>

እስክንድር ነጋ የዘመናችን  የጽናት ተምሳሌትና ምልክት ነው። 

እስክንድር ነጋ የዘመናችን  የጽናት ተምሳሌትና ምልክት ነው።

 

በሰላሙ ትግል ድልን ተቀዳጅቷል። ጋዜጠኝነትን፣ የሰብዓዊ መብት ተሟጋችነትንና ፖለቲከኛነትን ያለማወላወል ነው የተወጣቸው። ዝንፍ ሳይል። እንደ ሻማ እየቀለጡ ብርሃን መሆን የቻለ ምጡቅ፣ ትሁት፣ ታታሪ፣ፅኑ፣ ጎበዝና ጀግና ነው።  በሃገራችን ውስጥ ባለፉት ሰላሳ ሶስት ዓመታት እነዚህን ሁሉ መስፈርቶች ያሟላው አንድ ሰው ብቻ ነው።  ያም እስክንድር ነጋ ነው። 

 

ግርማ እንድሪያስ ሙላት

እስክንድር ባሳየው ጽናት፣ ትግል፣ በከፈለው መስዋዕትነት ብዙዎችን አነሳስቷል። ‘‘በሰነፎች መካከል ከሚገኝ የገዥዎች ጩኽት ይልቅ የጠቢባን ቃል በጸጥታ ትሰማለች” እንዳለው መጽሐፉ :- እስክንድር በብዕሩም፣ በጸጥታውም ባለፉት ጊዜያቶች ሃገራችን ኢትዮጵያን ተፈራርቀው የገዟትን አምባገነኖች ጩኽታቸውን ሲያስጨንቅ፣ ውሸታቸውን ሲያጋልጥ፣ ቱልቱላቸውን ሲከልልና ሲጋርድባቸው አሳይቶናል። በዚህም ብዙዎችን አነቃቅቷል።

ይሄንን እየጻፍኩ የነጻው ፕሬስ አባላት የነበሩት  የእስክንድርን ወዳጆች ጓደኞችና የስራ ባልደረቦችን በዓይነ-ህሊናዬ ለመቃኘት ሞከርኩ። ”የት ነው ያሉት?… ምን እያደረጉ ነው?… ወዘተ” አልኩኝ።  እስክንድርን የማይወድ፣ የማያከብር፣ አንድም የነጻ – ፕሬስ ሰው እንዳልነበረ አውቃለሁ። የተወሰኑትን ለማነጋገር ሞክሬ ነበር። ስለ እስክንድር ያላቸውን አመለካከት ለማወቅ።

ብዙዎቹ አመለካከታቸውን አለወጡም። ”በአንዳንድ ሓሳቡ ባልስማማም ጽናቱን ድፍረቱን አደንቃለሁ” ብለውኛል። ከፊሎቹ ደግሞ ከነሐሳቡ። አገዛዙን የሚደግፍ ሁሉ የእስክንድርን ሐሳብ ይደግፋል ማለት አይቻልም። ሊሆንም አይችልም። በአንጻሩም የቀድሞው የስራ ባልደረቦቹ ወይም የነጻው ፕሬስ አባላት ከነበሩት ውስጥ ሁለት ሰዎች በተቃራኒው ሚዲያ ይዘው፤ ሲሳይ አጌና ቀስ እያለ ሲጎነትለው፤ የሕብሩ ሃብታሙ አሰፋ ደግሞ፤ ከ”ነጻው ፕሬስ” የወጣ ሰው አልመስል እስኪል፤  ትላንት  እንደመጣ ”ዩቱበርና” ባልቴት ”ቲክቶከር”  ወዳጁን እስኬውን ” ልነጠፍልህ” ሲለው የነበረውን  ጀግናውን ሲዠልጠው ይውላል። ¨አህያ ወደ ቤት ውሻ ወደ ግጦሽ¨ የሆነበት ዘመን ላይ ደርሰናል።

¨ኧረ ወዳጃችን ሃብታሙ አሰፋ ምን ነካው?¨ ብዬ ሰዎችን ጠይቄ  ”እኛም ገርሞናል’‘ ያላለኝ የለም።” ጸጥታ ማንን ገደለ?  ለዛውም ቁጩ!?

