>

የኢፍትሃዊነትን ታሪክ የዃሊት [በዳዊት ሰለሞን]

Andualem-Eskindir-300x165ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋና የትውልድ ተጋሪው ፖለቲከኛ አንዷለም አራጌ ስርዓቱ የአረቡ አለም አይነት አብዮት ተቀስቅሶበት መጨረሻው እንደ ቓዳፊ ከአይጥ ጉድጓድ ተጎትቶ መውጣት እንዳይሆን ስልጣኑን እንዲያስረክብ በገሃድ ወጥተው ሲወተውቱ ቆይተዋል። አንዷለም መድረክ እየመራ እስክንድር በአንድነት ፓርቲ ቅጥር ግቢ ተገኝቶ ሐሳቡን አካፍሏል።ዝግጅቱ በፍኖተ ነጻነትና በአዲስ አድማስ ጋዜጦች ጭምር ማስታወቂያ ተሰርቶለት በይፋ የተደረገ ቢሆንም አፋኙ ቡድን ልክ በህቡዕ የተደረገ በማስመሰል የአደባባዮን በፖሊሶቹ የምርመራ ጥበብ የተቀረጸ ቪዲዮ በማስመሰል ለካንጋሮው ፍርድ ቤት ቆራርጦ አቀረበው።

በዛሚ ሬዲዮ ከስቱዲዮው በላይ የምትስቀው ትልቋ ሚሚ “ለምን አንዷለምና እስክንድር አይታሰሩም፣ የመንግስትስ ሆደ ሰፊነት እስከመቼ ነው?”በማለት ዘበዘበች። ልክ በዛሬው ዕለት 14 sep 2011 አንዷለም ልጁን ት/ቤት አድርሶ እንደተመለሰና የመጀመሪያ ልጁ ከመጀመሪያው የት/ቤት ውሎው ሲመለስ ምን እንደሚለው ለመስማት እንደጓጓ የጸረ ሽብር ግብረ ሀይል አባላት ነን ባሉ የስርዓቱ ቅጥረኞች በቁጥጥር ስር መዋሉ ተነገረው።

ጋዜጠኛ እስክንድር በአሜሪካን አገር ከሁለተኛ ደረጃ እስከ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ዘልቆ የተማረ የተንደላቀቀን የስጋ ኑሮ እንደ ሙሴ በመግፋት የህዝብ ልጅ ለመሰኘት ሸገር የከተመ ነው።ከኢትዮጲስ ጋዜጣ ጋር ወደ ህትመት ሚዲያው የዘለቀው እስክንድር ከሞያው ጋር በተያያዘ ለ15 ጊዘያት እየታሰረ ተፈትቷል። አንደኛውኑ እዚያው እስር ቤት ለምን ክፍል ስጡኝ አትላቸውም እያሉ ጓደኞቹ ይቀልዱበት የነበረውን እስክንድርን አምባገነኖቹ ብዕሩን ለመንጠቅ በማሰብ የህትመት ፈቃድ ከመከልከል አልፈው ከአሁን በዃላ አንተን ማሰር ስለሰለቸን እንገድልሃለን በማለት ነግረውታል። የሞያ አጋሩና ለአፍታ በየትኛውም ውሳኔው ከጎኑ የማትነጠለውን ባለቤቱን Nafkot Eskinderን ነፍሰ ጡር እንዳለች በማሰርም የእስክንድርን አቋም ለማስለወጥ ሞክረዋል።ፍጹም በማይመች ሁኔታ ውስጥ የነበረችው ሰርካለምም ናፍቆትን ተገላግላለች። ናፍቆት የተሸከመው ስም እስክንድርና ሰርካለም የቃተቱለት፣ሽብርተኛ ተብለው የታደኑለት ፣ሌሎች መሰሎቻቸው የሞቱለትና የተሰደዱለትን ብሩህ ቀን የሚያመለክት በመሆኑ ናፍቆት የእስክንድርን ህልም የሚጋሩ ሁሉ ልጅ ነው።

እስክንድር በዛሬዋ ዕለት ከልጁ ጋር በመኪናው እየሄደ ነፍጥ ባነገቱ ቅጥረኞች ሽብርተኛ ተብሎ ወህኒ ወርዷል። በወህኒ የተወለደው ናፍቆት በአባቱ ሁለት እጆች ካቴና ሲጠልቁለት ተመልክቷል። በእርግጥ ናፍቆት ለአባቱ ስራ እውቅና በመስጠት ታላላቅ ተቋማት በታላላቅ መድረኮች ሽልማት ሲያበረክቱለት በመመልከቱ ካቴናው በአገሩ እንደ ነቢይ ባለመታየቱ የተደረገለት እንጂ አባቱን እንደማይመጥነው ይገነዘባል። እስክንድርና አንዷለም በቅጥረኞቹ የቀረቡባቸው ክሶች በፖለቲካዊ ውሳኔ ፍርድ የተሰጡባቸው መሆናቸውን ለማወቅ ስራዎቻቸውን መለስ ብሎ መቃኘት ይገባል። እስክንድር ለሰበር ሰሚ ችሎት አቅርቦት የነበረው ጉዳይ በችሎቱ ታይቶ ዳኛው የቀድሞውን ውሳኔ ሲያጸኑ በችሎቱ ተገኝታ የነበረችው ሰርካለም አጋቾቹ እየሰሟት “እስክንድር አንተ ጀግና ነህ። በፍጹም እንዳታዝን እውነት ነጻ ታወጣሃለች።አንተ ወንጀለኛ አይደለህም “ብላው ነበር። የሰርካለም ድምፅ ዛሬም ድረስ በህሊናዬ ያስተጋባል ።እስክንድር አንተ ጀግና ነህ!!!!”

Filed in: Amharic