admin
እልልታ የዋጠው እሪታ ….!!! (አሳዬ ደርቤ)
እልልታ የዋጠው እሪታ ....!!!
አሳዬ ደርቤ
*.. የሰኔ 15ቱም ግድብ እንዲህ ተከትቧል!!
......ከእልህ አስጨራሽ ሕዝባዊ ተጋድሎ በኋላም “የአማራ ሕዝብ ገዳይ ህው፥ሓት መሆን አለበት” የሚለው የእነ በረከት ቡድን...
ባልደራስ ጠቅላላ ጉባኤውን በአንድ ወር ማራዘሙን አስታወቀ…!!! (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)
ባልደራስ ጠቅላላ ጉባኤውን በአንድ ወር ማራዘሙን አስታወቀ...!!!
ኢትዮጵያ ኢንሳይደር
ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ ከ12 ቀናት በኋላ ሊያካሄደው የነበረውን ጠቅላላ ጉባኤ ወደ መስከረም ወር አራዘመ። ፓርቲው የጠቅላላ...
ባልደራስ በመግለጫው ስለ ወደፊት የትግል መስመር አቅጣጫ አስቀመጠ….!
ባልደራስ በመግለጫው ስለ ወደፊት የትግል መስመር አቅጣጫ አስቀመጠ....!
ሰለሞን አላምኔ
*.. ባልደራስ ከዚህ በኋላ በ“ፖለቲካል አክቲቪዝም” ላይ ማተኮር እንዴለለበት ተመላክቷል።
*.... ለጉራጌውም በክልል እንዲደራጅና ራሱን በራሱ የማስተዳደር መብቱ ሊከበርለት...
ደብረ ማርቆስን በጨረፍታ (ፀሐፊ- ጌታ በለጠ ደበበ)
ደብረ ማርቆስን በጨረፍታ
ፀሐፊ- ጌታ በለጠ ደበበ
ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ደብረ ማርቆስ ከተማ የመጣሁት መስከረም 17 ቀን 2007 ዓም ነው። የፀደይ ወቅት የመጀመሪያው ወር የሆነው መስከረም መጥባቱን ለመመስከር ሰማዩ ጥርት፣ምድሩ ፍክት ብሏል። በአዱስ ዘመን ሁሉም አዲስ ተስፋ ሰንቋል። ትምህርት ቤቶች ተማሪዎች ለመቀበል በዝግጅት ላይ ናቸው። የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በራዴዮ፣ በቴሌቪዥን ተማሪዎቻቸውን መጥራት ይዘዋል። ንብረትናቷ የአባቴ አገልግሎቷ የእኔ የሆነች "ፍሊፕስ" ራዲዮ እንደጆሮ ጉትቻ ከጆሮዬ አትለይም። አንድ ቀን ዜና ከመናገሯ አበክራ ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ የመጀመሪያ ዓመት ተማሪዎችን መጥራቱን ነገረችኝ። አመሰገንኋት።
አሁን ለጉዞ ዝግጅት ላይ ነኝ። የገጠር ልጅ እንደመሆኔ ጎረቤት ተሰብስቦ ቡና ተፈልቶ፣ ያለው ሳንቲም የሌለው ምክር ሰጥቶኝ ነው የተሸኘሁት። የማስታውሰው አጎቴ አስር ብር፣ አክስቴ አምስት ብር፣ የክርስትና አባቴ 50 ብር እና አባቴ ትቂት ብር ሲሰጡኝ አያቴ "የገጠር ልጅ ተስፋው ትምህርቱ ነው፥ ጠንክርውህ ተማር" ብሎኛል። ከጓደኞቼ ጋር ዘግይተን በመነሳታችን ደብረ ማርቆስ የገባነው ከመሸ ነበር። "ከመሸ በኋላ በታክሲ መኼድ ለደህንነትም ለኢኮኖሚም አስጊ ነው" ስለተባልን ከከተማው መነኻሪያ ወደ ዩኒቨርሲቲው የገባነው በእግራችን ነበር።
አብረውኝ የመጡ ሴት ተማሪዎች ተቀባይ ስለነበራቸው ተለይተውኝ ወደ ህንፃቸው ሲኼዱ ብቻዬን ቀረሁ። በእውነቱ ከሆነ ከፋኝ። ድሮ እኮ ከመሸብን አብረን ነበር የምናድረው። ወዲያው አንድ የማስታወቂያ ሰለዳ አንብቤ ህንፃ 20 ላይ መመደቤን ባውቅም ህንፃው ያረፈበትን መሬት ማግኘት አልቻልሁም። አዲስ (ፍሬሽ) ተማሪ ተቀብሎ ለመጥበስ ከወዲያ ወዲህ ሲኳትን ያገኘሁትን አንድ የጤና ተማሪ ህንፃ 20 ያለበትን እና የተመደብሁበትን ቤት ያሳዬኝ ዘንድ ተማፀንሁት። ሰውዬውም ለወደፊቱ ቤት ሳይሆን ዶርም መባል እንዳለበት መክሮ እየጎተተ ወስዶ ዶርሜ ውስጥ አስገባኝ። (በወቅቱ ቀድመን የተጠራን አዲስ ተማሪዎች ብንሆንም የጤና ተማሪዎች በግቢው ነበሩ)።