እንዲያውም አንድ ሰው:–

”ሃብታሙ ዶርዜ ወይም ጉዴላ ነው። ሆኖም አማራ ሳይሆን፣ የአማራን ጉዳይ በጣም ያቦካል። ያምሳል። የአማራን ጉዳይ በበጎ ጎኑ ማማሰል እንጂ፤ በተቃራኒው ሲሆን ቅናት፣ ምቀኝነት፣ እናም ከጠላት በኩል የግድ ተከፋይነት መኖር አለበት። ሐብታሙ አማራ ጓደኞች አሉት እንጂ አማራ አይደለም። ምነው  አማራ ጉዳይ ላይ እኝኝ አለ?  ኢትዮጵያን ማቀንቀኑ ነበር የሚያዋጣው።” ብሎኛል። ልቦና ይስጠው። ወደ ቀልቡም ይመልሰው .. ከማለት ውጭ ምን ይባላል?

  የነጻውን ፕሬስ አብዬት የጀመሩት እስክንድርና ተፈራ አስማረ  ናቸው ።አስደማሚ ነበሩ።  .በአንድ ጋዜጣ ላይ አንድ ርዕስን ይዞ መውጣት የጀመረው  የነ እስክንድር ኢትዮጲስ ነበረ። ”ትግራይ እስክትለማ ሌላው ክልል ይድማ?” እያለ ይጠይቃል።”አማራ አንድ ቀን ታሪኩን ያድሳል”። ማንም ጋዜጠኛ ያልነካካውን ርዕሰ-ጉዳይ አንገብጋቢና አንኳር ጉዳይ ያነሳል።   ”ውድ ፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ ሆይ ውለታዎ አለብን” ወዘተ… እያለ ጀግናውን በአምባገነኖች ፊት ያወድሳል።  ….አይነኬ ጥያቄዎችን ይዞ ነበር ጋዜጣው ይዞ ብቅ ያለው። ያከታተለው። ያነቃነቀው። ያቀጣጠለው።
እስክንድር በዓላማ፣ የሚንቀሳቀስ ሰው ነው። በዕቅድ የሚኖር ነው። በእርግጥ እየቋጠሩት፣ እየገመዱት፣እያሰሩት እቅዱን ከጉዞው ቀንሰውበት ይሆናል እንጂ፤ አንዳችም አልተጓደለበትም። እየሰበሩት ያልተሰበረ፣ እየመቱት ያልተመታ፤ ሁሌም ብርሃን የሆነ ጀግና ነው። ድሮ የማውቀው እስክንድር ሁሌም እንዳስደመመኝ አለሁ።
”የቀድሞው ውድ ወዳጁ ሲሳይ አጌና…” ብዬ ጀመርኩና አልቀጠልኩም። ትንሽ ልበል። ሲሳይ አጌና ያጫወተኝን ነው የምነግራችሁ። ያን ጊዜ ሁሉም ”አብይ አብይ” ያለ ጊዜ። እስክንድር ግን ”ቆም ብለን እንመልከት እንጂ?፤ እኔ ለውጥ አላየሁም ነውጥ እንጂ” ባለበት ጊዜ።
ሲሳይ አጌና  ነው የሚለኝ:-
”ልዑካን የሚመስል ልዑክ ይዘን እስክንድርን ለማነገገር ሄድን።” ነፍሳቸውን ይማረውና፤ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማሪያም ነበሩበት። ብቻ ምን አለፋህ… ትንሽ ልዑካን ይዘን ሄድን። እናም ”እስክንድር በቃ ይቅርብህ፤ ለውጥ አለ። አብረን ለውጡን እናግዝ። በማለት ተሰብስበን  ያለበት ድረ ስ ሄደን ጠየቅነው። እሱ ግን አሻፈረኝ አለ። ያለምኩትን የዲሞክራሲ ለውጥ በጭራሽ አልተመለከትኩም። ኢሕአዲግ ስም ለውጦ ብልጽግና ብሎ መጣ። አለቀ። እኔ የማውቀው ይሄንን ነው። ለውጥ ትክክለኛ ለውጥ፣ ሰዎች መስዋዕትነት የከፍሉበት ለውጥ አልመጣም። ለሱም እታገላለሁ። የምከፈለውን መስዋዕትነትም እከፍላለሁ። እናንተም አክብራችሁ እኔ ድረስ ስለመጣችሁ እግዚአብሔር  ያክብራችሁ”  ብሎ እንደሸኛቸው ወዳጄ የነበረው ሲሳይ ያኔ አጫውቶኛል።

