>

መሬት አስረክቦ ትዕግስት - እግር እያስበሉ ዝምታ ...!!! (አባይነህ ካሴ)

መሬት አስረክቦ ትዕግስት – እግር እያስበሉ ዝምታ …!!!

አባይነህ ካሴ

የሱዳን ኃይል በተጠናከረ ሁኔታ ወደ ኢትዮጵያ ድንበር እየተስፋፋ መኾኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ አስታወቁ። የሱዳን ሀይል ስምምነቶችን ባለከበረ መንገድ  ቦታዎችን እየተቆጣጠረ ነው ብለዋል ።
ኢትዮጵያ  ቀጠናውን የማተራመስ ፍላጎት በመኖሩ  ችግሩ በንግግር ብቻ እንዲፈታ በትዕግስት እየሰራች ነው ብለዋል።
ነገሮች መፍትሔ የማያገኙ ከሆነ ግን ትዕግሥት ገደብ ይኖረዋል ብለዋል ቃል አቀባዩ።
አምባደሳደር ዲና ሙፍቲ “ጦርነት አያስቸኩልም፣ አፍንጫህን የመታህን ወዲያውኑ አፍንጫውን ላትመታው ትችላለህ ፤ ሌላ ጊዜ ግን አንገቱንም ልትቆርጠው ትችላለህ።…ትዕግስታችንን እንደ ፍርሀት አትቁጠሩት” በማለት ስለሱዳንን ወረራ ተናግረዋል።
ወዳጄ እግር እያስበሉ ዝም በሉ ማለት ፍርሃት እንጅ ሌላ የዳቦ ስም የለውም። መሬት አስወርሮም ትዕግስት የሚባል የለም። የተደፈረው የሀገር ዋናው ውቅር ሉዐላዊነት (soverignity) ነው። ዳር ድንበር ተጥሶ ትዕግስት አይባልም። እንዲያው በዳቦ ስም አለቅን እኮ!
ከእግዚአብሔር በላይ ታጋሽ ማን ነው? እርሱ ግን የማይታገስበት ጉዳይ አለ። እግዚአብሔር በመለኮቱ ጎልማሳ በሚስቱ አይታገሱም። ትዕግስት ካለቦታው ሲጠቀስ ፍርሃት ወይም ሽንፈት ይኾናል። የግለሰብ አፍንጫ ሲመታ መታገስ ዋጋ አለው። የኢትዮጵያ አፍንጫ ሲመታ ግን ትዕግስት ብሎ ነገር አይሠራም።
ባይኾን ሌላ ጦርነት ላይ ስለሰነበትን መዘጋጀት ስላለብን ነው ቢሉ ሰሚ ያገኛሉ። ሉዐላዊነት ተደፍሮ ትዕግስት ማለት ቀልድ ነው።
Filed in: Amharic