በአንድ ጠባብ ክፍል ውስጥ ለስድስት መኖር ተጀመረ። የዶርም ደባሎቸን ተዋውቄ በፌስታል ከያዝኋት ቆሎ ቀምሼ ተኛሁ። ነጋ። ከተማሪዎች ጋር ለመላመድ ጊዜ አልወሰደብኝም። ብዙ ሴት እና ትቂት ወንድ ጓደኞችን በዙሪያዬ አደረግሁ።
የንጉስ ተክለሃይማኖትን ቤተ መንግስት ለመጀመሪያ ጊዜ ያዬሁት ለአዲስ ገቢ ተማሪዎች የሚሰጠውን የአንድ ቀን ስልጠና በከተማው ውስጥ በወሰድሁ ዕለት ነው። ግሩም ነው። የንጉሱን ታሪክ በስሱ አውቀው ነበር። ንጉስ ተክለሃይማኖት የልጅነት ስሙ አዳል ተሰማ ነበር። አዳል ተሰማ እናቱ ወይዘሮ ምዕላድ ስትባል የአፄ እስክንድር ዘር ናት። አዳል የአባቱ የዘር ሃረጉ የሚመዘዘው ከጎጃሙ ልዑል ዮሴደቅ ወልደ አቢብ እና ከጎንደሯ ንግስት ዳግማዊት ወለተ እስራኤል ነው።
ባሻዬ! ተከተለኝማ ግሩም የሆነውን የአዳል ተሰማ ውልደትና ዕድገት ልንገርህ። ታላቁ ዮሴዴቅ በአንድ ወቅት ለያዥ ለገናዥ ያስቸገረ ሆነ። ያኔ ጎንደሮች "ይኼንን ጉልበተኛ በጋብቻ ጉልበቱን እናብርደው" ብለው በማሰብ ዳግማዊት ወለተ እስራኤል የተባለች ቆንጆ ዳሩለት። እንደታሰበውን ዮሴዴቅ ጊዜውንም ጉልበቱን ዳግማዊት ወለተ እስራኤል ላይ አደረገ። ሙሽሮች ትዳራቸው ሰምሮ ታላቁ ራስ ኃይሉ ዮሴዴቅን ወለዱ። ታላቁ ራስ ኃይሉ ወይዘሮ ድንቅነሽ እና ደጃዝማች መርዕድን ወለዱ። መርዕድ ከፊሉን ጎጃም ሲያስተዳድር ወይዘሮ ድንቅነሽ ለዳሞቱ ባላባት እና አስተዳዳሪ ደጃዝማች ዘውዴ ተዳረች።
የወይዘሮ ድንቅነሽ ባል ደጃዝማች ዘውዴ የመርዕድን ግዛት በኃይል ነጥቆ የማስተዳደር ሃሳብ መጣለት። ለዚህም "ግጠም ግጠም" የሚል ከዬት እንደመጣ ያላወቀው ጀብደኝነት ተሰማው። ደጃዝማች መርዕድ ግን የዋዛ አይደለም፥ ነገሩን ቀድሞ ሰምቷል። ደጃዝማች መርዕድ ታዲያ አምቻውን( የእህቱን ባል) ማሰር ፈለገና "እህቴን ድንቅነሽን ይዘሃት ናና ልያት" ሲል ላከበት። ዘውዴ ሚስቱን ከኋላው አስከትሎ "ከተፍ" አለ። መርዕድ ዘውዴን ቀራኒዮ አካባቢ አንድ ዋሻ ውስጥ ወስዶ በግዞት አስቀመጠው። ደጃዝማች ዘውዴ ሥልን በሚስቱ ናፍቆት ተንገበገበ፥ ተቀምጦም ተኝቶም ድንቅነሽ ብቻ ማሰብ ሆነ ስራው። ሲጠናበት "ኮሶ ታምሜያለሁና ሚስቴ መጥታ መድሃኒቱን ትጋተኝ" ሲል ደጃዝማች መርዕድን ተማፀነ። ደጃዝማች መርዕድ ድንቅነሽን ላከለት። ተላቅሰው ተቃቀፉ፥ የናፈቀ ሰው ሊያደርግ የሚችለውን ሁሉ አደረጉ። መሽቶ መንጋትን ረገሙ፥ መለያየትን ጠሉ፥ አብሮነትን ከልባቸው ተመኙ። ወይዘሮ ድንቅነሽ በልቧ ትዝታዋን በማኃፀኗ ጎሹን ይዛ ወደ ደብረ ማርቆስ ተመለሰች። ወይዘሮ ድንቅነሽ ከዘጠኝ ወራት በኋላ ጎሹን ወደምድር አመጣችው። አደገ። አገባና ተሰማን ወለደ። ተሰማ ወይዘሮ ምዕላድን አግብቶ አዳል ተሰማን ወለደ።
አዳል ተሰማ ጎርምሶ ከቤት እስከሚወጣ ድረስ ያደገ ከቀድሞው የጎጃም ገዥ እና የደብረ ማርቆስ ከተማ መስራች ደጃዝማች ተድላ ቤት ነው።ደብረ ማርቆስ እንዴት ተመሰረተች የሚል አይጠፋምና ነገሩ እንዲህ ነው። ደብረ ማርቆስ ከተማ “ደብረ ማርቆስ" ከመባሏ በፊት ሁለት የሳርን ልጆች (ዝና እና መንቆረር) ይኖሩባት ነበር። ደጃዝማች ተድላ ጓሉ መንቆረር የሚለውን ስም እንደያዘች የመንግስታቸው መቀመጫ ትሆን ዘንድ መረጧት ። ደጃዝማች ተድላ ጓሉም ህይወታቸው እስከ አለፈበት ህዳር 6 ቀን 1860 ዓ/ም ድረስ መቀመጫቸውን መንቆረር አድርገው ገዙ።