እስክንድርን የማውቀው በ¨ኦንላይን¨ አይደለም። ሲሳይ አጌናንም።  ሲሳይ አሁን በሚያደርገውና እያደረገ ባለው ከሚያዝኑት ውስጥ ነኝ። ምንም ማድረግ አይቻልም። ሰው የመረጠውን ጎዳና የመከተል መብት አለው። ሌላው ምንም ይሁን ምንም፤  ሰው የሚያምንበትን አቋም ሆኖ ስመለከት  በግሌ እፈልጋለሁ። አጭበርባሪ፣ አድርባይ፣ ሁሉም ጋር የሚጫወት ቀጣፊ ጥሩ አይደሉም።  ሲሳይ የብልጽግና ደጋፊ  ነው። ደጋፊነቱንም ለአብይም የሚከፈለውን መስዋዕትነት ለመክፈል ቃል የገባና ለዚሁም ሜዳሊያ ያጠለቀ ነው። አለቀ።

 ምናልባት ሲሳይ አጌናን ለዚህ ሁሉ ያበቃው ከአብይ ውዳሴ በዘለለ ይሄ ይሆን እንዴ?…
”በሃገር ቤት ቆይታህ ግን፤ ምን  አስደሰተህ ሲሳያችን”  የኔ ጥያቄ ነበር።
”ይገርምሃል!,… በተቀመጥኩበት ”ካፌ” ሁሉ ፈርምልኝ፣ ፎቶ አብረን  እንነሳ የሚለኝ ወጣት ብዛቱ፥ በሰልፍ ሆነው እኮ ነው የምፈርምላቸው። የደነቀኝ ይሄ ነው። ”  የሲሳይ መልስ ነው።
”ሰቅለሃላ”  እኔ ነኝ።
”ቀላል። ይሄን ያህል ወጣቱ የሚከታተለኝ አልመሰለኝም ነበር። በጣም ይደንቃል።” የሲሳይ መልስ ነበር።
በሆዴ ብልጽግና ”እንደ ሮናልዶ ሂዱና ክበቡት፤ እንደ ሜሲ  ፈርምልኝ እያላችሁ አስጨንቁት” ብሎ የላካቸው ካድሬዎች መሆናቸውን እያሰብኩ🙂 (ምክንያቱም በእኛ ሃገር ባህል እንኳን ጋዜጠኛን ዘፋኝን ሲጋፋ የሚውል መሆኑን ስለማውቅ)
ከዚህ በላይ ከ”ወዳጄ” ሲሳይ አጌና ጋር ያወራነውን አላወራችሁም። ይሄንንም ያወራኋችሁ እስክንድርን ከሲሳይ አጌና ጋር  በነጻው ፕሬስ ላይ ለውጣቸውን፣ ጽናታቸውን፣ አሁን ላይ የቆሙበትን ቦታ ለማሳየትና ለንጽጽር ያቀረብኩት ነው።  እስክንድርና ሲሳይ የነበራቸውን ቅርበት የተመለከተ ለጉድ ነበርና። በመታሰራቸው፣ በነጻ ፕሬስ ጉዞአቸውም ወዘተ… ብዙ ቅርበት ነበራቸው።
እስክንድር ነጋ በልጅነቱበግሌ እስክንድርን ለመምሰል የሚሞክሩ ሰዎችን እንጂ የተመለከትኩት፤ በትክክል እስክንድርን ሆነው ያገኘሁዋቸው ሰዎች አላገኘሁም። ይሄዱ- ይሄዱና ያዳልጣቸዋል። ሆድ፣  ወይም ጉድ ላይ ይወድቃሉ።  ጊዜው ከባድ ነው።  በዚያ ላይ በልጅነቱ እያጣ ያደገ ሰው ሲያገኝ አያስተውልም። የተነሳበትን ይረሳል።  አለመታደል ነው። በእጅ የያዙትን ወርቅ ሲቀጠቅጡ መዋል?!….  ልክ አይደለም። በጣም – በጣም ነውር ነው። እስክንድር ወርቃችን ነው። እናም ወርቃችንን መንከባከብ ግድ ይለናል። ከዚህ በላይ እንደሻማ መቅለጥ ከወዴት ይገኝ ይሆን ?
በጋዜጠኝነት ህይወቱ፣ እስክንድር ነጋ የገጠመውን ማንም የነጻው ፕሬስ አባላት አልገጠመውም። በእያንዳንዱ የእስር ወከባውና እንግልቱ ላይ አንድ እናቱና ከወጣትነንታቸው ጀምሮ አብረው የተንገላቱት ባለቤቱ ሰርካለም ፋሲል ነበረች። ሌላው የደፈሩ ወዳጆቹ ነበር በእስር ቤት ቆይታው እንኳን የሚጠይቁት። የእስክንድር ወላጅ እናት ነፍሳቸውን ይማረውና በ እስክንድር ብዙ ውጣ – ውረድን ሲያዩ በዓይኔ በብረቱ ተመልክቻለሁ። የልጃቸውን የት ቦታ እንደታሰረ ለማረጋገጥ ነጠላቸውን በቅጡ ሳያስሩ ሲሮጡና፣ ሲባዝኑ አይቻለሁ።
እስክንድር ነጋ በልጅነቱ⇐
ልጃቸውን የሚያበረቱ ብርቱ እናትም ነበሩ። ፅናትን ”ይወርሱታል፣ ይታደሉታል፤ ይኖሩበታልም። እናትየውም ባለቤቱ ሰርካለምም ከእስክንድር ጋር ባዝነዋል። ተንገላተዋል። አንድያ ልጁን ባለቤቱ የወለደችው በእስር ቤት ውስጥ ነው። ያንንም ልጁን ሊያየው፣ ሊመለከተው ስላልቻለ ”ናፍቆት” የሚል ስም አወጡለት። ስለናፈቀው።
ይሄ ቤተሰብ ላለው ሰው ስይሆን፤ ሰው ለሆነ ሰው ብቻ፤ ከበቂ በላይ የትግል ተምሣሌትነት ነው።

