዴዎች፣ ጳጳሣት መነኮሣት፣ አርቲስት አክቲቪስቶች፣ ፖለቲከኞች፣ ጋዜጠኞች፣ ሁሉም አደሽዳሽ ሆዳም ይጠንቀቅ፡፡ ሀገርንና ፈጣሪን፣ ፍቅርንና መዋደድን ከገንዘብ እናስቀድም፡፡ ከኔ ከድሃው መማር ይቻላል፡፡ እንዲህ እንደጨለመ አይቀርምና ከታሪክ ትቢያነት ለማምለጥ ሁላችንም አካሄዳችንን እንመርምር፡፡ ዛሬ የሚያሽቃብጥልንና ያልበላንን የሚያክልን ሁሉ ነገ ጊዜ ዘመም ሲል እኛኑ ለማማትና ለማበሻቀጥ ወደባለጊዜው ለመገልበጥም የሚቀድመው የለምና ሁላችንም ወደየኅሊናችን እንመለስ፡፡ ሚዛናዊና አስተዋይ ኅሊና እንዲኖረን መጻሕፍትን እናንብብ፤ የሃይማኖት ሰዎችም እንሁን፡፡ 

በመሠረቱ ሁሉም ነገር አላፊ ጠፊ ነው፡፡ ሞት ቢምርህ ዕርጅና አይምርህም፡፡ በሽታ ቢምርህ ድንገተኛ አደጋ አይምርህም፡፡ ከአሁኑ ዕድሜህ ላይ – ለምሣሌ – 50 ዓመታትን ደምርበት፡፡ ያኔም በሕይወት እንዳለህ ቁጠርና እንዴት እንደምታስጠላና ሞት እንኳን ባቅሙ ምንኛ እንደሚጠየፍህ ገምት፡፡ እኔ በዚያን ጊዜ 110 አካባቢ እሆናለሁ፡፡ በሕይወት እንኳን ብገኝ ውሻ በጨው የማይበላኝ የሰዎች መሣቂያ ነኝ፡፡ እንኳን ያኔ አሁንም እንደዚያው ነኝ ለነገሩ – የዛሬ 30 ዓመት ገደማ በ20ዎቹ መጨረሻ አካባቢ እያለሁ ግን … ምን አስቀባጠረኝ፡፡ ታዲያ ለዚች ዕድሜ ኖሯል በዘርና በጎሣ፣ ባለውና በሌለው፣ በተማረና ባልተማረ፣ በአርሲና በባሌ፣ በወለጋና በጥሙጋ፣ በጎንደርና በሸገር፣ በትግሬና በአማራ፣ በኦሮሞና በአማራ-ጉራጌ …ተቧድነን የምንተረማመሰውና የምንጨራረሰው? በደምብ አስበው፡፡ ለምኑ ብሎ ነው ጫልጪሣ አመንቴ ሞላ ፍላቴን ወዶና ፈቅዶ ባልተወደበት የዘር ሐረግ ምክንያት የሚጠላውና የሚገድለው? የአእምሮ ህሙማንን ስብከትና የዘር ጥላቻ ተከትለን ሺህ ዓመት ቀርቶ መቶ እንኳን በቅጡ ለማንደፍንባት የምድር ዕድሜ በከንቱ የምንጨራረሰው ለምንድን ነው? ትንሽነትን እንዋጋ እንጂ፤ ኢትዮጵያውያን እኮ በታሪክ ታላቅ ሕዝብ ነበርን፡፡ አሁን እንደዚህ የወረድነውና የቀለልነው ለምን እንደሆነ ተገንዝበን ወደጥንታችን እንመለስ፡፡ 

ደግሞስ እግዜር በፈጠራት መሬት እኛ ጠፍጥፈን የሠራናት ይመስል “ይሄኛው የኔ፣ ያኛው ያንተ” ለመባባል ማን ሥልጣን ሰጠን? “ኦሮምኛ ቋንቋ ከአማርኛ ቋንቋ ይበልጣል” እያልን ልጆችን ማስተማሩን ከየት አገኘነው? ስለዓለም ከንቱነት ማስተማር ሲገባው “አዲስ አበባ የኦሮሚያ ናት፤ እደግመዋለሁ፤ አዲስ አበባ የኦሮሚያ ናት” እያለ በሰማይ ቤት የሚገኙ አዳምና ሔዋንን ሳይቀር በሣቅ ጦሽ የማድረጉንስ ምሥጢር ለኦሮሞ ካህን ማን ገለጠለት? በአንዲት የጋራ ከተማ ውስጥ ሁለት ብሔራዊ መዝሙር ማዘመርንና ሁለት ባንዲራ መስቀልን ከየት ተማርነው? ባሏን የጎዳች መስሏት ሰውነቷን በጋሬጣ እንደወጋችው ሴት ሆነን የጤፍን ዋጋ እንደዕንቁ ሰቅለን ሕዝብን በኑሮ ውድነትና በገንዘብ ግሽበት ማሰቃየትን ከየት አመጣነው? በሀፍረት የምንሸማቀቅበት ነገር መብዛቱ!! ግዴላችሁም፤ ኦሮሙማዎች አንጎላችሁን ለመጠቀም ጥቂት አረፍ ብላችሁ አስቡ፡፡ ነገ ሌላ ቀን ነውና ከገባችሁበት የህልም ዓለም በአፋጣኝ ውጡ – ጊዜ ካላችሁ ነው ሊያውም፡፡

Filed in: Amharic