በነገራችሁ ላይ ደጃዝማች ተድላ ጓሉ ጠንቃቃ ቤተክርስቲያን ሳሚ እና ሩህሩህ ነበሩ። ቤተክርስቲያን በማሰራት የታወቁ ናቸው። እሁድ ከቤተክርስቲያን አይቀሩም። የሞቱ ጊዜ ሞታቸው ለሰፊው ህዝብ ተደብቆ በድብቅ ነበር የውሽ ሚካኤል የተቀበሩት። ህዝቡ ግን ጭምጭምታ ሰምቶ ስለነበረ እንደዚህ አለ።
አልሞተም ይሉናል ደጃዝማች ተድላን
አሁን እሑድ ሲቀር የምናዬውን።
የደጃዝማችን ሞትን ተከትሎ ስልጣን የያዘው ልጅ ደስታ ተድላ በወቅቱ ከነበረው የኢትዮጵያ መሪ አፄ ተክለጊዮርጉስ ሊስማማ አልቻለም። አፄ ተክለጊዮርጊስ ነገሩን በጋብቻ ማብረድ ፈልገው ልጃቸውን እንዲያገባ ቢለምኑትም አሻፈረኝ አለ። በዚህ ጊዜ ብልሁ አዳል ተሰማ አጋጣሚውን ተጠቅሞ ከአፄ ተክለጊዮርጊስ ጋር ተወዳጀ። የአፄ ተክለ ጊዮርጊስ እህት የሆነችውን ወይዘሮ ላቀች ገብረ መድኃንን ላፍ አድርጎ ሚስት አደረገ። አጤ ተክለጊዮርጊስ ለአዳል ተሰማ መጀመሪያ ደጃዝማች፣ በኋላ ራስ የሚል ማዕረግ ጨመሩለት። አጤ ተክለጊዮርጊስን በአፄ ዩሐንስ ሲተኩ አዳል ተሰማ የሚለው ስም ተቀይሮ ንጉስ ተክለሃይማኖት ተባለ። ከዚህ በኋላ አንቱ እያልሁ እቀጥላለሁ። ንጉስ ተክለሃይማኖት በ1872 ዓም የጎጃም እና የከፋ ገዥ ተብለው ነገሱ። በንግስናቸው ወቅት ቅዱስ ማርቆስ ቤተክርስቲያን በከተማው አሰርተው የከተማይቱ ስም መንቆረር መባሉ ቀርቶ ደብረ ማርቆስ እንዲባል አስደረጉ።ንጉሱ ያሰሩት የቅዱስ ማርቆስ ቤተ ክርስቲያን ከንጉሱ ቤተ መንግስት በስተሰሜን አቅጣጫ በቅርብ ርቀት የሚገኝ ሲሆን ፎቶው ከስር ተያይዟል። ከተማይቱ እስካሁን ደብረ ማርቆስ ትባላለች። እኔ አንዳንዴ ዴንማርክ እላታለሁ።
መሞት ከአዳም የወረስነው ነውና ንጉስ ተክለኃይማኖት ታመው ጥር ሦስት ቀን 1893 ዓ/ም ደብረ ወርቅ ማርያም ሞቱ። አስክሬናቸው ወደ ደብረ ማርቆስ መጥቶ ራሳቸቸ ባሰሩት የቅዱስ ማርቆስ ቤተክርስቲያን አረፈ። ሚስታቸው ወይዘሮ ላቀች ገብረ መድኃን እጅጉን አዘነች::
ልጃቸው ደጃዝማች ስዩም( ራስ ኃይሉ) እንዲህ አለ።
በተድላ በጎሹ ያልነበረ ነገር
በከርሰ መቃብር ከአቡን መነጋገር"
ይኼንን ማለቱ ንጉሱ የተቀበሩት ከጳጳሱ አቡነ ሉቃስ ጎን በመቀበራቸው ነው። ራስ ኃይሉ ማለት ከንጉሱ ሞት በኋላ የጎጃም ገዥ የነበረ በጣም ሃብታም ሰው ነበር። የሚታወቀውም ከፍተኛ ግብር በመሰብሰብ ነበር። ጭስ የሚጨስባትን እያንዳንዷን ጎጆ እያስቆጠረ ግብር ያስከፍል ስለነበር በጎጃም ሚስት ያገቡ ወጣቶች ጎጆ አይወጡም ነበር:: እናም አንድ ወጣት እንዲህ ሲል ብሶቱን ገልጿል።
ጎመኔን ቀንጥሼ ጥሬውን በላሁት
እንዳላበስለውም የጢሱን ፈራሁት።
ዶክተር ታደለ ገድሌ የተባሉ ፀሐፊ "ቅኔና ቅኔያዊ ጨዋታ ለትዝታ" በሚል ርዕስ በፃፉት መፅሐፍ ያነበብሁትን አንድ ቀልድ ልጨምር። ራስ ኃይሉ በጣም የሚወዱት ባለሟል ነበራቸው። እንደሌሎቹ ሰዎች ስልጣን ሰጥተው እንዲርቅ ስላልፈለጉ "ዛሬ ሹመት ልሰጥህ ነበር እግዚአብሔር ሳይፈቅድ ቀርቶ ለባላንባራስ...ለፊታውራሪ....ለግራዝማች.... ለቀኝአዝማች እገሌ ሰጠሁት" እያሉ በየጊዜው ይነግሩታል። ባለሟሉም ካሁን አሁን እግዚአብሔር ፈቅዶ ስልጣን ይሰጡኛል ብሎ ደጅ ቢጠናም " እግዚአብሔር አላለልህም" እያሉ ስልጣን ሊሰጡት አልቻሉም። ባለሟሉ በስቅለት ዕለት ወደ ራስ ኃይሉ ቀርቦ " ጌታዬ! ዛሬ እግዚአብሔር ተሰቅሏልና በሌለበት ይስጡኝ" አለ ይባላል።