እስክንድር ልዩ ነው። የጋዜጠኞችን ሰደት ያስቆመና ለሌሎች አርአያነትን ፈጥሮ እነ ተመስገን ደሣለኝን ”ትግላችን እስከ ቀራኒዮ”  እንዲሉ ያሰኘ ጀግና።

እስክንድር ነጋ በኢትዮጵያ ውስጥ አገዛዞች አስፍነነዋል እያሉ የሚደሰኩርትን ዲሞክራሲንና ፍትህን እንዳልተገበረ እርቃናቸውን እንዲቀሩ ያደረገ ፅኑ ሰው ነው። እስክንድር ሁሉንም ውሸቶች ዕውነትንና ፈጣሪውን ይዞ ሲጋፈጥ በነጻ አይደለም። እያንዳንዱን እንቅስቃሴውን መስዋዕትነት ከፍሎበታል። እንደሌሎች በገንዘብ፣ በቲፎዞ፣ በአገዛዙ አስተኳኪሾችና፣ ተኳሾች፤ ቲክቶከሮችና ”ተርብ-ግራሞች” (ቴሌግራም) የገነባው ስም አይደለም እስክንድራችን ያለው። የእርሱ ከሁላችንም ይለያል። በክፍለ ዘመን የሚሰጥ ስጦታ።

በሃያ ዕድሜዎቹ የጀመረው አቋሙና ትግሉ አንድ ዓይነት ነው። አይወላውልም። አይልመጠመጥም። አይሽለመጠመጥም። አያቃጥርም። አይፈትልም። በቃ ወንድ ነው። በእርግጥ ብዙ ወንዶች ነበሩ። በነበሩ ያለፉ። ለወራት ይዘመርላቸውና ወይም ለዓመታት ከዚያ ቃየል አቤልን ከገደለው የበለጠ ሴረኛና ደበኛ የሆኑ። ትግሉን የጀመሩት ሳያስቡት፣ ስያልሙት፣ ሳይከነክናቸው ወይም ”የኔ” ብለው ያልጀመሩት ይሆንና፤ በአቋራጭ ባገኙት ፍቅረ- ነዋይ ሲወድቁ ይገኛሉ። እስክንድር ይለያል። ባለፉት አስር ዓመታት ውስጥ ወደ -ኋላ ዞር ብላችሁ ተመልከቱ። ወይም በዓይነ -ህሊናችሁ አስተውሉ። ለአፍታ። ስንቱን ዥዋ -ዥዌ ሲጫወት ትመለከታችሁ። ታዲያ እዚህ ሁሉ ዥዋ- ዥዌ ውስጥ እስኬው የለበትም። እንዲያውም በሰላም እስከመጨረሻው ሄዶ፤ ነገር ግን አሸንፎ ያልተሳካለትን ድል በሌላ ትግል ቀይሮታል። እስክንድር ይለያል።

በትግል ሜዳ አፈርን እፍ ብሎ፣ ውርጭንና ብርድን ተቋቁሞ፤ ረሐብና ጥምን ችሎ፤ ከዚያም መፍትሔው ጋር እደርሳለሁ ብሎ ማሰብና ማድረግ እስክንድርን ብቻ መሆን ይጠይቃል።

እኔ በዚህ አምስት ዓመት ውስጥ ስለፈሉት ኮተቶች አስቤ አላውቅም። ስለ እስክንድር ሳስብ። እስክንድርን መለስ ዜናዊ የሚፈራውና የሚያከብረው ሰው ነበር። እስክንድርን ሃይለማሪያም ደሳለኝ ያከበረው ነበር። እስክንድርን አሳሪዎቹም ገራፊዎቹም ያከብሩትም ይፈሩትም ነበር። ብርሓኑ ነጋ በዓለም ላይ ማንን ትፈራለህ ብትሉት ለሚስቱም ቢሆን የሚነግራት የሚፈራው እስክንድርን ነው። ምክንያቱም ውሽታሞች ዕውነተኛን ይጠየፋሉ። ብርሐኑ ደግሞ ቀጣፊና አጭበርባሪ ነው። ስለዚህም እስኬውን አይወደውም።

አብይ አህመድ:- ”ባልደራስ የሚባል ጨዋታ የምታመጣ ከሆነ ጦርነት እንገጥማለን” ያለው እስክንድርን ነው። እርሱን ተከትሎ ብርሃኑ ነጋ ”ይሄ ባልደራስ ምናምን የሚባል—” ሲል ያላገጠው እስክንድር ላይ ነው። በአምስት ዓመት ውስጥ የፈሉት ዩቱበሮች፣ ቲክቶከሮች፣ ቴሊቪዥኖች፣ መሰረት እስኪይዙ ድረስ ወይም በእግራቸው እስኪቆሙ ድረስ፤ ወይም ለአቅመ ገንዘብ (ሆድ) እስኪበቁ ድረስ የእስክንድር ስም የገቢ ማግኛቸው፤ የእስክንድርን ተግባራቶች ማውራትና ማወደስ የፕሮግራማቸው ግብ-አት ነበረ። የእስክንድር ጽናት ብቻ ነው በዚህ ዘመን ሊገለጽና ሊወደስ የሚችለው።  አለያ ከመቶ ዓመት በፊት መሄድ ግድ ያላል። እንዲህ ያለ ሰው ለማግኘት። ለዚያ ነው እስክንድር ሲያልቅባቸው ቴዎድሮስ ምንሊክ እያሉ ሚያላዝኑት። ስለዚህም የዘመናችንን ወርቅ እንጠብቅ። ተወደደም ተጠላም፤ እስክንድር ነጋ የዘመናችን  የጽናት ተምሳሌትና ምልክት ነው። አበቃሁ። 

እስክንድርን ባለበት ሁሉ እግዚአብሔር እንዲጠብቀው የዘወትር ጸሎቴ ነው።

 

ግርማ እንድሪያስ ሙላት

www.ethioreference.com

Email:⇓

ethreference@gmail.com

girma077@gmail.com

 

 

 

 

 

Filed in: Amharic