ደብረ ማርቆስ ብዙ ከተሞች መኪና የሚባል ነገር ሳያውቁ አውሮፕላን ማረፊያ ነበራት። ከ1937 ዓ/ም ጀምሮ እስከ 1987 ዓም ድረስ መደበኛ በረራ አልተቋረጠም ነበር። ከ1995/6 ዓ/ም በኋላ ሙሉ ለሙሉ ተቋረጠ። ያሳዝናል። አሁን እንደገና እየተሰራ ነው። ቢዘገይም ለልጆቻችን መድረሱ አይቀርም። አያቴ በበቅሎ አደገ፣እኔ በመኪና ኖርሁ፣ ልጄ ደግሞ በሮቤላ ( አውሮፕላን)።
ደብረ ማርቆስ የጎጃም ጠቅላይ ግዛት ዋና መዲና በመሆን ለብዙ ዘመን አገልግላለች። አሁን የከተማይቱ ድምቀት የሆነው የንጉስ ተክለሃይማኖትን አደባባይ ያሰሩት ኃይለ ስላሴ ዘመን ጎጃንም እንዲያስተዳድሩ በተሾሙት እና "አማራ አንገቱ አንድ ነው" በማለት የሚታወቁት የሸዋው አርበኛ ደጃዝማች ፀሐዩ እንቁስላሴ ነው። ዐብዬ ብርሌ የተባለ የግሽ ዓባይ ተወላጅ በ1957 ዓም በደብረ ማርቆስ ከተማ የንጉስ ተክለሃይማኖት ትምህርት ቤት ተማሪ በነበረበት ወቅት ፀሐዩ እንቁስላሴ የንጉስ ተክለሃይማኖት አደባባይን ሲያሰሩ በግል ጉዳይ የሚመጣውን ባላገር ሁሉ ድንጋይ እና አፈር ያሸክሙ እንደነበረ እና እራሳቸውም እየተዘዋወሩ ያስተባብሩ እንደነበረ ያዬውን "በሀገር ፍቅር ጉዞ" በተሰኘው መፅሐፉ አስፍሯል።
ዴንማርክ ዕመት እስከ ዓመት እንደ ጋለሞታ ያለምንም ስራ ሲገማሸር የሚኖረውን የጨሞጋን ወንዝ ተጠቅማ ኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጨት ብትችል ከቀን አምስት ጊዜ በርቶ እየጠፋ ቆሎ ዘግኘ የገዛውትን ባለብዙ ብር ዘመናዊ ማንደጃ ( ስቶቨ) ከአንዴም ሁለት ጊዜ ባላበላሸብኝ ነበር። በ2002 ዓ/ም ከቻይና መንግስት በተገኘ ብድር የጨሞጋ ሐይል ማመንጫ ሊገነባ ስምምነት ላይ የተደረሰ ቢሆንም ችግሩ ከእኛ ከቻይና ሳይታወቅ "እልም" ብሎ ቀረ። ደብረ ማርቆስ በዙሪያዋ ሰንተራ፣ እነራታ፣ ወንቃ፣ አባ አስራት ገዳም ፣ እንግጫ እና የመሳሰሉ ሰፈሮች አሉ። እነራታ የአፄ ምኒልክ እናት የወይዘሮ እጅጋዬሁ ኃይሉ የትውልድ አገር ነው።ሰንተራ ድሮ እነ ተድላ ጓሉ ፈረስ ጉግስ የሚጫወቱበት ለጥ ያለ መስክ ነው። መስኩ አሁንም ከነ ግርማ ሞገሱ አለ። አባ አስራት ገዳም - በ1816 ዓ/ም አካባቢ አባ አስራት በተባሉ አባት የተመሰረተ ገዳም ነው።
ፀሐዩ እንቁስላሴ ምንም እንኳ መሰረተ ልማት በመገንባት ጎበዝ ቢሆኑም ኃይለ ስላሴ በጣሉት የመሬት ግብር ብዙ አቤቱታ ይቀርብባቸዋል። አንድ ቀን ሰውነቴ የሚባል ግለሰብ ደጃዝማች ፀሐዩ እንቁስላሴ ላይ አቤቱታ ይዞ ይቀርባል። በወቅቱ ኃይለኛ ዝናብ እየዘነበ ስለነበረ ደጃዝማች ፀሐዩ "አያ ሰውነቴ! ዝናቡ እንዳይመታህ ወደ ውስጥ ዝለቅ( ግባ)" ሲሉት አያ ሰውነቴ "ጌታዬ! እኔን የመታኝ ዝናቡ ሳይሆን ፀሐዩ ነው" ሲል በቅኔ የደጃዝማች ፀሐዩን በደለኛነት ተናገረ ይባላል። ቅሬታው ሲበረታ ጃንሆይ ኃይለስላሴ ደጃዝማች ፀሐዩ እንቁስላሴን አንስተውም ወደ ከፋ ወስደው በእሳቸው ፈንታ መጀመሪያ ደጃዝማች ደረጀ መኮነንን ቀጥሎም ልጅ የኃይለማርያም ከበደን ወደ ደብረ ማርቆስ ላኩ። ወዲያው ደርግ ገባ።ደጃዝማች ፀሐዩ እንቁ ስላሴም ደርግ ጋር ገጥመው ህይወታቸው አለፈ። ነፍስ ይማር!
ደብረ ማርቆስ አሁን "ሪጅኦፖሊታን" የሚባል የከተማ የዕድገት ደረጃ ላይ ደርሳ በአራት ክፍለ ከተማ ተዋቅራለች። አብማ ፣መንቆረር፣ደጃዝማች ተድላ ጓሌ እና ንጉስ ተክለሃይማኖት የክፍለ ከረማውን ስም ይዘዋል።
ከደብረ ማርቆስ መሐል ከተማ ምስራቃዊ ክፍል ላይ ሁለት የትምህርት ተቋማት ትውልድ መቅረፅ ላይ ተጠምደው ይገኛል። አንደኛው በ1957 ዓ/ም የተመሰረተው የእንድማጣ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ሲሆን ሁለተኛው በ1999 ዓ/ም የተመሰረተው የደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ነው። ሁለቱም ተቋማት ከላይ ከደጋው እየወረደ የውሰታን መስክ ለሁለት ሰንጥቆ ጨሞጋ ወንዝ ጋር ከሚገናኘው የውሰታ ወንዝ አጠገብ ነው የተመሰረቱት። የውሰታ ወንዝ በበጋ ውሃው ቢቀንስም በክረምት ድልድዩን ሸፍኑ የትራንስፖርት እክል ይፈጥራል። ውሰታ የወንዙም የመስኩም ስም ነው። ዋለልኝ አዘነ የተባለ ዘፋኝ የሚወዳትን ልጅ ቤት በአቅጣጫ ሲጠቁም እንዲህ ይላል።
ደገኛ በቅሎውን ይለዋል አምባላይ
ቤቷ ደብረ ማርቆስ ከውሰታ በላይ።
ዘፋኙ ከውሰታ በላይ ሲል ምን አልባት የእንድማጣ እየሱስ ወይም የእንግጫ ሰፈር ያለችውን ቆንጅዬ ልጅ ይሆናል። እኔም አንድ ቀን ከእንግጫ የመጣች ቆንጅዬ ልጅ አይቻለሁ። እዚያ አካባቢ የገጠር ውበት ከነ ክብሩ ታገኘዋለህ። የደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ተማሪ በነበርንበት ወቅት የእንድማጣ ትምህርት ቤት ተማሪዎች ከትምህርት የሚለቀቁበትን ሰዓት አስልተን ከግቢ እንወጣ ነበር። እኔ ግን ያው "ጨዋ ልጅ" ስለሆንሁ ውበት አድንቄ ነው የምመለስ። ዩኒፎርም (የተማሪዎች የደንብ ልብስ) ውበት እንደሚጨምር ያረጋገጥሁት ከእንድማጣ ትምህርት ቤት እንስት ተማሪዎች ነው። የልብስ ሰፊዎች ለእንስቶች ውበት የራሰውን አሻራ አሳርፈዋል። ልብሱን ከዳሌ አስታርቀውና አስማምተው ነው የሚሰሩት።
ውሰታ መስኩን የደብረ ማርቆስ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ለሁለት አላማ ይጠቀሙበታል። ኳስ የሚወዱ ተማሪዎች በቡድን ይጫወቱበታል። እኔን ጨምሮ ኳስ የማይወዱ ተማሪዎች ግን ከሔዋን ጋር ንፁን አየር ስበው፣ ቫት ( የግብር አይነት) ሳይከፍሉ ተዝናናንተው፣ አለፍ ሲልም በፍቅር ተደባድበው፣ ሸግዬ ጊዜ ያሳልፉበታል።
በከተማው ወደ ዩኒቨርሲቲው መኼጃ መስመር የስነ ፅሑፍ አድባር የሆኑት የሃዲስ አለማየሁ የክብር ሃውልት ሌላው የከተማይቱ ድምቀት ሆኗል።ሃዲስ አለማዬሁ ከጠላት ወረራ በኋላ የኢትዮጵያ በዲፕሎማትነት በሃገረ እየሩሳሌም ተመድበው በሚሰሩበት ጊዜ በሁለት ሂዷ እስራኤል ያደገች ክበበፀሐይ በላይ የምትባል ኢትዮጵያዊ ወጣት ላይ አይናቸው አረፈ። ወደዷት እና አገቧት። ወይዘሮ ክበበ ፀሐይ በላይ። ጥሩ የፍቅር ጊዜ ቢኖራቸውም ልጅ ትዳራቸው በልጅ ሳይታጀብ በ1954 ዓ/ም ወይዘሮ ክበበፀሐይ ለዘላለሙ በሸክላ ሰሪው ተጠራች። ከዚያ በኋላ ሃዲስ ህይወታቸው እስካለፈበት ድረስ ለአርባ ዓመታት ያኽል ሌላ አላገቡም። በአንድ ወቅት ጋዜጠኛ ጥበቡ በለጠ ሃዲስን ለምን እንዳላገቡ ሲጠይቃቸው "ጣቴ ላይ ያለችውን ቀለበት ያሰረችልኝ ክበበፀሐይ ናት። እና ቀለበቷን ማን አውልቋት ነው የማገባው?" ሲሉ መለሱ። ፍቅር እስከ መቃብር በተግባር ይኼ ነው።
ደብረ ማርቆስ ከባህሏ ጋር የታረቀች፣ ወግና ልሟዷን ጠብቃ የያዘች ከተማ ነች። የጎጃም የባህል ልብስ በያይነቱ ተለብሶ ታገኘዋለህ። የህዳር ማርያም አብማ ታቦት ለማስገባት ብቅ ካልህ በብዝሃ ጥለት ያሸበረቀ ከእንክርት እስከ ሙሉ ሽንሽን፣ ከጉርድ ሽንሽን እስከ አርባ ሽንሽን በለበሰች ውብ ሴት አይንህን አስደስተህ ትመለሳለህ። የጥምቀት ዕለት እንድምጣ ሥላሴ ጎራ ብትል ከአንገት እስከ ጡት ማረፊያ( ታችኛው የደረት ክፍል) ድረስ በቁልፍና በተለያዩ ዲዛይኖች የደመቀ አርባ ሽንሽን በለበሰች፣ እጇን በጠልሰም ( በአምባር)፣ እግሯን በአልቦ፣ራሷን በባውንድ(ጥምጣም)፣አንገቷን በድርብ ወይም ሽርብ ድሪ አስውባ በምትሞናደል የደብረ ማርቆስ ጉብል ውበት ልትማረክ ትችላለህ። ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ጎራ ብትል አባቶች ሲፈልጉ መብሩቃቸውን፣ ሲሻቸው ባት ተሁለታቸውን ገድግደው ባማረ ጋቢ ተጀቡነው ፈጣሪያቸውን አመስግነው ሲመለሱ ታገኛለህ። ጋቢ የክብር ልብስ ነው። በቤተ ክርስቲያን፣ ጥሪ ቦታ፣ ሽምግልና (የእርቅ ቦታ) ይለበሳል። አንድ ሽማግሌ ጥሪ ቦታ ጋቢ ሳይለብስ ቢኼድ " እሯ! ምን ቢነቀን ነው ጋቢውን ጥሎ እንደ ውርጋጥ መምጣቱ" ሊባል ይችላል።
አንዴ አብማ ሰፈር ገብተን እንመለስ እንዴ? ለመጀመሪያ ጊዜ የአብማን ጠላ የቀመስሁት ብቻዬን ነው። አንድ ቀን ከዩኒቨርሲቲ ወጥቼ ወደ ንጉስ ተክለሃይማኖት አደባባይ ሄድሁ። በንጉስ ተክለሃይማኖት አደባባይ ውስጥ "ሙሉ ጎጃም" አጠገብ ትቂት ደቂቃዎች ተቀምጨ ወደ ረዕቡ ገብያ የሚወስደውን መስመር ተከትዬ ጉዞ ጀመርሁ። አብማ ቤተክርስቲያን ሳልደርስ ወደምስራቅ አቅጣጫ ባለው የውስጥ ለውስጥ መንገድ ዙሪያ ገባውን እየቃኘሁ ስንቀሳቀስ የተጠቀለለ ወረቀት አናቷ ላይ ያጠለቀች እንጨት ቀጥ ብላ ቁማ ወጪ ወራጂውን "ኑ ጠላ ጠጡ" የሚል ማስታወቂያ ባዬሁ ጊዜ አንድ ሁለቷን ቀመስ ለማድረግ ጎራ አልሁ። ውበቷ የሚያነሆልል ድንቅ ውበት የተቸራት ወጣት አስተናጋጅ ተቀበለችኝ። በሎጋ ብርጭቆ ጠላውን ልትቀዳልኝ ከፊቴ ጎንበስ ስትል ዓይኔ እንደ ጦር የሚዋጉ፣ ልውጣ ብለው ከለበሰችው ነጭ ሹራብ ጋር ግብግብ የገጠሙ ጤቶቿ ላይ አረፈ።
ሔዋን ሰይጣን ይሆን ሌላ አካል "አሳስቶኝ አመጣሁት" የምትለውን ዕፀ በለስ ካቀመሰችን ቀን ጀምሮ የአዳም ዘሮች ፈተናችን የበዛ ሆኖብን እንጅ ግቢ( ዩኒቨርሲቲ) ውስጥ ከተዋወቅኋት ልጅ አትበልጥም። ራጉኤልን የግቢይቱ ልዩ ናት። በገባን በመጀመሪያዎቹ ሳምንታት እኔ ወንድሟን ልተካ፣ እሷ እህቴ ልትሆን ተስማምተን ነበር ወዳጅነት የመሰረትነው። እንዴት ዓይነት ዕዳ ይገባል ሰው ጎበዝ!?
ዓይኖቿ በመጠን ትንንሽ ሆነው ፍቅር ይተፋሉ። ጎራዳው አፍንጫዋ ድንቡሽቡሽ ያሉ ጉንጮቿ ጋር የውበት ሰገነት ፈጥሯል። ጥርሶቿ አይሳቁ እንጅ ከሳቁ የአንድ ብርጌድ ጦር ያኽል ያስበረግጋሉ። ከሰንተራ መስክ እስከ ወሰታ፣ ከወሰታ እስከ ራባ ጫካ፣ ከመምህራን ኮሌጅ ሰፈር እስከ ወንቃ ያሉ ውብ ቦታዎች በሁለቱ እህት እና ወንድማማቾች ወጣቶች አጀብ የተሞላበት ጉብኝት ተካኺዷል። እንደዚህም ሆኖ እህቴ ናት። እኔም ወንድሟ ነኝ። ብዙ በጎ የጨዋታ ጊዜዎች አልፈዋል። አሁን የሌላ ናት። የሌላ ሁና ግን ከገጣሚ ኤልያስ ሽታኹን ተውሼ የሚከተለውን ጋበዝኋት:-
ሠርቄ ልሳምሽ
ሰርቄ ልቀፍሽ - ሰርቄ ልሳምሽ፣
ከባልሽ በፊት ነው ልቤ የሚያስብሽ።
ባልሽን እርሽልኝ
መንትፌ ልቀፍሽ- ደብቀሽ እቀፊኝ
ጨለማን ስናስስ - ከብርሃን ስፊኝ።
አበጀሁ ሰረቅሁሽ
እሠይ እሰርቃለሁ መቃብር እስክኾን
ማነው የሚያውቅልኝ
ባልሽስ እራሱ ከእኔ ዘርፎሽ ቢኾን።
ትንሿ ምሳር ወይም ጥልቆ ትልቁን የኮሶ ዛፍ ገዝግዛ ትጥላለች! (አገሬ አዲስ)
ትንሿ ምሳር ወይም ጥልቆ ትልቁን የኮሶ ዛፍ ገዝግዛ ትጥላለች!
አገሬ አዲስ
ትንሿ ምሳር ወይም ጥልቆ ትልቁን የኮሶ ዛፍ ገዝግዛ ትጥላለች!
ነሓሴ 7 ቀን 2014 ዓም(13-08-2022)
ዕድሜ ለሸጋው አማርኛ...
እስክንድር ነጋ ለምንና እንዴት ከመሰረተው ፓርቲ – ባልደራስ እራሱን ሊያገል ቻለ… ? (ወንድወሰን ተክሉ)
እስክንድር ነጋ ለምንና እንዴት ከመሰረተው ፓርቲ - ባልደራስ እራሱን ሊያገል ቻለ... ?
ወንድወሰን ተክሉ
*.... የታላቁ እስክንድር ነጋ እርምጃ የይስሙላውን ሰላማዊ ትግል ህልፈተ ህይወት ማሳየቱና በአጠቃላይ በሀገረ...
ግራ በገባው ሕገ መንግስት ግራ የምትጋባ ሀገር፤ ክልልም – ሀገርም…!!! ( ያሬድ ሀይለማርያም)
ግራ በገባው ሕገ መንግስት ግራ የምትጋባ ሀገር፤ ክልልም - ሀገርም...!!!
ያሬድ ሀይለማርያም
ክልል ብቻ ሳይሆን አገር የመሆንም መብት የሚፈቅድ ሕገ-መንግስት ይዞ የወላይታን፣ የጉራጌን እና የሌሎች ሕዝቦችን...
የጉራጌ ክልላዊ መንግሥት (ብርሐኑ ዘርጋው )
የጉራጌ ክልላዊ መንግሥት
ብርሐኑ ዘርጋው
የኢትዮጵያ መንግሥት ፈፅሞ ችላ ሊባሉ የማይገባቸው ህዝባዊ ጥያቄዎች እንደ ማዕበል በራሱ ላይ እያንጃበቡበት ነው:: ለጥያቄዎቹ መልስ ለመስጠት ምናህል ዝግጅትና ፈቃደኝነት እንዳለ ለማወቅ በቅርቡ የጉራጌ ህዝብ ባነሳው የመብት ጥያቄ ዙሪያ የተሰጠው መልስ ምልክት ይሰጠናል:: እምቢተኝነትና ኢህጋዊነት የአብይ መንግስት መለያ ምልክቶች ከሆኑ ቆይቷል:: በተጨማሪም የዶ/ር አብይ አስተዳደር የወደቀና የተሸረሸረ እምነትም የማይጣልበት መንግሥት መሆኑን የምናውቀውየሕዝብን ደህንነትንና ሰላም ማስጠበቅ ባለመቻሉም ነው::
ዶ/ር አብይን እንድንታዘበውና እምነታችንን እንዳንጥልበት ካደረጉን ጉዳዮች አንዱ ምናልባት ምዋነኛው "ላም አለኝ በሰማይ ወተቷን እማላይ" አይነት ወሬዎችን ባለማፈርና ባለመፍራት ያለይሉኝታ ሲያዥጎደጉድና ከተግባሩ ጋር የተጋጨ ሥራ በመሥራቱ ነው::
ዶ/ሩ ኢትዮጵያ ሲሉና እኛ ኢትዮጵያውያን ኢትዮጵያ ስንል አንድ አለመሆኑም ከታወቀ ቆይቷል:: እያንዳንዱም ንግግር ኪሳራን እንጂ ትርፋማ አልሆነልንም:: ኢትዮጵያን በግዙፍ መርከብ ብንመስላት ከክምር በረዶ ጋር የምትላተምበት ወቅት ላይ እንደደረሰች መገመት እንችላለን:: የመርከቧ መሪ አቅም የተፈተነበትና የወደቀበት ሁኔታ ላይ ደርሰናል:: ሕዝብ በሰቆቃ ማእበል እየተናወጠ መሆኑ የሚካድ አይደለም:: ከሰሜን እስከ ደቡብ ከምእራብ እስከ ምሥራቅ ኢትዮጵያ የቀውስ አገር ሆናለች::
በዚህም ምክንያት በአብይ የለውጥ ባቡር ላይ የተሳፈሩት ሁሉ እየወረዱና አቅጣጫ እየለወጡባለበት ጊዜ ዶ/ር አብይን ግን ምንም ያናወጠው አይመስልም:: "ስንኖር ኢትዮጵያዊ ስንሞት ኢትዮጵያ" ብሎ ያቆላመጠባት መሪ ሃሳብ ማማለያና ማታለያ ሁና እንደተቆጠረች ቀርታለች:: ዛሬ ሕዝብ ሲሞት እንጂ ሲኖር ኢትዮጵያዊ መሆኑ በየቀኑ በግልፅ እየተለፈፈ እየተጨረሰ ነው:: ይህም በጣም የሚያሳዝን ነው::
ዲሞክራሲን ሊያለማምደን ለመጣ መምህር ማስፈራራት ማፈን ማሰርና መግደል የሕዝብንም ፍላጎትና ፈቃድ መናድ አይነተኛ የአስተዳደሩ ያሰራር ዘይቤ ሆኗል::
በተለይ በተለይ የአንድ አገር ትልቅ ክፍል የሆነ ሕዝብ ሲጎዳ ሁላችንም እንደተጎዳን መቁጠር በሚገባን አገር ውስጥ አማራው እንደባይተዋር ተቆጥሮ የዘር ፍጅት ሲደርስበት የታላቂቷ ኢትዮጵያ መሪ ግን የሕዝብ ህመም ህመሙ የሕዝብ ስቃይ ስቃዩ አልሆነለትም:: አይኑን ከሰው ነፍስ አንስቶ ችግኝ ላይ ማዋሉ ፈጽሞ ሰብአዊም ይሁን ፍልስፍናዊ እይታው የተንሸዋረረ መሆኑን ያሳያል:: ይህም የሕዝብን አመኔታ ቦርቡሮታል::
ኢትዮጵያችን ዛሬ ከምንጊዜም ይልቅ ልዩነት የጦዘባት: ሰላምና ጸጥታ የጠፋባት መንግስቱም በዚህ ጡዘት ተመቻችቶ ለሽብርና ለዘር ፍጅት ተገቢውን ምላሽ ለመስጠት ተግባራዊ ፍላጎት የማያሳይበት ሆናለች:: ለዚህም ጡዘት ዋነኛ ምክንያት የሆነው ህገ መንግስት አሁንም በአብይና በመንግስቱ ልብ ውስጥ ዙፋኑን ዘርግቶ እስቲ ትሞክሩኝና እያለ ነው:: አብይም እስከ ሞቱ ድረስ የሚዋጋለት ህገመንግስት እንደሆነ ደጋግሞ አስረግጧል:: ይህም ህገ መንግስት ለሕዝብ የተሰጠ ሰነድ ነው:: ከዚህ በመነሳት ከጊዜ ወደ ጊዜ ሕዝቡ ከሰነዱ እየጠቀሰ ተሰጠህ የተባለውን መብቱን ለማስከበር እየተጠቀመበት ነው::
ይህ ሰነድ ለትግሬ ለኦሮሞ ለአማራውና ለሌሎች የብልጽግና ገዢ መደብ የፌዴራል ከክልል እስከቀበሌ ላሉ አካላት የማይናቅ የንብረትና የስልጣን ጥቅም አስገኝቶላቸዋል:: ሕዝብ ግን በየእለቱ ካሉት በታች ከሞቱት በላይ ሆኖ በችግር እየኖረ ነው:: ይህም ፍጹም ድህነት ድምጹ እንዳይሰማና ካደባባይ እንዲርቅ አድርጎታል::
ይልቁንስ የሕዝብን ዲሞክራሲያዊ ጥያቄ የህገመንግስቱ ሰነድ የፈቀደውን መብት እንኳ ለማፈን ትልቅ ርምጃ ተጉዘዋል:: ይህም የዚህን መንግስት ድክመት ውድቀትና መፍረስ ያመላክታል:: ይህን ለማወቅ የወላይታ ሕዝብን የክልልነት ጥያቄውንና የደረሰበትን አፈና ማየት ይበቃል:: የሚገርመው ሻሸመኔ ስትነድ ያልታደገ የጦር ሃይል ወላይታን ለማንበርከክ ጊዜ ሳይወስድበት ፈጥኖ በመድረስ ጥቃት ፈፅሟል:: ያም ካልበቃ የሰሞኑን የታላቁን የጉራጌን ሕዝብ የክልል ጥያቄ ዋጋ ለማሳጣትእየተሄደበት ያለው የእብደት መንገድን ማጤን ነው:: ክልልነት ሲሰጠውና ሲወሰድበት ለጉራጌ ይህ የመጀመሪያው አይደለም:: ክልልነት መብት ነው:: በችሮታ የሚገኝ አይደለም:: ጉራጌም የጠየቀው መብቱ እንዲከበር ነው:: ህገ መንግስቱም ግልፅ ነው:: ከዛ ይልቅ ግን ብልጽግና ጉራጌ እንዳይኑ ብሌን የሚያያቸውን ሽማግሌ አባቶቹን የማዋረድ ተግባር ላይ መሰማራቱ የሚያሳዝን ነው:: ይህም የንቀት ጥግ ነው:: ሰላማዊውን ጉራጌ ካልናቀ ማንን ሊንቅ ነው? ይህም ታሪክን አለማወቅ ነው:: ተናቀም አልተናቀ ጉራጌ መብቱን መጠቀሙና መብቱ መከበሩ የማይቀር ነው:: ትግሉንም ይቀጥላል::
ጉራጌ ክልል መሆን አለበት ስንል ምክንያት ለመስጠት በመነሳሳት አይደለም:: ምክንያት የመስጠት ግዴታም የለበትም:: መብቱ ነውና መብት መሆኑ ብቻ በቂ ነው:: ጉራጌ መብቱን የመጠቀሚያ ጊዜው አሁን ነው:: ክልል ነንና እወቁልን እያለ ነው:: ማንም ግር እንዳይለው ለኦሮሞ ለትግሬና ለአማራ ክልል የሚሉት ቋንቋ ከሰራ ከነሱ በቁጥር ቢሆን እንጂ በምንም ለማያንሰው ለጉራጌም ይሰራል:: ክልል አይሰራም ከተባለ ኦሮሞም ትግሬም አማራም ክልልነትን መተው ይገባቸዋል:: ያደርጉታል ብዬ ግን ራሴን አላታልልም::
ጉራጌ ኢህአዴጋዊ በትር ያረፈበት የንግድና የኑሮ አቅሙ በሽብርና በሻጥር የተዘረፈና የተቃወሰበት ሕዝብ ነው:: ኢህአዴጋዊ አማራም ይሁን ትግሬ ወይም ኦሮሞ ጉዳቱን ቢያባብስበት እንጂ አልታደገውም:: ብልጽግናም ቢሆን ለጉራጌ ያለው እይታ መብቱን እስከ መንጠቅ የደረሰ ነው:: በተለያ የዘይቤ ሊከፋፍሉት የጀመሩትን ሕዝብ መብቱን አሳጥተው የራሱን እድል በራሱ መንገድ እንዳይወስን ሊያደርጉት እየፈለጉ ካልሆነ በቀር ያልተስማማበትንና ህገ መንግስታዊ ያልሆነን እቅድ ሊጭኑበት አይገባም::
በተለይም ድልድይ ላልሰራህለት ትምህርት ቤት ላልገነባህለት መብራት ላላስገባህለት ምን ጊዜም ግን ቀረጥ የሰበሰብክበት ማሕበረ ሰብ ላይ የሞትና የሕይወትን ውሳኔ ልትወስንበት አትችልም:: ጉራጌ በራሱ አቅምና ሃብት እስከዚህ ደርሷል:: ከታሰረበት የዞን እስር ቤት መፈታት አለበት:: የእስር ሰንሰለቱንም ሰብሮ መውጣት አለበት:: የራሱን ባህልና እሴቶችን የሚያንፀባርቅ የህገ መንግስት የፖለቲካ የጸጥታና ሰላም የትምህርት የጤና የእርሻ የመብራትና ውሃ ሃይል የህግና ዲሞክራሲያዊ አስተዳደር የማህበራዊ ኑሮ ወዘተ ሕዝብ ተኮር አገልግሎትና እንቅስቃሴማድረጉን ይቀጥላል:: ሕዝብ ለሕዝብ እንደቀድሞው ሁሉ አብሮ የሚኖርበትን መፍትሄ በራሱ ይሻል:: ስለዚህ የጉራጌ ሕዝብ ራሱን በትልቁ ለማስተዳደር መብቱን ለመጠቀም ሲሞክር የፖለቲካ ጨዋታ ህጉን በጨዋታው መሃል ላይ ለመለወጥ በክለስተር ተደራጁ ማለቱ ሕዝብን መናቅና እንደሰውም አለመቁጠር የእብደት ጥግ ይመስለኛል:: አይገባችሁም እየተባልን ነው:: እኛ ደግሞ እናንተ ከተገባችሁ እኛም ከማንም አናንስም እያልን ነው:: በዚህ መንገድ ሕዝብን ለማፈን የሚደረገውን ጥረት በጥብቅ እንዋጋዋለን:: እናወግዘዋለንም:: መፋለሚያ ዘዴአችንም ሰላምን የተላበሰ ነው:: የጉራጌ ሕዝብ ለክልልነት ለዲሞክራሲያዊ አመራር አድልዎ ለሌለበት እድገትና ለሰላም ዝግጁ ነው:: ማደናቀፉን ተዉት!



























